የ12 ዓመት ታዳጊ የቤት ሰራተኛቸውን ገድለው በድብቅ ሊቀብሩ ሲሉ የተያዙ ባለትዳሮች በ25 ዓመት ጽኑ እስራት ተቀጡ

በአዲስ አበባ ከተማ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ማንጎ ሰፈር ተብሎ በሚጠራው አከባቢ የ12 ዓመት ታዳጊ የቤት ሰራተኛቸውን ገድለው በድብቅ ሊቀብሩ ሲሉ የተያዙ ባለትዳሮች በ25 ዓመት ጽኑ እስራት መቀጣታቸውን ፍትሕ ሚኒስቴር አሰታወቀ።

በፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ በሴቶችና ህፃናት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎች ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ህግ ምርመራውን በመምራት  ክስ መስርቶ ክርክር በማድረግ አጥፊዎቹ እንዲቀጡ ማደረጉ ተገልጿል።

የዐቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፤ 1ኛ ልጃለም ጌታቸው ታዬ እና 2ኛ ቆንጂት ሙለታ በቀለ የተባሉት ባለትዳር ተከሳሾች በዋና ወንጀል አድራጊነት በአዲስ አበባ ከተማ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ማንጎ ሰፈር ተብሎ በሚጠራው አከባቢ በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ ከታህሳስ 17/2014 እስከ ጥር 17/2014  ባለ ጊዜ ሟች አስቴር ነገሰ የተባለች የ12 ዓመት ታዳጊን ተከሳሾቹ በተደጋጋሚ በተለያየ ጊዜ በፍልጥ እንጨት፣ በእርግጫ፤ በሞባልይ ቻርጀር ገመድ ጀርባዋን፣ ወገቧን እና እግሯን ደጋግመው በመደብደብ፤  ከገደሏት በኋላ የሟችን አስከሬን በሳጥን በማድረግ በድብቅ ለመቅበር ሲሰናዱ ተይዘዋል።

ጉዳዩ በምርመራ ሲጣራ በሟች ላይ በርካታ የቆዳ መጋጋጥ እና የመበለዝ፣ ከአንገትዋ የፊተኛው ክፍል አንስቶ ወደ ቀኝ እና ግራ ትከሻዋ የተሰራጨ” የመበለዝ፣ በደረትዋ የላይኛው ፊተኛና ጎን 1/3 ክፍል የመበለዝ፣ በቀኝና በግራ መቀመጫዋ ጭን የላይኛው ኋለኛ ክፍል እና በጀርባዋ የታችኛው ክፍል ላይ በርካታ የቆየ የቆዳ መጋጥ፣ በራስ ቅልዋ ፊተኛ መካከለኛ ክፍል የመበለዝ፣ በእጅ እና እግሮቿ ላይ ወደ ውስጥ ደም የመፍሰስ፣ የመሰራጨትና የመበለዝ ጉዳት ምክንያት ህይወቷ ማለፉ በማስረጃ በመረጋገጡ  ዐቃቤ ሕግ በከባድ የሰው መግደል ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዉ ክርክር ሲደረግ ቆይቷል፡፡

ተከሳሾችም “ድርጊቱን አልፈፀምንም ጥፋተኛም አይደለንም”  ብለው የተከራከሩ ሲሆን፣  ዐቃቤ ሕግ በማስረጃ አስደግፎ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው በበቂ ሁኔታ ያረጋገጠ በመሆኑ እና ተከሳሾችም ይህን የዐቃቤ ሕግ ክስ እና የቀረበባቸውን ማስረጃ እንዲያሰተባብሉ በተሰጠ ብይን መሰረት 2 የመከላከያ ምስክር አቅርበው ያሰሙ ቢሆንም የቀረበባቸውን ክስ እና ማስረጃ ያላስተባበሉ በመሆኑ ፍርድ ቤቱ በዐቃቤ ህግ በቀረበባቸው ክስ እና ማስረጃ መሰረት ጥፋተኛ ናቸዉ ብሏል።

See also  ለ68 ዓመታት በሥራ ላይ የቆየውን የዳኝነት ክፍያ አገልግሎትን ለማሻሻል በቀረበ ረቂቅ ላይ ውይይት ተካሄደ

በዚህም መሰረት ክርክሩን የመራው በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ ሰው ግድያና ከባድ ውንብድና ወንጀል ችሎትም በቅጣት አወሳሰን መመሪያ 02/2006 መሰረት የወንጀል  ደረጃውን  2 እርከን 39 ስር በማድረግ መነሻ ቅጣት በመያዝ፣ ሁለቱም ተከሳሾች ሪከርድ የሌለባቸው በመሆኑና የቤተሰብ አስተዳዳሪ በመሆናቸው 2 የቅጣት ማቅለያ ተይዞላቸው በእርከን 37 ስር ተከሳሾችን ያርማል ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችን ያስተምራል ያለውን እያንዳንዳቸው በ25 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ እና እንዲሁም ተከሳሾች ለ5 ዓመት ከመብቶቻቸው እንዲሻሩ ሲል መወሰኑን አዲስ ማለዳ ከፍትህ ሚኒስቴር ያገኘችው መረጃ አመላክቷል፡፡

Leave a Reply