በትግራይ ሰፍሮ በነበረው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ላይ ትህነግ ” መብረቃዊ” ሲል የሰየመውና መንግስት “ክህደት” ሲል ይፋ ያደርገው ወንጀል ሲፈጸጸም አዲስ አበባ ተቀምጠው የግንኙነት መስመር በመቆለፍና በማቋረጥ ከፍተኛ የሀገር ክህደት ወንጀል ተከሰው የፍርድ ሂደታቸውን እየተከታተሉ ያሉት የጦር መኮንን ሞቱ። ትህነግ ከመቀለ “ተገለዋል” ቢልም በስፍራው ነበሩ የተባሉት የቤተሰብ አካላት እስካሁን መረጃ አልሰጠም።
የቀድሞ የመከላከያ ሚኒስቴር የኮሚኒኬሽን ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ ኃላፊ ሜ/ጀ ገብረመድህን ፍቃዱ በእስር ላይ እያሉ ሰኞ ሚያዝያ 24/2014 ዓ.ም ሕይወታቸው ከቤተሰቦቻቸው ጋር እየተነጋገሩ ባለበት ወቅት በድንገት ራሳቸውን እንደሳቱ ተመልክቷል። የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን “ከረፋዱ ሦስት ሰዓት ተኩል አካባቢ በቤተሰብ ጥየቃ ሰዓት ባለቤታቸው እና ልጃቸው አስጠርተዋቸው እያወሩ እያለ በድንገት በመውደቃቸው ወዲያውኑ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ሕክምና ቦታ ቢወሰዱም ህይታቸው አልፏል” ሲል ሂደቱን በፌስ ቡክ አመልክቷል።
ማረሚያ ቤቱ ቤሰቦቻቸው ባሉበት ወይም እያዩ በድንገት መውደቃቸውንና ከቤተሰቦቻቸው ጋር በአንድነት ወደ ህክምና መሄዳቸውን ጠቅሶ ህልፈታቸውን ይፋ ማድረጉን ቢቢሲና ቪኦኤ ዘግበው የሟችን ባለቤት ማግኘት አለመቻላቸውን አመልክተዋል። ዘመድ ያነጋገረው ቢቢሲ “ጤነኛ መሆናቸውን አውቃለሁ” ማለቷን አመልክቷል።
የፌደራል ማረሚያ ቤት በቅጽል ስማቸው “ወዲ ነጮ” በሚል ስያሜ የሚጠሩት የቀድሞ የአጋዚ ሰራዊት ዋና አዛዥ ህልፈት ቤተስብ ባለበት በድንገት ወደቀው ወደ ሃኪም ቤት ቢወሰዱም ሊተርፉ እንዳልቻሉ መግለጹን ተከትሎ እስካሁን ቤተሰብ ያለው ነገር የለም። ማረሚያ ቤት የሰጠውን ቃል “ሃሰት ነው። እኛ በቦታው አልነበርንም። ስማችን ያለ አግባብ ተጠቅሷል…” በሚል ሲከሱም ሆነ መረጃውን ሲያስተባብሉ አልተደመጠም።
ዘርዝር መረጃ ለመስጠት ቤተሰብ ምን አልባትም በድንጋጤና በትኩስ ሃዘን ላይ መሆናቸው እንደ ምክንያት ቢቀርብም ትህነግ ሩቅ ሆኖ ባለው መልኩ የተፈጸመ ነገር ስለመኖሩ ይህ እስከታተመ ድረስ የተሰጠ መረጃ የለም።
ትህነግ ባወጣው መግለጫ የቀድሞው የትህነግ ታማኝ የአጋዚ ሰራዊት አዛዥ የሜጀር ጀነራል ገብረመድህን ሕይወት በማለፍ ሐዘን እንደተሰማው አስታውሶ፣ ለቤተሰቦቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናት ይሁን ብሏል። አያይዞም የፌዴራል መንግሥት ወንጅሎ ጉዳዩን ማንነትን ላይ ያነጣጠረ ነው” ብሎታል። ሲቀጥልም “የህልፈታቸው መንስኤ በገለልተኛ አካል ይጣራልኝ” ብሏል። ማረሚያ ቤቱ የከፍተኛ መኮንኑ ህልፈት ምክንያቱ በሃኪም እየተጣራ መሆኑንን አመልክቷል።
የሜጄር ጄኔራሉን ሕልፈተ ሕይወት በተመለከተ ከቤተሰቦቻቸውና ከጠበቃቸው መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት ሊሳካለት እንዳልቻለ ያስታወቀው ቪኦኤ. በ97 ምርጫ ወቅት በርካታ ሰላማዊ ዜጎችን ጭንቅላት እየመታ ሲደፋ የነበረው አጋዚ ሰራዊት አዛዥ የነበሩት ሜጀር ጀነራል ገ/መድህን ፍቃዱ፣ የመከላከያ ሚኒስቴር የኮሚኒኬሽን ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ ኃላፊ በነበሩበት ወቅት፣ ጥቅምት 24/2013 ዓ/ም መከላከያ ሰራዊቱ ከሰሜን ዕዝ ጋር የነበረውን የሬዲዮ ግንኙነትን በማቋረጥ እንዲሁም የሬዲዮ መገናኛ መሳሪያ ለህወሓት ወታደራዊ ቡድን አሳልፈው ሰጥተዋል በሚል በዓቃቤ-ህግ የቀረበባቸውን ከፍተኛ የሀገር ክህደት ክስ ሂደት በመከታተል ላይ ነበሩ ሲል የክሳቸውን ጭብጥ አስታውሷል።
በቀድሞ የመከላከያ መኮንኖች የክስ መዝገብ ላይ 1ኛ ተከሳሽ የሆኑት ሜጀር ጀኔራሉ ሕይወታቸው በድንገት ማለፉን ተከትሎ በሌሎች ተከሳሾች ላይ የዐቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱን የፍትህ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ የፀረሽብርና የህገ መንግስታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ቀሪ የዐቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለዛሬ ተይዞ በነበረው ተለዋጭ ቀጠሮ፣ 7ኛ እና 15ኛ የዐቃቤ ህግ ምስክሮች ቃላቸውን ለመስጠት ተገኝተው ቃለ መሀላ ፈፅመው ነበረ ብሏል ሚኒስቴሩ በፌስቡክ ገጹ ባወጣው መረጃ፡፡
ይሁንና የ1ኛተከሳሽ ድንገተኛ ሕልፈተ ሕይወትን ተከትሎም በክስ መዝገቡ የተካተቱ ሌሎች ተከሳሾችና የተከሳሽ ጠበቃ የሟች አስከሬን ባልተቀበረበት ሁኔታ ዐቃቤ ህግ የሚያሰማብንን ምስክሮች ለመከላከል የሚያስችል የስነ ልቦና ዝግጅት ስለሌለን ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠን ሚል ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቶ፣ ቀሪ የዐቃቤ ህግ ምስከሮችን ለመስማት ከግንቦት 08 እስከ ግንቦት 12/2014 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱን ገልጿል፡፡
በመዝገቡ የተካተቱት ሌሎች ተከሳሾች አጃቢ ተመድቦልን በቀበር ሥነ ስርዓቱ ላይ እንድንገኝ ለማረሚያ ቤት ደብዳቤ ይፃፍልን ሲሉም ፍርድ ቤቱን የጠየቁ ሲሆን፣ ዐቤ ሕግ በበኩሉ ሁኔታው “ያልተለመደና ለደህንነት አስጊ” መሆኑን ገልፆ ማረሚያ ቤትም ጉዳዩን ቢመለከተው መልካም ነው ሲል ማሳወቁ ተመላክቷል።
በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ የፀረ ሽብርና የህገ መንግስታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት በፅ/ቤት ከተወያየ በኋላ በፅ/ቤት በኩል ትዕዛዝ እንደሚሰጥበት ገልጾ፣ ሌሎቹ ተከሳሾች በቀብሩ ላይ ለመገኘት ያላቸውን ፍላጎት በፅሑፍ እንዲያቀርቡና መወሰኑንም ነው ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ አመልክቷል፡፡