በትግራይ ክልል ለተፈጠረው ሰብአዊ ኪሳራና አለመረጋጋት ሃላፊነቱን የሚወስደው ትግራይን ሲመራ የነበረው ህወሃት እንደሆነ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ለድርጅቱ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በጻፈው ማስታወሻ ይፋ አደረገ።
ሚስጥራዊ ነው የተባለውን ማስታወሻ እንዳገኘው የገለጸው ፎሬይን ፖሊሲ መጽሄት እንዳብራራው ከሆነ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም አስተዳዳሪ አቺም ስቴይነር በምስራቅ አፍሪካ ደም አፋሳሽ ግጭት እንዲፈጠር ያደረገው ኢትዮጵያን ላለፉት 30 አመታት ያህል ሲመራ የነበረው የህወሃት አመራር በትግራይ ክልል በሚገኘው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ላይ መብረቃዊ ያሉትን ጥቃት በመሰንዘር የሰሜን እዝ ንብረቶችን በሙሉ ለመቆጣጠር የታለመ ነበር ብሏል።
የትኛውም አገር ወታደራዊ ጥቃት ሲደርስበት የአጸፋ ምላሽ እንደሚሰጥ የታወቀ መሆኑን የሚያብራራው ማስታወሻው፤ ከለውጡ በኋላ ያለው መንግስት የፖለቲካ ስርአቱን ለማስተካከልና ሽግግሩን የሚያሳኩ ሁሉን አቀፍ ውይይቶችን ለማድረግ የሚያስችሉ አበረታች እርምጃዎችን ለመውሰድ ቢሞክርም ላለፉት ሁለት አመታት በዘለቀው የህወሃት ተንኳሽነት ምክንያት የተቀሰቀሰውን ችግር የአለም አቀፉ ማህበረሰብ በተሳሳተ መንገድ በመረዳቱ ኢትዮጵያ ላይ አስፈላጊ ያልሆነ ጫና እያሳደረ መሆኑን ገልጿል።
READ THE ENGLISH FULL ARTICLE HERE
ለጋሾችና የመብት ተማጋቾች ሁኔታውን ከማስጮህ ተቆጥበው በመልሶ ማልማትና በሰብአዊ እርዳታ ስርጭት ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ ምክረ ሃሳብ ስለማቅረቡ የተነገረለት ማስታወሻው፤ “ተፈጽመዋል የተባሉ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን መሪነትና በአለም አቀፉ ማህበረሰብ ተሳትፎ ሊጣሩ ይገባል” ብሏል።
በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ወደ አንድ ወገን ያጋደሉ ሰብአዊ መብቶችን የተመለከቱ ዘገባዎች ግጭቱን ከማባባስ ባለፈ አፍራሽ አስተዋጽኦ ሊኖረው እንደሚችልም ማስታወሻው አስጠንቅቋል።
“ላለፉት 27 አመታት በነበረው የህወሃት አገዛዝ ህዝቡ በከፍተኛ ምሬትና ሮሮ ውስጥ መኖሩ ሊዘነጋ አይገባም” ያለው ማስታወሻው፤ የአለም መንግስታትን በማሳሳት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ሲያደርጉት ለነበረው ለውጥ እንቅፋት በመሆን አገሪቱን እዚህ ችግር ውስጥ የከተታት የህወሃት አመራር ቡድንም በክልሉ ለተፈጠረው ሰብአዊና ቁሳዊ ውድመት የአለም ማህበረሰብ ተጠያቂ ሊያደርገው እንደሚገባም አስገንዝቧል።
የህግ ማስከበር ዘመቻውን ተከትሎ ህወሃት በደረሰበት ሽንፈት ከ10ሺህ በላይ የወንጀል እስረኞችን ከማረሚያ ፈትቶ በመልቀቅ የትግራይ ክልል ለአስተዳደር እንዳይመች ብሎም የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እንዲፈጸሙ ወንጀሎችና ግድያዎች እንዲበራከቱ ስለማድረጉም ማስታወሻው ዘርዝሯል።
RELATED ARTICLE
የኢትዮጵያ መንግስት እነዚህን ችግሮች ለመቀነስ የሚያስችሉ እርምጃዎችን ለመንግስት ሰራተኞች ውዝፍ ደመወዝ በመክፈል የባንክ የቴሌኮምና የመብራት አገልግሎቶች ዳግም ወደ ስራ እንዲመለሱ ማድረጉን አትቷል።
ማስታወሻው የህግ ማስከበር ዘመቻውን ተከትሎ ለእርዳታ ሰጪዎችና ለአለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት አካባቢው ዝግ ሆኖ እንዲቆይ ስለመደረጉ አስታውሶ፤ የህግ ማስከበር ዘመቻው በመጠናቀቁ የኢትዮጵያ መንግስት ለጋሾችና ጋዜጠኞች ወደ አካባቢው መሄድ እንደሚችሉ ቢፈቅድም የድርጅቶቹ ሰራተኞችና ጋዜጠኞች የተሳሳቱና የተዛቡ መረጃዎችን አሁንም እያሰራጩ እንደሚገኙ ገልጿል። Ena