Site icon ETHIO12.COM

ንግድ ባንክ የብር ወለድ ለውጥ ማሻሻያ አደረገ

 የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአንዳንድ የአገልግሎት ዘርፎች ላይ የዋጋ ማሻሻያ ማድረጉን አስታውቋል።

ባንኩ ማሻሻያ ያደረገው በብድር ወለድ ምጣኔና በዓለም አቀፍ የባንክ አገልግሎቶቹ ላይ ነው።

የዋጋ ማሻሻያውን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ በሰጡት መግለጫ በባንኩ ገቢና ወጪ ላይ የተከሰተውን መዛባት ለማስተካከል፣ ባንኩ ላይ የሚደርሰውን ጫና ለመቀነስ፣ በዝቅተኛ ዋጋ ወይም በነፃ በሚሰጣቸው አገልግሎቶች ላይ አነስተኛ ማስተካከያ ለማድረግ፣ እና ከገበያው ሁኔታ ጋር ለማቀራረብ በአብዛኛው የአገልግሎት ዘርፎች ላይ ከ1 በመቶ ያልበለጠ የወለድ ምጣኔ መጨመር የሚያስችለውን የዋጋ ማሻሻያ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

የብድር ወለድ ምጣኔ መጠነኛ ማሻሻያ የተደረገው ብድሮችን በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ገደብ በመከፋፈል እና ባንኩ የሚሰጣቸው የአገልግሎት አይነቶችን ታሳቢ በማድረግ መሆኑን አቶ አቤ ሳኖ በመግለጫቸው አስታውቀዋል፡፡

የወጪ ንግድ የአጭር ጊዜ አገልግሎቶች ላይ መጠነኛ ጭማሪ ብቻ ተደርጎ፤ የረጅም ጊዜ አገልግሎቶች ዋጋ ደግሞ ባለበት እንዲቀጥል መደረጉንም ገልፀዋል፡፡

የወጪ ንግድን ለማበረታታት ከወጪ ንግድ ጋር የተያያዙ የብድር አገልግሎቶቹ ላይ ሲያስከፍለው በነበረው የወለድ ምጣኔ ላይ እንዲሁም መንግስት ለሚያስመጣው መድሀኒት የሚቀርበው የውጭ ምንዛሬ አገልግሎት ተመን ላይ ቅናሽ መደረጉም ነው በመግለጫው የተገለፀው፡፡

ህብረተሰቡ ላይ የሚደርሰውን ጫና ለማስቀረት ባንኩ ለነዳጅ የሚያቀርበው የውጭ ምንዛሬ አገልግሎት ተመን ባለበት እንዲቀጥል መወሰኑን የገለጹት አቶ አቤ፤ ሌሎች በመንግስት የሚሠሩ ሥራዎች የአገልግሎት ዋጋ ላይ አነስተኛ ጭማሬ ብቻ መደረጉንም አስታውቀዋል፡፡

የባንኩን ውጤታማነት ለማስቀጠልና ለሀገር የሚያበረክተውን አስተዋጽዖ ለማሳደግ የተደረገው የዋጋ ማስተካከያ አስፈላጊ መሆኑን የገለፁት ፕሬዚዳንቱ፤ ባንኩ እስካሁን ከመደበኛ አገልግሎት የሚያገኘው 27 በመቶ ብቻ የነበረ ሲሆን፤ ከ73 በመቶ በላይ በነፃ እና በዝቅተኛ ዋጋ አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን ተናግረዋል።

እስካሁን በነበረው አሰራር ባንኩ ዝቅተኛ ዋጋ በማስከፈል አገልግሎት መስጠቱ ገበያን በማዛባት፣ ሃብት በማባከን፣ ፕሮጀክቶች በጊዜ እንዳይጠናቀቁ፣ በብድር አከፋፈል በኩልም ዳተኝነትን ማሳየትና ጥገኝነትን የሚያበረታታ ነውም ተብሏል።

ባንኩ መንግስታዊ ከመሆኑ አንፃር ዋጋ የማረጋጋት ኃላፊነት እንዳለበት የገለጹት አቶ አቤ፤ አሁን የተደረገው አነስተኛ የዋጋ ማስተካከያ ህብረተሰቡ ላይ ጫና በማያሳርፍ መልኩ እና የባንኩን ህልውና በሚያስጠብቅ መልኩ እንዲሆን መደረጉን ማስረዳታቸውን ከባንኩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡


ምንጭ:-ኢፕድ

Exit mobile version