Site icon ETHIO12.COM

“ለጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር አብይ አህመድ ያላችሁን ፍቅር በራስ ተነሳሽነት ለመግለጽ ያሳያችሁት አንድነት የሚበረታታና የሚደገፍ ተግባር ነው” -አቶ ሙስጠፌ

የሶማሌ ክልል ነዋሪዎች ለጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር አብይ አህመድ ያላችሁን ፍቅር በራስ ተነሳሽነት ለመግለጽ ያሳያችሁት አንድነት የሚበረታታና የሚደገፍ ተግባር መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መሰተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሀመድ ገለጹ፡፡ ሀገራችሁን ኢትዮጵያን የምትወዱና የዶክተር አብይ አህመድ መንግስትን እየደገፋችሁ ያላችሁ በመሆኑ ልትኮሩና ልትደሰቱ ይገባልም ብለዋል፡፡

በሶማሌ ክልል ሀገራዊ ለውጡንና ዶ/ር አዐብይ አህመድን ለመደገፍ ጅግጅጋ ከተማን ጨምሮ በ11 ዞኖችና ወረዳዎ የድጋፍ ሰልፍ ተካሂዷል፡፡ የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መሰተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሀመድ ዑመር ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤የሶማሌ ህዝብ የሚታወቀው በፌድራል ስርዓቱ የማይደራደር በመሆኑ ከሌሎች ብሄር ብሄረሰብ ጋር በፍቅርና በጋራ አብሮ የመኖሪን እሴቱን በማጠናከር የሶማሌን ህዝብ አንድነት ከማይፈልጉ ቅጥረኛና ተላላኪ ከሆኑ ግለሰቦችና ቡድኖች በመጠበቅ ሁላችንም በፍቅርና በአንድነት ኢትዮጵያን ልናሳድጋት ይገባ ብለዋል፡፡

የተጀመረውን ሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት የብሔር ብሔረሰቦችን እኩልነትና አንድነት ለማረጋገጥ በሚከናወኑ ተግባራት ከዶክተር አብይ አህመድና ከመንግስታቸው ጎን በመቆም ሀገራዊ ኃላፊነታችሁን ልትወጡ ይገባል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ እንጂነር መሀመድ ሻሌ በበኩላቸው ለዉጡንና ዶክተር አብይ አህመድን በመደገፍ እንዲሁም ከዶክተር አብይ አህመድ ጎን በመቆም ሀገራቱን ወደ ፊት እናሻግራለን ብላችሁ ከተለያዩ ቦታዎች በመምጣትና እዚህ በመገኘት ያላችሁን ፍቅርና አድናቆት በመግለፃቹ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ለተጀመረው ሀገራዊ ለውጥ የሶማሌ ህዝብ ብዙ የህይወት መስዋዕትነትን ሲከፍል መቆየቱን በመግለጽ በቀጣይም የሀገሪቱን ሰላም፤ አንድነትና እድገት ለማፋጠን ሁሉም በጋራና በአንድነት በመሆን ዘብ ሊቆም ይገባል ብለዋል፡፡

ብልጽግና ማለት ስራ፣ እድገት፣ ፍቅርና አንድነት መሆኑ የገለጹት ሃላፊው በተቃራኒው መንገድ ዝጉ፣ ስራ አትስሩ፣ የግለሰብንና የመንግስት ንብረትን አውድሙ የሚሉ አካላት የኢትዮጵያን አንድነት የማይፈልጉ ግለሰቦችና ቡድኖች ተልእኮ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ የጥፋት ሃይሎችን በማጋለጥ ሐገሩን፣ እራሱንና ወገኑን ከጥፋት ሊታደግ ይገባል ብለዋል፡፡

በድጋፍ ሰልፉም “አሸናፊ ሐሳብን እናራምዳለን፣ እንደ አይናችን ብሌን ዶክተር አቢይ እንጠብቃለን፣ ፅንፈኝነተን አምርረን እንታገለዋለን!፤ ብልፅግና የሁሉም ችግሮች መፍቻ ቁልፍ ነዉ!፤ ከብልፅግና ጋር ስኬታማ እንደምንሆን አንጠራጠርም!” የሚሉ መፈክሮችን በመያዝ ድጋፋቸውን ገልጸዋል፡፡

በድጋፍ ሰልፉም ከ11 ዞኖችና ሁሉም ከከተማና ከገጠር ቀበሌዎች የተውጣጡ በርካታ ነዋሪዎች መሳተፋቸውን ከክልሉ መንግስት ኮሙዪኒኬሽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

(ኢ ፕ ድ )

Exit mobile version