የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ፤ ዛሬ ከሰዓት ባወጣው መግለጫ ፤ በታዋቂው እና ተወዳጁ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) ህልፈት ሀዘን እንደተሰማው ገልጿል።
በመግለጫው ፤ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) በህይወት በነበረበት ወቅት የዓይን ባንኩ አምባሳደር እንደነበርና ህልፈት በሚያጋጥምበት ጊዜ የዓይን ብሌኑን ለመለገስ ቃል ገብቶ እንደነበር ጠቁሟል።
የኢትዮጵያ ዓይን ባንክ ፤ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) ” ስሙንም ብርሃኑንም ከመቃብር በላይ ህያው አድርጎ ያለፈ መልካም አርቲስት ” ሲል ጠርቶታል።
አርቲስቱ በገባው ቃል መሰረትም በቤተሰቦቹ እና በጓደኞቹ ቀና ትብብር ቃሉ ተፈፃሚ መሆኑን ባንኩ አሳውቋል።
በሌላ በኩል ፤ የአርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ)ን ስርዓተ ቀብር ለማስፈፀም ኮሚቴ ተዋቅሮ እየሰራ ሲሆን ይኸው ኮሚቴ የአርቲስቱ ስርዓተ ቀብር ነገ ታህሳስ 3 ቀን 2015 ዓ/ም ከቀኑ 9:00 ሰዓት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ወዳጅ ዘመዶቹ በተገኙበት እንደሚፈፀም ገልጻል።
ከስርዓተ ቀብሩ ቀደም ብሎ ከጠዋቱ 5:00 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮዽያ ብሔራዊ ቴአትር ሽኝት ይደረጋልም ተብሏል።
(ቲክቫህ ኢትዮጵያ)