Site icon ETHIOREVIEW

በትግራይ [የጊዜያዊ አስተዳደሩን ለመንጠቅ ይሰሩ ነበር] የትባሉ አራት ከፍተኛ የትህነግ አመራሮችና የአስተዳደሩ አካላት ተሰናበቱ

« የትግራይን ክልል ከ32 ዓመታት በላይ በበላይነት ሲመራ የቆየው ህወሓት ለሁለት ዓመታት በተካሄደው አውዳሚ ጦርነት ምክንያት ከብዙ የትግራይ ተወላጆች በኩል ከባድ ተቃውሞ እየገጠመው መሆኑ መነገር ከጀመረ ቆይቷል። ከሰላም ስምምነቱ ጎን ለጎን “ለምን አስጨረሰን” በሚል ለሚነሳ ጥያቄና በክልሉ በጥቅሉ እንዲህ ያለ ቀውስ እንዲደርስ የተፍለገበት መነሻ ምን እንደሆነ የሚጠይቁ በርክተዋል የሚል ተደጋጋሚ መረጃ አዘል ጽሁፎችና አስተያየቶች እንደሚሰሙ ቢቢሲን ጨምሮ በርካታ የትህነግ የቀድሞ ደጋፊ የነበሩ ዘግበዋል።

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታቸው ረዳ አቶ ዓለም ገብረዋህድን ጨምሮ አራት ከፍተኛ አመራሮችን ከሥልጣን ማንሳታቸው ተስመቷል። ይህ የሆነው ባለፉት ሳምንታት አቶ ጌታቸውን ገምግሞ ከስልጣን ለማስወገድ ያለመ የትህነግ ካድሬዎች ስብሰባ መጠራቱን ተከትሎ ነው።

ከትህነግ ሰፈር መረጃ የሚያገኘው ቢቢሲ እነ ዶክተር ደብረጽዮንና ዓለም ገብረዋህድ የጠሩት ስብሰባ አቶ ጌታቸው የሚመሩትን ካቢኔ የማስወገድ ዓላማ እንደነበረው ዘግቧል። አሁንም የባለስልታናቱን መነሳት አስመልክቶ የሚከተለውን አስፍሯል።

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ በህወሓት እና በክልሉ ውስጥ ከፍተኛ ሚና አላቸው የሚባሉትን አቶ ዓለም ገብረዋህድን ጨምሮ አራት የጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች ከሥልጣን አነሱ።

ከሥልጣናቸው ከተነሱት መካከል በምክትል ፕሬዝዳንትነት ማዕረግ የትግራይ ክልል የጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት የሕዝብ አደረጃጀት አማካሪ የሆኑት አቶ ዓለም ገብረዋህድ ይገኙበታል።

አቶ ጌታቸው ከሥልጣናቸው ካነሷቸው አመራሮች መካከል የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ኃላፊ የነበሩት አማኑኤል አሰፋ፣ የደቡብ ምሥራቅ ዞን አስተዳዳሪ ሊያ ካሳ እንዲሁም የሰሜን ምዕራብ ዞን አስተዳዳሪ ተክላይ ገ/መድኅን ይገኙበታል።

የአቶ ጌታቸው ረዳ ፊርማ ያረፈበት ደብዳቤ ኃላፊዎቹ ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምሥጋና በመግለጽ ከጥቅምት 14 እና 15/2016 ዓ.ም. ጀምሮ ከኃላፊነታቸው መነሳታቸውን ገልጿል።

አቶ ዓለም ገብረዋህድ የህወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል እና የፓርቲው የጽ/ቤት ኃላፊ ሲሆኑ፣ አማኑኤል አሰፋ፣ ሊያ ካሳ እና ተክላይ ገ/መድኅን ደግሞ የህወሓት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ናቸው።

ለአራቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከኃላፊነት መነሳት ምክንያት ምን እንደሆነ በጊዜያዊ አስተዳደሩ በኩል የተሰጠ ማብራሪያ የለም።

በክልሉ ዋነኛ ፓርቲ የሆነው ህወሓት ከፍተኛ አመራሮቹ ከጊዜያዊ አስተዳደሩ እንዲወጡ መደረጋቸውን በተመለከተ እስካሁን ያለው ነገር የለም።

አቶ ጌታቸው ባለፉት ሳምንታት የተለያዩ ኃላፊዎችን ከሥልጣን ሲያነሱ የአሁኑ የመጀመሪያቸው አይደለም። ከሳምንት በፊት የህወሓት ከፍተኛ አመራሮች ከጠሩት እና ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከተቃወመው ስብሰባ ጋር በተያያዘ የዞን ባለሥልጣናትን ማሰናበታቸው ይታወቃል።

ከተመሠረተ ወራት ባስቆጠረው በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር እና በህወሓት መካከል የተፈጠረው ልዩነት በግልጽ ወጥቶ ባይነገርም ባለፉት ቀናት ልዩነቱ በይፋ መታየት ጀምሯል።

ከሳምንት በፊት የህወሓት አመራሮች የጠሩትን የካድሬዎች ስብሰባ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት “ያለ እውቅና የተጠራ ነው” በማለት እንዳይካሄድ መወሰናቸው ይታወሳል።

ይህ በህወሓት ከፍተኛ አመራሮች መካከል የሃሳብ ልዩነት ያስከተለ ሲሆን፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል እና የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ስብሰባው እንዳይካሄድ የወሰዱትን እርምጃ “ተቋማዊ አሠራርን ያልተከተለ ነው” ሲል ፓርቲው ተችቶታል።

የፌደራል መንግሥቱ እና ህወሓት ለሁለት ዓመታት የቆየውን ደም አፋሳሽ ጦርነት ያስቆመውን የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ከተፈራረሙ በኋላ ጌታቸው ረዳ ክልሉን በጊዜያዊነት እንዲያስተዳደሩ በጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ መሾማቸው ይታወሳል።

አቶ ጌታቸው ጊዜያዊ አስተዳደራቸው ዘጠኝ ወራትን ቢያስቆጥርም፣ በትግራይ ክልል ባሉ ዞኖች እና ወረዳዎች መዋቅሩን መዘርጋት አለመቻሉን ተናግረው ነበር።

የአቶ ጌታቸው ጊዜያዊ አስተዳደር ባለፉት ወራት የሚጠበቅበትን ሥራ ለማከናወን እንቅፋቶች እንደነበሩበት የገለጸ ሲሆን፣ እራሳቸውም አስተዳደራቸው በዞኖች እና በወረዳዎች ውስጥ እግሩን መትከል አለመቻሉን እና አንዳንድ ወረዳዎች የጊዜያዊ አስተዳደሩ አካል መሆናቸውን እንዳይቀበሉ የሚያደርግ “የተደራጀ እንቅስቃሴ” መኖሩን ተናገረው ነበር።

አቶ ጌታቸው አባል የሆኑበት እና በዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል የሚመራው ህወሓት ከአንድ ሳምንት በፊት በጠራው ስብሰባ ላይ የአቶ ጌታቸው ጊዜያዊ አስተዳደርን ዋነኛ አጀንዳ ለማድረግ ታስቦ እንደነበር ለደኅንነታቸው ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ውስጥ አዋቂ ለቢቢሲ መናገራቸው ይታወሳል።

“የተጠራው የካድሬዎች ስብሰባ የጊዜያዊ አስተዳደሩን እና በተለይም የአቶ ጌታቸው ረዳን አመራር ለመገምገም ያነጣጠረ እና ህወሓት የጊዜያዊ አስተዳደሩን ሥልጣን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ያለመ ነበር” ብለዋል።

የትግራይን ከ32 ዓመታት በላይ በበላይነት ሲመራ የቆየው ህወሓት ለሁለት ዓመታት በተካሄደው አውዳሚ ጦርነት ምክንያት ከብዙ የትግራይ ተወላጆች በኩል ከባድ ተቃውሞ እየገጠመው መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል።


Exit mobile version