ሶስት የውጭ ድርጅቶች ከተቋቋሙለት አላማ ውጭ በመንቀሳቀሳቸው የመጨረሻ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ ለሶስት ወራት ታገዱ ሲል የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ኤጀንሲ አሳውቋል፡፡
አንደኛ MSF HOLLAND ሁለተኛ NORWEGIAN REFUGEE COUNCIL እና ሶስተኛ AL MAKTOUME FOUNDETION የተባሉ የውጭ ድርጅቶች የኢትዬጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፓብሊክ የሲቪክ ማህበራት ድርጅቶች ኤጀንሲ በሰጣቸው ፍቃድ በህጋዊነት በተለያዩ የሰብዓዊ ስራዎች ተሰማርተው እየሰሩ የቆዩ ድርጅቶች ሲሆኑ የድርጅቶቹን እንቅስቃሴ በተመለከተ ፍቃድ ሰጪው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ኤጀንሲ በሚያደርገው ክትትል መሰረት ድርጅቶቹ ከተቋቋሙለት አላማ ውጭ በመንቀሳቀስ፤
- አንደኛ- 1ኛ እና 2ኛ የተጠቁት ድርጂቶች የተለያዩ ሃሰተኛ መረጃዎችን በማህበራዊ ሚዲያ እና በሌሎች ዘዴዎች ሲያሰራጩ በመገኘታቸው፣
-ሁለተኛ – ሶስቱም ድርጅቶች ስልጣን በተሰጠው አካል የስራ ፍቃድ ያልተሰጣቸውን የውጭ ሃር ዜጎች ወደ ሃገር ውስጥ በማስገባት ከስድስት ወር በላይ ቀጥረው ሲያሰሩ በመገኘታቸው፤ - ሶስተኛ- 1ኛ የተቀመጠው ድርጅት ስልጣን በተሰጠው አካል ፍቃድ ያልተሰጣቸው የሳተላይት የሬድዬ መገናኛ መሳሪያውችን ወደ ሃገር ውስጥ በማስገባ የድርጂቱ ሰራተኞች አፍራሽ ለሆኑ አላማ ሲጠቀሙበት እና ይዘው ሲንቀሳቀሱ በጸጥታ አካላት ቀጥጥር ስር በመዋላቸው፣
- አራተኛ- 3ኛ የተጠቀሰው ድርጅት የትምህርት ሚንስቴር የኮቪድ-19 ፕሮቶኮልን ባለማክበር ፣ የበጀት አጠቃቀም ግልጽነት የጎደለውና በትምህርት ቤቱ ስም የሚመጣን በጀት ከአላማው ውጭ እየተጠቀመ በመሆኑ እንዲሁም በሰራተኞች አስተዳደር ችግር የታየበት በመሆኑ ምክንያት፤
ድርጅቶቹ ከተቋቋሙት አላማ ውጭና የሃገርን ጥቅም በሚጻረር መልኩ ሲንቀሳቀሱ በመገኘታቸው እንዲታረሙ በተደጋጋሚ ከድርጅቶቹ ሃላፊዎች ጋር ውይይት ቢደረግም ሊያስተካክሉ ስላልቻሉ አጠቃላይ ምርመራ ተደርጎ የመጨረሻ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ በአዋጅ ቁጥር 1113/2011 አንቀጽ 77(4) መሰረት አጠቃላይ የድርጅቶቹ እንቅስቃሴ ለሶስት ወራት የታገዱ መሆኑን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ኤጀንሲ አሳውቋል፡፡