Site icon ETHIOREVIEW

ከአርሰናልና ከሲቲ የተሻለ ዕድል ለማን? አሃዛዊ መረጃዎች ወዴት ያደላሉ

ከሚታወቅበት ጥለዛ በየጊዜው መሻሻል እያሳየ ውብ ኳስ ባምስኮምኮም ላይ ያለው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ልብ አንጠላጥይ ሆኗል። የዘመኑ የዋንጫ ደመራ ወደ የትኛው አቅጣጫ ይወዳቃል የሚለው የሁሉም ጥያቄ ሆኗል። የጋርዲዮላ ረዳት የነበረው አርቴታ ዋንጫ ካነሳ ጋርዲዮላ ምን አልባትም በአርቴታ ድጋፍ ብዙ ስራዎችን ፈጽሟል የሚል አሳብ ሊነሳ እንደሚችል የሚገልጹም አሉ።

አርሰናል ጥሩ አስራ አንድ እንጂ በተጠባባቂ ወንበር ላይ ተመጣጣኝ ችሎታ ያላቸው ተጫዋቾች ስለሌሉት እክል ቢገጥመውስ ሲሉ ስጋታቸውን የሚገልጹ አሉ። የጫዋች ጉዳት ካላጋጠመው በያዘው መንገድ ሊያቀና እንደሚችል የሚናገሩ ቢበረክቱም ሲቲ ሊቀመስ እንደማይችል፣ ቀሪ ጨዋታቸውን በማስላት ግምታቸውን ከወዲሁ ያስቀመጡ አሉ።

አርሰናል፤ ባለፈው ሰንበት ክሪስታል ፓላስን በኤሜሬትስ ስታድየም 4 ለ 1 በመርታት መሪነቱን አጠናክሯል። የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ዋንጫን ካነሱ አስራ ዘጠኝ ዓመት ያስቆጠሩት አርሰናሎች የዋንጫ ረሃባቸውን በቃ ለማለት አስር ጨዋታ ይቀራቸዋል።

ተቀናቃኙ ማንቸስተር ሲቲ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀየረው ከአርሰናል በስምንት ነጥብ ዝቅ ብሎ ተቀምጧል። ሲቲ በኤፍኤ ዋንጫ እና በቻምፒዮንስ ሊግ እየተሳተፈ የሚገኝም ቡድን ነው።

ማንቸስተር ሲቲ በኤቲሃድ ስታድየም ረቡዕ ሚያዚያ 16/2015 ዓ.ም. አርሰናልን ያስተናግዳል። ይህ ጨዋታ ዋንጫውን ማን ያነሳው ይሆን? ለሚለው ግምት ምልክት የሚሰጥ የሚጠበቅ ፍልሚያ ነው። ከዛም ከሁለቱ ቡድኖች የተሻለ ቀላል ቀሪ ጨዋታ ያለው ማነው? የሚለው ስሌት ይነሳል።

ቀሪ ጨዋታዎች

አርሰናል ከሲቲ ጋር ሲነፃፀር ቀለል ያሉ ቀሪ ጨዋታዎች እንዳሉት ይታመናል። ሲቲ የቀሩትን ሁሉንም ጨዋታዎች ያሸንፋል ብለን ብንገምት፤ አርሰናል ከቀሪዎቹ 10 ጨዋታዎች 26 ነጥብ መሰብሰብ አለበት።

አርሰናል የመጨረሻ ጨዋታውን ከዎልቭስ ጋር በሜዳው ያደርጋል።

የፔፕ ጉዋርዲዮላ ቡድን 11 ጨዋታዎች ይቀሩታል። አልፎም በቻምፒዮንስ ሊግ ከባየርን ሙኒክ ሁለት ጊዜ፤ በኤፍ ኤ ዋንጫ ደግሞ ከሼፊልድ ዩናይትድ ይገናኛል።

ሲቲ፤ ሁሉንም ጨዋታዎች ቢረታ በአውሮፓውያኑ ሰኔ 3 የኤፍኤ ዋንጫ ፍፃሜ፤ በሳምንቱ ሰኔ 10 ደግሞ በቻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ ኢስታንቡል ላይ ይፋለማል።

የመረጃ ቋቱ ድርጅት ኒልሰንስ ግሬስኖትስ የአርሰናል እና ሲቲን ቀሪ ጨዋታዎች እንዲሁም የማሸነፍ ዕድል ተምኖ ይህን ብሏል።

በድርጅቱ ስሌት መሠረት የማይክል አርቴታ አርሰናል ፕሪሚዬር ሊጉን ዋንጫ የማንሳት ዕድላቸው 53 በመቶ ሲሆን፤ ሲቲ ደግሞ 47 በመቶ ነው።

“ምንም እንኳ አርሰናል ሊጉን በስምንት ነጥብ ልዩነት እየመራ ቢሆንም፣ ዋንጫውን የማንሳት ዕድሉ 50/50 ነው። ሲቲ አንድ ቀሪ ጨዋታ አለው። አልፎም አርሰናል ከስድስቱ ኃያላን ቡድኖች ከሦስቱ (ሲቲ፣ ኒውካስትል እና ሊቨርፑል) ጋር ከሜዳው ውጭ ይጫወታል” ይላል የድርጅቱ የስፖርት ተንታኝ ሳይመን ግሊቭ።

“ሲቲ በጣም ሊከብደው የሚችለው ፍልሚያ በሚቀጥለው ወር ከሜዳው ውጭ ከብራይተን ጋር የሚያደርገው ነው።”

ተንታኙ እንደሚለው ድርጅቱ በሠራው የማሸነፍ ስሌት መሠረት በውድድር ዘመኑ መጨረሻ አርሰናል 87 ነጥብ ይኖረዋል፤ ሲቲ ደግሞ 86።

ሳይመን አክሎ በእያንዳንዱ ጨዋታ ሁለቱ ቡድኖች ያላቸውን የማሸነፍ፣ የመሸነፍ አሊያም አቻ የመውጣት ዕድል ቢሰላ ደግሞ ሁለቱም ቡድኖች በ88 ነጥብ የውድድር ዘመኑን ይጨርሳሉ።

ረቡዕ ሚያዚያ 16 በኤቲሃድ ስታድየም ማንቸስተር ሲቲ ከአርሰናል የሚያደርጉት ፍልሚያ ዋንጫው ወደየት እንደሚሄድ የሚያሳይ ሊሆን ይችላል።

ማንቸስተር ሲቲ በዚህ ጨዋታ የተሰጠው የማሸነፍ ዕድል 66 በመቶ ነው። ነገር ግን አርሰናል አቻ ቢወጣ፤ አሊያም ቢያሸንፍ ሁኔታዎች ይቀያራሉ።

ታሪክ ለአርሰናል ያደላል

አርሰናል ከ19 ዓመት በኋላ የፕሪሚዬር ሊጉን ዋንጫ ያነሳ ይሆን ወይ ብለው እንቅልፍ ያጡ ‘ጋነርስ’ ታሪክን ተመልክተው ሊረጋጉ ይችላሉ።

ኦፕታ የተሰኘው መረጃ ተንታኝ ድርጅት እንደሚለው በፕሪሚዬር ሊግ ታሪክ ሦስት ቡድኖች ብቻ ናቸው በስምንት ነጥብ ልዩነት እየመሩ ዋንጫ ሳያነሱ የቀየሩት።

በአውሮፓውያኑ 1997/98 ማንቸስተር ዩናይትድ በዘጠኝ ልዩነት ነጥብ ሊጉን እየመራ ቢቆይም ሦስት ቀሪ ጨዋታዎች የነበሩት አርሰናል ከኋላ ተነስቶ ሊጉን መብላቱ አይዘነጋም።

ከአምስት ዓመታት በኋላ ማንቸስተር ዩናይትድ፤ ሊጉን በስምንት ነጥብ ልዩነት እየመራ የነበረውን አርሰናል በመገልበጥ በቀሉን አጣጥሟል።

በ2011/12 የውድድር ዘመን ደግሞ ዩናይትድ የነበረውን የመሪነት ነጥብ ሳይጠቀምበት ማንቸስተር ሲቲ ከኋላ መጥተው በታሪካዊው የአጉዌሮ ጎል አሸንፈዋል።

ታሪክን ብንመለከት 30 ጨዋታ ተጫውተው ከ69 በላይ ነጥብ ካከማቹ ክለቦች መካከል አንድ ቡድን ብቻ ነው ዋንጫውን ማንሳት ያልቻለው። እሱም የ2018/19 ሊቨርፑል።

የቀድሞው የአርናል ተከላካይ ማርኢን ኬዎን የዋንጫ ፉክክሩ በጣም አጓጊ እንሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም። ቢሆንም አርሰናል የሚቻላቸውን ሁሉ እያደረጉ ነው ይላል።

“አሁንም ብዙ ሥራ ይቀራል። ቢሆንም እዚህ ለመድረስ የሚቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል። ሲቲ የተጣበበ ጊዜ ነው ያለው። በቻምፒዮንስ ሊግ እና በኤፍኤ ዋንጫ እየተፎካከረ ሳለ ነው ከአርሰናል ጋር የሚገዳደረው።” የቀድሞው የዌልስ ተከላካይ ዳኒ ጋቢደን ደግሞ የዘንድሮው አርሰናል በጣም የተመጣጠነ ነው ይላል።

ምንም እንኳ አርሰናል ትላልቅ ከሚባሉ ቡድኖች ጋር ጨዋታዎች ቢቀሩትም ቡድኑ አሁን ያለበት አቋም ለየት ያለው ነው ባይ ነው። “የዘንድሮው የዋንጫ ፉክክር እስከመጨረሻው ይቀጥላል።”

Exit mobile version