ከአራት ቀናት በፊት “አቶ” በሚባለው ቦታ ወደ ሶማሌ ክልል አፍዴር ዞን የገባው አሸባሪው የአልሸባብ ታጣቂ ቡድን “ሁልሁል” በሚባል ንዑስ ቀበሌ ከተከበበ በኋላ ሙሉ ለሙሉ ለወሬ ነጋሪ ሳይተርፍ መደምሰሱን የሶማሌ ክልል ፀጥታ ምክር ቤት አስታውቋል።
የሶማሌ ክልል ፀጥታ ምክር ቤት ጉዳዩን አስመልክቶ መግለጫ አውጥቷል።
ምክርቤቱ በመግለጫው ከአራት ቀናት በፊት “አቶ” በሚባለው ቦታ ወደ ሶማሌ ክልል አፍዴር ዞን የገባው አሸባሪው የአልሸባብ ታጣቂ ቡድን “ሁልሁል” በሚባል ንዑስ ቀበሌ ከተከበበ በኋላ ሙሉ ለሙሉ ለወሬ ነጋሪ ሳይተርፍ ተደምስሷል ብሏል።
ቡድኑ በኤልከሬ ወረዳ አልፎ ወደ ኦሮሚያ ክልል በመግባት ከሸኔ ሽብርተኛ ቡድን ጋር ለመገናኘት አልሞ ነበር ብሏል የጸጥታ ምክር ቤቱ።
አሸባሪው ቡድን ወደ አሰበው ቦታ ሳይደርስ የያዛቸው 13 ተሽከርካሪዎች የተቃጠሉ ሲሆን ይዞት የገባው ትጥቅና ስንቅም ተማርኳል ብሏል።
ለሶስት ቀን በተካሄደው ኦፕሬሽንም ከ100 በላይ የአሸባሪው ቡድን አባላት መገደላቸውን ምክርቤቱ አስታውቋል።
ባለፉት ሦስት ቀናት ለኦፕሬሽኑ መሳካት የሶማሌ ክልል ሕዝብ እንደ ወትሮው ሁሉ በርካታ የቁም እንስሳቶችን፣ መጠጦችን ፣ ምግቦችን፣ አልሰባሳት እንዲሁም ደም በመለገስ ከልዩ ኅይሉ ጎን መቆሙን ምክር ቤቱ ገልጿል። በመኾኑም የክልሉ ሕዝብ ላደረገው ድጋፍና እገዛ የሶማሌ ክልል የፀጥታ ምክር ቤት ላቅ ያለ ምስጋና አቅርቧል።
የኦፕሬሽኑን ስኬት በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎች ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረጉ የፀጥታ ምክር ቤቱ አስታውቋል። መረጃው የሶማሌ ክልል ኮምዩኒኬሽን ነው። (አሚኮ)