Site icon ETHIOREVIEW

የኢትዮጵያውያንና የዳያስፖራ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፎረም በዋሽንግተን ዲሲ ተካሄደ

በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የተሰማሩ ባለሃብቶች እና ነዋሪነታቸውን በአሜሪካ ያደረጉ ኢትዮጵያውያን የዳያስፖራ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፎረም ሚያዚያ 5 ቀን 2015 ዓ.ም በዋሽንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ተካሂዷል።

በፎረሙ መክፈቻ ላይ የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ እንደገለጹት ኢትዮጵያ ያላትን እምቅ የኢንቨስትመንት አማራጮች በመጠቀም በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ወደ ተለያዩ የኢንስትመንት ዘርፎች ተሰማርተው እንዲሰሩ መንግስት እስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል።

በአገራችን የተጀመረውን ዘላቂ ሰላም የማስፈን ሂደት እንዳይቀለበስ በሙሉ ቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።

በትግበራ ላይ የሚገኘው የአገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የግሉ ዘርፍ ጉልህ ሚና እዲጫዎት የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው መንግስት አስቻይ የፖሊሲ ማዕቅፎችን በመዘርጋትና ውስን በሆኑ የኢንቨስትመንት መስኮች ብቻ ይሳተፋል።

በተለይም አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ ዓለማት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራ ባለሃብቶች ያካበቱትን ልምድ እና እውቀት ወደ አገራቸው ይዘው በመግባት በግል እና ከአገር ውስጥ ባለሃብቶች ጋር በመሆን እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።

ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት ዘጠና በመቶ የሚሆነው ባንኮች የሚሰጡት ብድር ለግል ዘርፉ ተደራሽ እየተደረገ መሆኑን ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አቶ ማሞ ምህረቱ አስታውቀዋል።

በአሜሪካ የኢፌዴሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣነ አምባሳደር ስለሺ በቀለ ሲናገሩ “በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልድ ኢትዮጵያውያን በሀገር ልማት፣ በገጽታ ግንባታ፣ በንድግና ኢንቨስትመንት፣ በትህምርት፣ በጤና እና በሌሎች ዘርፎች የሚኖራቸውን ተሳትፎ ለማሳደግና ከአገራቸው ኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ትስስር ለማጠናከር ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው”፡፡

በግልም ሆነ በጋራ በመሆን በኢትዮጵያ በቢዝነስና ኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፍላጎት ላላቸው ባለሃብቶች ኤምባሲው በአገር ቤት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና ከሌሎችም ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመቀናጀት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ክብርት ሌሊሴ ነሜ በበኩላቸው አገራችን ለኢንቨስትሮች ምቹ እንደትሆን ተግባራዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎች እንደተሰሩ ተናግረዋል።

ባለሃብቶች ከገበያ ዳሰሳ ጥናት፣ ከፈቃድ ማውጣት፣ በስራ ላይ እና ከዛም አልፎ የሚገጥሟቸውን የቢሮክራሲ እና ተያያዥ መሰናክሎች በፍጥነት እልባት እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ለአብነት ጠቅሰዋል።

እንደ ኮሚሽነር ሌሊሴ ገለጻ የተለያዩ አገራት ባለሃብቶችን ወደ አገራችን ለመሳብ እና መረጃዎችን በተገቢው መንገድ ለማሰራጨት ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ ሚሲዮኖች ጋር በቅርበት እየሰራ ይገኛል።

ዝግጅቱ ከኤምባሲው ጋር ያስተባበሩ የዋፋ ማርኬቲንግ እና ፕሮሞሽን ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ፋንታዬ ጌታነህ እንዳሉት መድረኩ ኢትዮጵያውያን ባለሃብቶች ከዳያስፖራ አጋሮች ጋር ትስስር እንዲፈጥሩ አሰችሏል።

(ኢ ፕ ድ)

Exit mobile version