ኢራን በስለላ የከሰሰቻቸውን የቀድሞ ምክትል የመከላከያ ሚኒስትሯን በሞት ቀጣች

ኢራን ውስጥ የሞት ፍርድ የተበየነባቸው የብሪታኒያ እና የኢራን ጥምር ዜግነት የነበራቸው አሊሬዛ አክባሪ መገደላቸውን የኢራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

ባለፈው ረቡዕ የአክባሪ ቤተሰቦች “ለመጨረሻ ጉብኝት” ወደ እስር ቤት ሄደው እንዲጠይቋቸው ተነግሯቸው እንደነበር እና አክባሪ ለብቻቸው ታስረው እንደቆዩ ሚስታቸው ገልጸው ነበር።

የቀድሞው የኢራን ምክትል የመከላከያ ሚኒስትር አሊሬዛ አክባሪ የታሰሩት ከሦስት ዓመት በፊት ነበር። እሳቸው ቢያስተባብሉም ለዩናይትድ ኪንግደም በመሰለል ተከሰው ሞት ተፈርዶባቸዋል።

ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ኢራን በአሊሬዛ አክባሪ ላይ ልትፈጽም ያቀደችውን የሞት ፍርድ በመተው በአስቸኳይ ግለሰቡን እንድትለቅ ስትጠይቅ ቆይታለች።

አርብ ዕለት የዩኬ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ጄምስ ክሌቨርሊ “ኢራን ጭካኔ በተሞላበት የግድያ ማስፈራሪያዋ መቀጠል የለባትም” ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር።

ባለፈው ረቡዕ ክሌቨርሊ በትዊተር ገጻቸው ላይ እንዳሉት “ይህ ፖለቲካዊ ትርፍ ለማግኘት የሚወሰድ ኋላቀር የጭካኔ ቅጣት ነው፤ ኢራን ሰብአዊ መብት ግድ አይሰጣትም” ሲሉ ጠንከር ያለ ትችት ሰንዝረው ነበር።
ቢቢሲ

See also  ውድመትና ዘረፋ የደረሰበት የአቡነ ዮሴፍ ተራራ የሕዋ ምርምር ጣቢያን መልሶ ለመገንባት እየተሰራ ነው

Leave a Reply