አውሮፓ ደስርሰው ከተመለሱ በሁዋላ የህዳሴውን ግድብ የሃይል ማመንጫ ቁልፍ በመጫን አባይ ማብራት መጀመሩን ይፋ ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ “ቅዠት አይደለም ሃይል ወደ አውሮፓ እንልካለን” ሲሉ ተደምጠዋል። ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ሱዳንና ግብጽ እንኳን ደስ አላችሁ በማለት በሴራ ውስጥ ያለፈው ፕሮጀክት እውን መሆኑን አብስረዋል። ኤሌክትሪክ ማመንጨት የጀመረው የህዳሴው ግድብ እስካሁን 163 ቢሊዮን ብር ወጪ ተደርጎበታል
ሲጀምሩና ሲጨርሱ አምላካቸውን እጅግ አድርገው ያወደሱት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፣ “ዛሬ የአፍሪካ ትልቁ የኃይል ማመንጫ የህዳሴ ግድብ ሥራውን ጀምሯል። ይህ ለአኅጉራችን እንዲሁም አብረናቸው ሠርተን በጋራ ለመጠቀም ለምንሻ የታችኛው ተፋሰስ አገራት የምሥራች ነው። ዐባይ ወንዛችንን ሀገራችንን አልምቶ ጎረቤቶቻችንን ሊያረሰርስ ጉዞውን ቀጥሏል። ዛሬ ለኢትዮጵያ የብርሀን መባቻ ነውና መላው ኢትዮጵያውያን እንኳን ደስ አለን!” ብለዋል።
“ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ወደ አውሮጳ ትልካለች” ሲሉ ያልታሰበና አዲስ ሃሳብ ይፋ አድርገዋል። ቅዠት እንዳልሆነ ሲያስረዱ ግብጽ የዘረጋችው እስከ አውሮፓ የሚዘልቅ የሃይል ማስተላለፊያ መስመር መኖሩን አንስተው ይህን መስመር በመጠቀም ኢትዮጵያ የሃይል ሽያጭ እንደምታከናውን ገልጸዋል።
በጋዝ የተነሳ የሚፈጠረውን ብክለት ለመታደግ እየተደረገ ያለውን ትግል አንስተው ሃይል ወደ አውሮፓ እንደሚላክ ያስታወቁት አብይ አሕመድ ንግግራቸው በአውሮፓ ቆይታቸው ከመከሩባቸው ጉዳዮች አንዱን ያሳበቀ ሆኖ ተገኝቷል።
አጼ ሃይለስላሴን የፕሮጀክቱ ጠንሳሽ፣ አቶ መለስን አስጀማሪ፣ አቶ ሃይለማሪያም አጎልባች አድርገው በውድ ቃላት ያመስገኑት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በግድቡ ዙሪያ የተሳተፉትን አጉልተዋል።
ኤሌክትሪክ ማመንጨት የጀመረው የህዳሴው ግድብ እስካሁን 163 ቢሊዮን ብር ወጪ እንድተደረገበት የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አመልክቷል። ሃይል ማምረት የጀመረው አብይ በንደኛው ተርባይኑ ብቻ 375 ሜዋ ዋት ኃይል እንደሚያመነጭ ተመክቷል። ከአጠቃላይ ወጪው 16 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብሩ ከሕዝብ የተሰበሰበ መሆኑም ተግልጿል።
አነስተኛ ገቢ ካላቸው እናቶች አንስቶ አስከከ ፍተኛ ባለሃብቶች ድረስ ለግድቡ ግንባታ መዋጮና ቦንድ ግዢ ፈጽመዋል። በተለያዩ ዓለማት የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለግድቡ ግንባታ ድጋፍ እያደረጉ እንደሚገኙና ግድቡ ሁሉንም አንድ ያደረገ የህብረት ተምሳሌት እንደሆነ ተመልክቷል።
ዲያስፖራው በገንዘብ ብቻ ሳይሆን ሲያስፈልግ ድምጽ በመሆን ለግድቡ ግንባታ እውን መሆን የህዝብ ለህዝብ ዲፕሎማሲ ስራ መስራቱን አብይ አክብሮት ሰጥተውታል። ይህ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን አሻራ ያለበት ግድብ፣ ሙሉ ወጪው በኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ የተሸፈነ ሲሆን በቀጣይም ከውጭ እርዳታና ብድር ነፃ በሆነ መንገድ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ ምስጋና ያቀረቡላቸው መሪዎች አመራሮችና ሌሎች በግድቡ የተነሳ የተመሰገኑ አካላት
1. አፄ ሃይለ ስላሴ
2. የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ
3. የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ
4. አቶ አለማየሁ ተገኑ
5. ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ
6. ዶክተር ምህረት ደበበ
7. ኢንጂነር አዜብ አስናቀ
ኢንጂነር ስመኘው በቀለ
8. ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ
9. ዲክተር አብርሃም በላይ
10. አቶ ግርማ ብሩ
11. የህዳሴ ግድብ ሰራተኞች
12. የሃገር መከላከያ ሰራዊት
13. የዲያስፖራ አባላት
14. የፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት
15. የኢትዮጰያ ህዝብ
16. ፈጣሪያቸውን በስተመጨረሻ አመስግነዋል፡፡