ሰሞኑን እየታየ ያለው ጉንፋን መሰል ወረርሽኝ ኮቪድ የመሆን እድሉ ከፍተኛ ነው

ህብረተሰቡ የእጅ ንፅህናን መጠበቅን ጨምሮ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ማስክ መጠቀም እና ክትባት በመከተብ እንዲሁም ሰው ከተሰበሰበበት በመራቅ ራሱን ከወረርሽኙ መከላከል

ሰሞኑን በብዛት እየታየ ያለው ጉንፏን መሰል ወረርሽኝ በአብዛኛው የኮቪድ 19 ምልክት እያሳየ መሆኑን የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩቱ የድንገተኛ አደጋ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ሻምበል ሀቤቤ በተለይ ለኢቢሲ ሳይበር ገልጸዋል።

ወረርሽኙ ኮቪድ 19ን ጨምሮ የብዙ መተንፈሻ አካላት በሽታዎች ምልክት ሊሆን እንደሚችል ጠቅሰው ኮቪድ የመሆን እድሉ ከፍተኛ መሆኑን አስተባባሪው አብራርተዋል።

በዚህ ወቅት ኮቪድ 19 የሚገኝባቸው ሰዎች ቁጥር ወደ 6 በመቶ እየጨመረ መምጣቱንም አቶ ሻምበል ተናግረዋል።

በዚህ ሳምንት ከተመረመሩ በርካታ ሰዎች መካከል ወደ 860 በላይ የሚሆኑት ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ከኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በመሆኑም እድሜያቸው ከ12 ዓመት በላይ የሆኑ ህጻናትን ጨምሮ ማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል አሁን እየቀረበ ባለው ፈጣን የ15 ደቂቃ የምርመራ ውጤት መሰረት በአቅራቢያው በሚገኝ ጤና ጣቢያ በመመርመር ውጤቱን አውቆ ተገቢውን ህክምና ማግኘት እንደሚገባ ተናግረዋል።

በተጨማሪም ህብረተሰቡ የእጅ ንፅህናን መጠበቅን ጨምሮ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ማስክ መጠቀም እና ክትባት በመከተብ እንዲሁም ሰው ከተሰበሰበበት በመራቅ ራሱን ከወረርሽኙ መከላከል እንዳለበት አቶ ሻምበል አሳስበዋል።
ዘገባው የኢቢሲ ነው።

See also  የነዳጅ ዕጥረት ያጋጠመ ለማስመሰል በሚሞክሩ ማደያዎች ላይ እርምጃ ይወሰዳል

Leave a Reply