Site icon ETHIO12.COM

ከህዋሓት አመራሮች የጥፋት ተልዕኮ ተቀብሎ ጥቃት ለማድረስ ተንቀሳቅሷል የተባለ ተጠርጣሪ ላይ ክስ ሊመሰረት ነው

ከህዋሓት አመራሮች የጥፋት ተልዕኮ ተቀብሎ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ህዝብ ላይ ጥቃት ለማድረስ ተንቀሳቅሷል የተባለ ተጠርጣሪ ላይ ክስ ሊመሰረት ነው

ከህዋሓት አመራሮች የጥፋት ተልዕኮ ተቀብሎ በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ህዝብ ላይ ጥቃት ለማድረስ ተንቀሳቅሷል የተባለ ተጠርጣሪ ላይ ክስ ሊመሰረት ነው።

አቶ አለም ደስታ የተባሉት ተጠርጣሪ ዛሬ ከሰአት በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው ለአቃቢ ህግ ክስ መመስረቻ ቀናት ተፈቅዷል።

ተጠርጣሪው ከህዋሓት አመራሮች የጥፋት ተልዕኮ ተቀብለው በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ህዝብ ላይ ጥቃት ለማድረስ ና አገርን ለማፍረስ ሲንቀሳቀሱ ነበሩ ተብለው በብሄራዊ መረጃ ደህንነት አገልግሎት እና በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ከተደበቁበት በክትትል በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ ሲከናወንባቸው መቆየቱ ይታወሳል።

ተጠርጣሪው የጦር መሳሪያዎችን ለህወሓት ቡድን ከማቀበል በዘለለ ሃገሪቱን ለማፍረስ ከህወሓት አመራሮች ጋር በመቀናጀት ሲሰሩ እንደነበር መርማሪ ፖሊስ ለፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የጊዜ ቀጠሮ ችሎት ማስረዳቱ ይታወሳል።

ብሄራዊ መረጃ ደህንነት አገልግሎት ባደረገው የቴክኒክ ምርመራም ተጠርጣሪው በኦሮሚያ ክልል ምርጫ እንዳይካሄድ ከኦነግ ሸኔ ጋር በትብብር ስለመስራታቸው የሚያመላክቱ በሁለት የሞባይል ስልካቸው ያደረጉት የስልክ ልውውጥ እና የተለያዩ መልዕክቶች መገኘቱን ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ገልጾ ነበር።

የህወሓት አመራሮች ለኦነግ ሸኔ ሲያደርጉ ለነበሩት የገንዘብ እና የመሳሪያ ድጋፍ በትብብር ስለመስራታቸው በቴክኒክ ማስረጃም መቅረቡ ተገልጿል።

በተጨማሪም የሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት መስጠፌ ሙሃመድ ከስልጣን ለማውረድ ከህወሓት ደጋፊዎች ከሆኑ ከቀድሞ የሶማሌ ክልል አመራሮች ጋር የነበራቸውን ግንኙነት የተመለከተው የቴክኒክ ማስረጃው ÷በተለይም እነ አብዱል ፈታ መሃመድን ለወንጀል ጥምረትና ተሳትፎ አዲስ አበባ በማስመጣት የሆቴል ክፍያ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉም ነው የተገለጸው።

እንዲሁም ለህወሓት አመራሮች የነበራቸው የመረጃ ልውውጥ የሚያመላክት የቴክኒክ ምርመራ ውጤትም ተያይዞ ቀርቧል።

ከዚህ በፊትም ተጠርጣሪው ከአዲስ አለም ቤሌማ ፣ ከስብሃት ነጋ ፣ ከዶክተር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል ፣ ከጌታቸው ረዳ እና ከኦነግ ሸኔ አመራሮች ጋር የነበራቸወን የስልክ ልውውጥ የሚገልጽ በብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት የቴክኒክ ምርመራ ተደርጎ ለፍርድቤቱ መቅረቡ ይታወሳል።

በዚህ መልኩ ሲከናወን የነበረው ምርመራ መጠናቀቁን ነው መርማሪ ፖሊስ ዛሬ ከሰአት በኋላ ለችሎቱ ያስረዳው።

በችሎቱ ከፖሊስ ጋር አብሮ የቀረበው ጠቅላይ አቃቢህግም በስነ ስርአት ህጉ መሰረት በአዲስ አበባና መቀሌ ሲፈጸም የነበረው ወንጀል ክብደትና ስፋት እንዲሁም ከውስብስብነት አንጻር መዝገቡን ተመልክቶ ክስ ለመመስረት ተጨማሪ ቀናት እንደሚያስፈልጉት ለችሎቱ አብራርቷል።

የተጠርጣሪ ጠበቃ እስካሁን ሲከናወን በነበረው ምርመራ አቃቢህግም ከፖሊስ ጋር እንደሚመረምር ነው የምናውቀው ስለዚህ እንደ አዲስ መዝገቡን ለማየት መባሉ አግባብነት የለውም ብለዋል።

በተጨማሪም የጊዜ ቀጠሮ ችሎቱም እስካሁን ሲሰበስብ የነበረውን ማስረጃ በማጠናቀቁ ከግምት አስገብቶ ዋስትና ሊፈቅድላቸው ይገባል ሲሉ የዋስትና ጥያቄ አቅርበዋል።

ጉዳዩን የተከታተለው ፍርድ ቤቱም የዋስትና ጥያቄያቸውን በማለፍ አቃቢህግ ክስ እንዲመሰርት 14 ቀናተ ፈቅዷል።

በታሪክ አዱኛ (ኤፍ.ቢ.ሲ)

Exit mobile version