Site icon ETHIOREVIEW

ኢዜማ በአማራ ክልል ለተፈጠረው ችግር መፍትሄ ያለውን ምክረ አሳብ አመላከተ

በአማራ ክልል የተከሰተውን የፖለቲካ እና የፀጥታ ቀውስ ተከትሎ ከክልሉ በቀረበለት ጥያቄ መሰረት የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሐምሌ 28/2015 ዓ.ም. በክልሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ ውሳኔ ማስተላለፉ ይታወሳል።…..ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን የመፍትሔ አቅጣጫዎች መቀየስ እንደሚገባ እናምናለን ።

1) ክልሉን ለዚህ ደረጃ እንዲበቃ ያደረጉት አንድም ሃላፊነቱን ካለመወጣቱ የመነጨ መሆኑን ተገንዝቦ ለእያንዳንዶቹ ጉዳዮች በግልጽ እራሱን ተጠያቂ በማድረግ ማህበረሰቡን በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቅ

2) መንግሥት የሚዘውራቸው የህዝብ መገናኛ ብዙሃን፣ ፋና እና ዋልታ ሚዲያዎች መንግሥት በጉዳዩ ላይ አንዳች ነገር ሲተነፍስ ብቻ ተቀብለው የገደል ማሚቱ ከመሆን ባለፈ የችግሩን ምንጭን ከመሰረቱ በማሳየት በደሎች ተዳፍነው እንዳይቀሩ የመስራት ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ ከአድር ባይ ማንነት ተላቀው ውግንናቸውን ለሙያቸው እና ለህዝብ እንዲያደርጉ ከዚህ ቀደም እንደጠየቅነው ሁሉ አሁንም ለማስታወስ እንወዳለን።

3) መንግሥት ወቅታዊ ነባራዊ ሁኔታዎችን አገናዝቦ ሀገርአቀፍ የዘላቂ ሰላም ፍኖተ-ካርታ በማዘጋጀት መዋቅራዊ እና ሕጋዊ የሰላም ግንባታ በአስቸኳይ ሊተገብር ይገባል።

4) የፌደራል እና የክልል መንግሥታት ከጊዜያዊ የሥልጣን ፍላጎት በላይ የሕዝብን ጥቅም በማስቀደም ላለፉት አምሥት ዓመታት የፈጸሟቸውን የፖለቲካ ምህዳሩን የሚያጠብቡ ተግባራት በመፈተሽ የሀገሪቱን የፖለቲካ ብዝኃነት የሚያንፀባርቅ የአሳታፊነት መርህን ተግባራዊ ማድረግ አለባቸው።

5) ላለፉት አራት ዓመታት ያለማቋረጥ ስንወተውት እንደነበረው፤ መንግሥት የዜጎችን ሰላም እና ደህንነት ለማስከበር ቁርጠኛ አለመሆኑ በተለይም ማንነት መሠረት አድርገው የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ማስቆም አለመቻሉ አሁን ላይ ለሚስተዋሉ ቀውሶች ምንጭ መሆናቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል። ይኽንንም መሠረት በማድረግ መንግሥት ቁርጠኛ የሰላምና ደኅንነት ማስከበር ሥራ በሀገርአቀፍ ደረጃ በአስቸኳይ ማከናወን ይጠበቅበታል።

6) መንግሥት የራሱን ድምፅ ብቻ ደጋግሞ ከማዳመጥ ወጥቶ በኹሉም አካባቢዎች ማኅበረሰቡ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማኅበራት፣ ምሁራን፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና ሌሎችም የሕብረተሰብ ክፍሎች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች ለማዳመጥ የሚያስችል መድረክ ማመቻቸት ይጠበቅበታል።

7) የመንግሥት ኃላፊዎች ቁርሾዎችን ከሚያባብሱ ውሳኔዎች፣ ተግባራት፣ ንግግሮች/ጽሑፎች መታቀብ ይገባቸዋል።

8) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈፀም በሚል በሃገሪቱ ህግ እና ሃገሪቱ ተቀብላ ካፀደቀቻቸው ድንጋጌዎች ውጪ መብቶችን በመጣስ የተለያዩ የገፍ እሥሮችን እና መሰል ተግባራትን በመፈጸም ያለውን ሁኔታ ከማባባስ እንዲቆጠብ እንዲሁም ገለልተኛ የሆኑ እንደ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ያሉ ተቋማት የሚሰጡትን ሃሳቦች ተግባራዊ እንዲያደርግ

እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩ የረዥም እና የአጭር ጊዜ መፍትሔዎች በተናጥል ሳይኾን በጣምራ መተግበር አለመቻል ሀገር እና ሕዝብን ለተራዘመ መከራ መዳረግ መኾኑ ሊሰመርበት ይገባል።
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
ነሐሴ 02/2015 ዓ.ም.


Exit mobile version