Site icon ETHIOREVIEW

የቀበሌ 14 ተጫዋቾችን 90 ደቂቃ ብቻ አጫውቶ የተበጫጨቀው ታኬታ አስገራሚው ሪፖርት

ጥር 12 ቀን 1980 በአዲስ ዘመን ጋዜጣ የታተመ እንደሆነ ተገለጾ የታተመው መረጃ 3800 ብር የፈጀ የቀበሌ 14 እግር ኳስ ቡድን ተጨዋቾች ጫማ ከዘጠና ደቂቃ ጨዋታ በሁዋላ ሙሉ በሙሉ ነትቦ በመበጫጨቁ የቀረበው ሪፖርት ጉድ የሚያሰኝ ነው። የዛሬዎቹን የከነማና የመንግስት ተቋማት ክለቦች ዝርፊያ ላየ ጉዳይ አስቂኝ ሳይሆን አሳዛኝም ነው። ወይ ዘመን!! ይህን ሪፖርት ያቀረቡት የኢሰፓ አባል ዛሬ በክፍለ ከተማ፣ በክልልና በመንግስት ተቋማት ስም በሚሊዮን ብሮች የሚታጨድበትን፣ ስንዝር የማይራመድ የኢትዮጵያ እግር ኩስ ጉዳይ ቢያዩት ያሰኛል።

በከፍተኛ ፲፬ ቀበሌ ፲፬ ለእግር ኳስ ተጫዋቾች በ፫ሺህ ፫፻፹ ብር የተገዛው “አዲዳስ ላፕላታ” ቡድኑ ለተጫወተበት ዘጠና ደቂቃዎች ብቻ አገልግሎት ሰጥቶ ከጥቅም ውጪ ሆኗል።

ይህ በጥቆማ ክፍሉ በደረሰበት ወቅት ከፍተኛውንና ቀበሌውን በስልክ የስፖርት ቤቱን በግንባር የኢትዮጵያ ደረጃ መዳቢ ባለስልጣንን በስልክ በማነጋገር ያገኘነውን አጠቃላይ መልስ እንደሚከተለው አቅርበናል።

“የቀበሌ ፲፬ የሂሳብ ሹምና የሕዝብ ሱቅ ሰብሳቢ ጓድ ቀደመ ተሾመ እንደገለጡት ቀበሌዉ ከሌሎች ቀበሌዎች ጋር የእግር ኳስ ውድድር ስለነበረበት ሐሙስ በ፲፬ /፭ /፹ የቀበሌው የሥራ አመራር ኮሚቴ ተሰብስቦ ለቡድኑ ታኬታ ጫማ፣ ማሊያና ገምባሌ ከሕዝብ ሱቁ ገቢ ወጪ ሆኖ እንዲገዛ ይወስናል።

ግዥው እንዲከናወን ለሂሳብ ሹምና የሕዝብ ሱቁ ሰብሳቢ ሁለት የሥራ አመራር አባላት ተመደቦላቸው መሆኑ ይነገራቸዋል። በ፲፬ ፭ ፹ ፕሮፎርማ ለመሰብሰብ በሚዘጋጁበት ወቅት የተመደቡት ጓዶች ባለመገኘታቸው በተጣበበ ሰዓት ውስጥ ለሚያከናውኑት ተግባር ቅድሚያ በመስጠት በስፖርት እንቅስቃሴ እገዛ የሚያደርጉ ሁለት ነዋሪዎችን በመያዝ ለግዥ መውጣታቸውን ተናግረዋል።

በሚፈልጉት ቁጥር «አዲዳስ ላፕላታ» ጫማ ለማግኘት የተለያዩ የስፖርት ቤቶችን አነጋግረዋል። በዋጋ፣ በቁጥር አለመስተካከል፣ ከሚፈልጉት ጋር የማይፈልጉትን እንዲወስዱ የሚያስገድድ ጥያቄ ስለቀረበላቸው ሳይስማሙ ቀርተው በመጨረሻም ከብሔራዊ ስፖርት ቤት አንዱን አዲዳስ ላፕላታ ጫማ በ፪፻፷ ብር ሂሣብ የ፲፫ ጫማ ዋጋ ፫ሺህ ፫፻፹ ብር፤ በ፫ሺv ፮፻፷ ብር ደግሞ ፲ የስፖርት ቁምጣ ፤ ፲፪ ማሊያና ፰፫ ገምባሌ ገዝተው ይመለሳሉ።

በማግሥቱ ቅዳሜ ጃን ሜዳ በተደረገ ውድድር ላይ ቡድኑ ሙሉ ትጥቁን አሟልቶ መግባቱን አስታውቀዋል። ውድድሩ በተጀመረ ግማሽ ጨዋታ ፍፃሜ ከመሆኑ አስቀድሞ ተጫዋቾቹ ጫማቸውን ማሳየት ቢጀምሩም ቀጥሉ ተብሎ ግማሽ ጨዋታው ካለቀ በኋላ የሁሉም ጫማ እንዳልሆነ መሆኑን ተመልክተን አዘንን ብለዋል።

ያም ሆኖ ጨዋታው መካሄድ ነበረበትና ዘጠና ደቂቃው ተጠናቆ እንዳለቀ ጫማዎቹ ሲታዩ እንዳጋጣሚ አንዱ ብቻ ደህና ከመሆኑ በቀር አሥራ ሁለቱ ታኬታዎች ሶላቸው ውልቅልቁ መውጣቱን ተናግረዋል። በ፲፮፭|፹ ሰኞ ጫማዎቹን በመሰብሰብ ለስፖርት ቤቱ ማስረከባቸውንና የስፖርት ቤቱ ባለቤትም ወደ ውጭ ሀገር በመሄዳቸው ቀበሌው ሌላ ጫማ ለማግኘት ወይም ገንዘቡ እንዲመለስለት ለማድረግ አለመቻሉን ጓድ ቀደመ ተሾመ የሂሣብ ሹምና የሕዝብ ሱቁ ሰብሳቢ ገልጠዋል።

የስፖርት ቤቱን ሠራተኞች ሄደን ባነጋገርናቸው ጊዜ ለናሙና ከተበላሹት መካከል ሁለት ጫማዎችን ያሳዩን ሲሆን፤ እስካሁን ይህን መሰሉ ችግር ያልገጠማቸው መሆኑን ተናግረዋል። ባለቤቱ ስላልነበሩም ሰፋ ያሉ ጥያቄዎችን ለማቅረብ አልተቻለም። ችግሩስ እንዲህ ተከሰተ ለመሆኑ የኢትዮጵያ ደረጃ መዳቢ ባለሥልጣን ሀገር ውስጥ ስለሚገቡ ዕቃዎች ጥራት ምን ይላል?

ጓድ እዝራ ተረፈ የጨርቃጨርቅና የቆዳ ውጤቶች የጥራት ፍተሻ ኃላፊን በስልክ አነጋግረናቸው ነበር። በሰጡን መልስም እስካሁን ደረጃ ከወጣላቸው እንደ መድኃኒት የጽሕፈት መሣሪያዎች ወረቀት ካርቶኖች ወደ ሀገር ውስጥ በሚገቡበት ጊዜ ከሚደረገው የጥራት ቁጥጥር ሌላ ሁሉንም ውጤቶች እንደማይቆጣጠሩ ተናግረዋል።

አንድ ባለድርጅት ከውጭ ድርጅቶች ጋር በሚደራደሩበት ጊዜ በሚያስገባቸው ውጤቶች ጥራት ፈትሹልኝ የሚል ጥያቄ ሲያቀርብ አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚሰጠው ተናግረዋል።

በሁሉም ውጤቶች ላይ ፍተሻ ለማካሔድ በውል ተደንግጐ የሚሠራበት ባለመሆኑ አብዛኞቹ ባለ ድርጅቶች እንደፍላጎታቸው ተደራድረው ወደ ሀገ ውስጥ እንደሚያስገቡ ገልጠው፤ ይህም የምናወጣው የውጭ ምንዛሪን ኅብረተሰቡ በሚፈልገውና የአገልግሎት ዘመኑም አስተማማኝ የሆኑ ውጤቶችን ለማግኘት እንደሚያዳግት ተናግረዋል።

አንዳንድ የውጭ ድርጅቶች ለናሙና የሚልኩትን ገንዘብ ወጪ ተደርጐበት ወደ ሀገር የሚገቡት ውጤቶችም ጥራት ተመሣሣይ እንደማይሆን ጠቁመው ይህንን ማስወገድም ባለድርጅቶች በሀገር ውስጥ የጥራት ፍተሻ እንደሚደረግ ከውጭ ድርጅቶች ጋር በሚያደርጉት ድርድር ውስጥ ቢያስገቡ የውጭዎቹን ባለድርጅቶች እንደሚያተጋ ያላቸውን አስተያየት ሰጥተዋል።

ከፍተኛ ወጪ ተደርጐባቸው የሚገዙ ዕቃዎች ላይ ማን እንደሚገዛ ፤ስንት ቀን የገበያ ዋጋና ጥራት ናሙና አሰሳ እንደሚያስፈልግ ትኩረት መሰጠት አለበት። ምንም እንኳን አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚፈለገው ነገር ይገኛል የሚል ቀና አመለካከት ቢኖርም፤ በይድረስ ይድረስ የሕዝብን ገንዘብ ጥሎ መሄድ የሚያስጠይቅ መሆኑ ለአፍታ መዘንጋት የለበትም።

ጥር 12 ቀን 1980 በአዲስ ዘመን ጋዜጣ የታተመ በሪሁ አረጋ


Exit mobile version