“ተማረ” የተባለ አመራር በሁለቱም ወገን በኩል ያለውን የግጭት ምክንያት በውል ተረድቶ አስታራቂ መፍትሄ እንደማምጣት እና ማህበረሰቡ የሰላም አየር እንዲተነፍስ ከማመቻቸት ይልቅ “በሰው ቁስል እንጨት ስደድበት” 


የሙዚቃ ቅኝት መሰረት የባቴ፣ የአንቺ ሆዬ እና የትዝታ፤ የስነ-ግጥም ውበት መለያ የወል ቤት መሰረት ነው – ወሎ!!

ታላቁ የስነ-ጽሁፍ ሰው የዓለም ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ቀዌሳ ስለ ወሎ እንዲህ ብሏል፡- “ወል” የሚለው ቃል እጅግ ጥንታዊ የኩሽ ጥቁር ህዝብ የህብር/የአንድነት አመልካች ትርጉም ያለው መሆኑን ያስረዳል፡፡

ጋሽ ፀጋዬ:-ወሎ ስንል አንድነት (United) ማለት እንደሆነ ይገልጻል፡፡ ወለ-ጋ ስንልም ደግሞ ታላቅ አንድነት ማለት እንደሆነም አስረግጦ ነግሮናል፡፡በተመሳሳይ ወል-ቂጤ፣ ወሊ-ሶ፣ ወል-ወል፣ ወላ-ይታ (የእውነት አንድነት)፣ ወል-መራ፣ ወለን-ጪቲ፣ ወል-ዲያ ወዘተ… በዚሁ አውድ የሚጤኑ መሆናቸውን አንስቷል፡፡

ፀጋዬ ስለ ገዳ ስርዓት ጥልቀት ያለው ሃገር-በቀል ሃይማኖት፣ ህግ፣ ባህል፣ ፍልስፍና … በአጠቃላይ የዋቃ/ፈጣሪ መመሪያ መሆኑን ዋቢ በመጥቀስ በአስረጂነት አብራርቷል፡፡

ከዚህ አንጻር ወሎ ብዝሃነትን በተግባር የሚኖር ማህበረሰብ መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡

“ሰግደን ስናበቃ ታቦት እናስገባለን”፣

ስማቸው “መሃመድ ሃይለየሱስ” አይነት በርካታ ሰዎች መኖራቸው ፤

“የገብርኤልን ታቦት ያሰሩት ሃጂ እገሌ ናቸው” … ወዘተርፈሃቆች ገላጭ ማሳያዎች ሲሆኑ ወሎ ልዩነትን ያለምንም ችግር መቀበልና ማስተናገድ የሚችል ማህበረሰብ መሆኑን ያሳያል።

ወሎ የባህል ልዩነትን እንደ አለላ በውበትነት፤ የሃይማኖት አለመመሳሰልን ደግሞ እንደ ጌጥ፤ የአስተሳሰብ ልዩነትንም ተፈጥሮዋዊ መሆኑን በንግግር ብቻ ሳይሆን በተግባር ኖሮ ያስመሰከረ ማህበረሰብ ነው፡፡ወሎ በጆግራፊያዊ አቀማመጡ እና በታሪክ አጋጣሚ ከሌሎች ማህበረሰቦች ጋር ተጎራብቶ ለዘመናት የኖረ በተለያየ መልክ የሚደርሱበትን ከፍተኛ ተጽዕኖዎች በመቋቋም የራሱን ማንነትና ባህል ጠብቆ የሌሎችንም አጎራባች ማህበረሰቦች ደግሞ አክብሮና አቅፎ የሚኖር የጽናት ተምሳሌትም እና ከፍ ያለ የስነ-ልቦና ጥንካሬ ያለው ነው – ወሎየሰሜን ሸዋ ከሚሴም አከባቢ ማህበረሰብ ደግሞ በተለየ ሁኔታ ከወሎ ማህበረሰብ ጋር ያለው ቁርኝት ጥብቅ ነው፡፡ በሃዘንና በደስታ፤ በከፍታና በዝቅታ፣ ለዘመናት በጥብቅ የተቆራኙ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው ማለት ይቻላል፡፡

እውነታው እና ሃቁ ከላይ የተገለጸው ሆኖ ሳለ ታዲያ ይህ ህብርን/አንድነትን እንደ እሴቱ ብቻ ሳይሆን ወሎ (አብሮነት) መጠሪያ ስሙ ጭምር የሆነው ማህበረሰብ እንዴት ስለ ግጭት እና መለያየት አስከፊነት ሊነገረው ይገባል? ይህ ከተፈጥሮዋዊ ባህሪው እና ማንነቱ ውጪ በተቃራኒው እንዴት የፖለቲካ መሳሪያ እና ኢላማ ሊሆን ቻለ ብሎ መጠየቅም ተገቢ ይሆናል።

አሁን አሁን ፖለቲከኛ ይሁኑ አልያም አክቲቪስት ወይንም ደግሞ የፖለቲካ ደላላ ሚናቸው በውል የማይታወቅ ግን ደግሞ የመንግስትን መዋቅርና ስልጣን ይዘውና ተጠቅመው የክተት አዋጅ እያወጁ ሁለቱን ለማጋጨት የፖለቲካ ትርፍና ጥቅም አገኛለሁ ብለው የሚያስቡ ጫጩት ፊደላውያን አላማ ግን እጅግ የማይገባ ነው፡፡ የሚያስከትለው ማህበራዊ መናጋት ከፍተኛ ነው።

በህቡዕም የማህበረሰቡን ሰላም ለማደፍረስ የሚሰራም አካል እንዳለ ከሁኔታው መረዳት ይቻላል።እኔ አውቅልሃለሁ አባዜ የፅንፍ እና የዳር ፖለቲካ ምች ነው። የፅንፍ ፖለቲካ እኔ እንጂ እኛን አያውቅም። የዳር ፖለቲካ ጩኸት እንጂ ውጤትና መፍትሄ አይታየውም። ለራሱ እንጂ ለሌላው አያስብም። አሁንን እንጂ ነገን አሻግሮ አይመለከትም። ግርግር እንጂ ስክነት የለውም። ፅንፈኛ እሱን መሰል ፅንፈኞች ሲያጨበጭቡለት ትክክል የሆነ ይመስለዋል። በሞቅታ መስመር ይለቃል። ጊዜያዊ ስሜት እንጂ ስሌት አይገባውም።

“ተማረ” የተባለ አመራር በሁለቱም ወገን በኩል ያለውን የግጭት ምክንያት በውል ተረድቶ አስታራቂ መፍትሄ እንደማምጣት እና ማህበረሰቡ የሰላም አየር እንዲተነፍስ ከማመቻቸት ይልቅ “በሰው ቁስል እንጨት ስደድበት” አይነት የጭር-ሲል አልወድም ትርክት በመፍጠር በሃቅ በመዳኘት መዳኛ ከመሆን ይልቅ እራሱ ከሳሽ እና ፍርደ-ገምድል ሆኖ ይቀርባል። ይህ አካሄድ ዳፋው ብዙ ነው። በታሪካችን ህዝብ ለህዝብ ሲጋጭ አላየንም ለግጭት መነሻ የሚሆኑት ግን “አውቅልሃለው” ባይ አሟሟቂ መሃይማኖች ናቸው።

አሁን እያየን ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ህዝብን አገለግላለሁ የሚል ነገር ግን የግጭት ነጋሪት የሚጎስም በአንድነት ስም ጭፍለቃን የሚናፍቅ ሸፍጠኛ የሰፈር ካድሬ በእኩልነት ፍትህን መሰረት ያደረገ አመራር ይሰጣል ብሎ ማሰብም የዋህነት ነው። እንኳን ህዝብን ይቅርና ራሳቸውን በወጉ መምራት የማይችሉ ዝቅ ያለ ስነልቦና እና በቂ ክህሎት የሌላቸው ባህላዊና የጫጬት “ፖለቲከኛ” ቀመር የአርብ እና እሮብ የደከመ አስተሳሰብ እና የሾቀ ስሌት ውጤት ነው።

ህዝብን ለመምራትም የአስተሳሰብ ልዕልና፣ የስነ-ምግባር መርህ፣ የመስከንና የመረጋጋት፣ የሞራልና የስነልቦና ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል ክህሎትና ዕሴቶች ዝግጁነትን ይጠይቃል።መንግስትን ዋጋ የሚያስከፍሉት እንዲህ አይነቶቹ እንከፍ “ካድሬዎች” ናቸው። (ካድሬ ከተባሉ ማለት ነው) ማህበረሰቡ ግን ቢጣላ እንኳን የራሱ የሆነ ሃገረ-ሰባዊ የግጭት አፈታት ዘዴ እንዳለውም ልብ ይለዋል። ከልክ ያለፈ ያልተገባ ጣልቃ ገብነትም ተገቢነት ይጎድለዋል።

በሌላ መልኩ ደግሞ የህዝብ ውክልና ያላቸው ግለሰቦች ሊደመጡም፣ ሊከበሩም ይገባል። ነገር ግን ለምን ተናገሩ ብሎ ለማሸማቀቅ መሞከር፣ የማሰብና የመናገር ሰብዓዊ መብታቸውን ለመገደብ ያልተገባ ታርጋ ለመለጠፍ መሞከር ፀረ-ህዝብ ብቻ ሳይሆን ኢ-ዲሞክራሲያዊም ተግባር ነው። ይሁንና የተናገሩትን ሃሳብ ብቻ ነጥሎ መሞገት ደግሞ ይቻላል። ይህ ዘመናዊነት ጭምር ነው። ሲጠቃለል የነ ወረ-ባቦ፣ ወረ-ሂመኑ፣ ወረ-የጁ፣ ወረ-ኢሉ፣ የነ በላይ ዘለቀ ቂልጡ፣ የነ ወርቄና ጣይቱ… መፍለቂያ ህብር ነው – ወሎ።ፍቅር እንጂ ፀብ አይመጥነውም!በላይ ባይሳ

መጋቢት 14/2013 ዓ.ም


Leave a Reply