Site icon ETHIOREVIEW

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፓርላማ ይሁንታ አገኘ፤ ከአማራ ክልል 125 የብልጽግና ተወካዮች ሶስት ብቻ ተቃውመዋል

– በአማራ ክልል “ሁሉንም ኃይሎች” ያካተተ “ጊዜያዊ አስተዳደር” እንዲቋቋም አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጠየቁ

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአንድ ሳምንት በፊት የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በአብላጫ ድምጽ አጸደቀ። አዋጁን 16 የፓርላማ አባላት ሲቃወሙት፤ 12 አባላት ደግሞ ድምጽ ከመስጠት ታቅበዋል።

የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሐምሌ 28፤ 2015 በሙሉ ድምጽ ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት፤ በአማራ ክልል እና “እንዳስፈላጊነቱ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች” ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማጽደቅ በዛሬው ዕለት የተገኙት የፓርላማ አባላት ብዛት 360 ነበር። በዛሬው አስቸኳይ የፓርላማ ስብሰባ ላይ አስተያየታቸውን ከሰጡ አስራ ስድስት የፓርላማ አባላት መካከል፤ የአዋጁ መጽደቅ የሚቃወም ሀሳብ የሰነዘሩት አራቱ ብቻ ናቸው።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የተቃወሙት ሁሉም የፓርላማ አባላት ከአማራ ክልል ተመርጠው የተወካዮች ምክር ቤትን የተቀላቀሉ ናቸው። የገዢው የብልጽግና ፓርቲ ተመራጮች ከሆኑ ሶስት የፓርላማ አባላት በተጨማሪ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ተወካዩ አቶ አበባው ደሳለው ተቃውሟቸውን በዛሬው ስብሰባ ላይ አሰምተዋል።

የተከበሩ አቶ ተስፋዬ የአዋጁን አስፈላጊነት ሲያብራሩ፤ በአማራ ክልል በትጥቅ የተደገፈ ጥቃት መፈጸሙንና የተፈጠረውን አለመረጋጋት በመደበኛው የህግ ሥነ ሥርዓት ለማስከበርና ለመቆጣጠር የማይቻልበት ሁኔታ መፈጠሩ፣ ይህም የክልሉን መንግስታዊ ሥርዓት አደጋ ላይ የጣለ በመሆኑ ሃገርን ከጥፋት ለመታደግ እና የህዝቦችን ሠላምና ደህንነት ለማስጠበቅ አዋጁ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ማብራሪያውን ተከትሎ በቀረበው ረቂቅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ የምክር ቤት አባላት የተለያዩ አስተያየቶችና ጥያቄዎችን አንስተዋል፡፡ በተነሱ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ዙሪያም በፍትሕ ሚንስትሩ ክቡር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ሠፊ ምላሽና ማብራሪያ ተሠጥቶባቸዋል፡፡

ምክር ቤቱ፤ የህዝብን ሠላም፣ የሃገርን ደህንነት እና ህግና ሥርዓትን ለማስከበር በተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በአዋጅ ቁጥር 1299/2015 በ12 ድምፅ ተአቅቦ በ16 ታቃውሞ በአብላጫ ድምፅ መጽደቁን ከምክርቤቱ ያገኘነው መረጃ ያሳያል፡:

በአማራ ክልል “ሁሉንም ኃይሎች” ያካተተ “ጊዜያዊ አስተዳደር” እንዲቋቋም አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጠየቁ የቀድሞው የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በአማራ ክልል “ሁሉንም ኃይሎች” ያካተተ “ጊዜያዊ አስተዳደር” እንዲቋቋም ጠየቁ። አቶ ገዱ በአማራ ክልል ያለውን “ችግር በቅንነት ለመፍታት” ፖለቲካዊ ንግግር መደረግ እንዳለበትም አሳስበዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን ወደ ስልጣን ያመጣውን “ለውጥ” ከመሩ ባለስልጣናት አንዱ መሆናቸው የሚነገርላቸው አቶ ገዱ ይህን ማሳሰቢያ የሰጡት፤ በዋነኛነት በአማራ ክልል ተፈጻሚ የሚሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተወካዮች ምክር ቤት ከመጽደቁ በፊት ባስደመጡት አስተያየት ነው። የገዢው ብልጽግና ፓርቲ የፓርላማ ተወካይ የሆኑት አቶ ገዱ፤ ዛሬ በተካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ የተገኙት፤ በአማራ ክልል ለተፈጠረው ችግር “በቅንነት” ሃሳባቸውን በማቅረብ “አስተዋጽኦ ለማበርከት” በማሰብ እንደሆነ ገልጸዋል። የአማራ ክልልን ለአምስት ዓመታት የመሩት አቶ ገዱ፤ በክልሉ በአሁኑ ወቅት ያለውን ችግር ለመፍታት መፍትሔው “የፖለቲካ ውይይት፤፡ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። “ይህን ችግር በቅንነት ለመፍታት ከተፈለገ መፍትሔው፤ እስካሁን በአማራ ክልልም ሆነ በሌሎች የኢትዮጵያ ክፍሎች ሲሞከር ከርሞ ሀገርን ወደ ከፋ ጥፋት ያመራው ወታደራዊ ኃይል መጠቀም ሳይሆን፤ የፖለቲካ ውይይት ነው የሚል እምነት አለኝ” ብለዋል አቶ ገዱ። አቶ ገዱ እንዲቋቋም በጠየቁት ጊዜያዊ አስተዳደር ይካተቱ ያሉትን አልዘረርዘሩም።

በመጨረሻም ምክር ቤቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መርማሪ ቦርድ አባላት ሹመትን አጽድቋል። የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ ዙር 2ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 1ኛ አስቸኳይ ስብሰባ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መርማሪ ቦርድ አባላት ሹመትን ውሳኔ ቁጥር 17/2015 አድርጎ በ1 ድምጸ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መርማሪ ቦርዱ አባላት፡- አቶ አዝመራው አንዴሞ ሰብሳቢ ዶ/ር ነጃት ግርማ ምክትል ሰብሳቢ፣ አቶ ሣዲቅ አደም አባል፣ አቶ መስፍን እርካቤ አባል ፣ ዶ/ር አብርሃም በርታ አባል ፣ወ/ሮ ፍሬህይወት ተሾመ አባል፣ አቶ ወንድሙ ግዛው አባል በመሆን ተሰይመዋል፤ የቦርዱ አባላት በጉባዔው ፊት ቃለ ማህላ ፈጽመዋል።

ዜናው ከኢትዮ ኢንሳይደር፣ ኢዜአ የተውጣጣ ነው


Exit mobile version