Site icon ETHIO12.COM

ከኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) የተሰጠ መግለጫ

መንግስት በፈጠራ ክስ ያሰራቸውን አባሎቻችንና ወገኖቻችንን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታ አጥብቀን እንጠይቃለን፡፡

ፓርቲያችን፤ የኦሮሞ ፌዴራለዊ ኮንግረስ በሀገሪቱ ሕግ መሠረት ተመዝግቦና ዓላማውን በሠላማዊ አግባብ ብቻ ታግሎ ለማሳካት እየተንቀሳቀሰ የሚገኝ ነው፡፡

ፖሊሲያችን፣ የፖለቲካ ፕሮግራማችንና አቋማችን በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነትን በማግኘቱ ምቾት ያልተሰማው ገዥው ፓርቲ (ኢህአዴግ/ብልፅግና) በተለይ ከ2005 ዓም ጀምሮ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችንን በአሸባሪነት በመፈረጅ ክስ መስርቶ ሲያንገላታ ከቆየ በኋላ የሞቱት ሞተው በሕይወት የተረፉትና በየእስር ቤቶች ፊዳቸውን ሲቆጥሩ የነበሩት ቄሮ/ቃሬ በአጠቃላይ ሕብረተሰባችን በከፈሉት መስዋዕትነት በ2010 ዓም አጋማሽ በኋላ ሊፈቱ ችለዋል፡፡
ከዚሁ ጊዜ በኋላ ለረጅም ጊዜ ስንመኘው የነበረው ዴሞክራሲ ሰፍኖ አዲስቷ ኢትዮጵያን እንገነባለን ብለን ተስፋ የሰነቅን ቢሆንም፤ ከ2011 አጋማሽ በኋላ በአገረሸው የብልፅግና ፓርቲ ጭፍን የማሳደድ፣ የማሰርና የመግደል እርምጃዎች የተነሳ አንዳች ወንጀል ያልፈጸሙ ከከፍተኛ አካል ጀምሮ እስከ ታችኛው እርከን ድረስ የሚገኙ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን የሌለ የወንጀል ታፔላ ተለጥፎባቸው እስር ቤቶች እንዲታጎሩ በመደረጋቸው፤ ተስፋችን ሟሸሸ፤ የሕዝቦችን መብትና ነፃነት ለማስከበር ሌላ የትግል ምዕራፍ እንዲካሄድም ጠይቋል፡፡

የታሳሪ አባሎቻችንና ወገኖቻችን ትግል የግላቸውን ወይም የፓርቲያቸውን ፍላጎት ለማስጠበቅ ሳይሆን ለመላው ወገኖቻችን በመሆኑና የዓላማ ጽናትም ስላላቸው፤ እነሆ ከአስራ አምስት ቀናት በፊት የጀመሩት የረሃብ አድማ በሕይወታቸው ላይ ከፍተኛ አደጋ እንዲያዣንብብ አድርጓል፡፡

በተለያዩ መግለጫዎችና አቤቱታዎች ስንገልጽ እንደቆየነው ሁሉ የመመገብ ተአቅቦ ያደረጉ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ስለሆነ ቀጥሎ የተመለከቱትን ጥያቄዎች ደግመን መንግስትንና ሕዝባችንን ልንጠይቅ ተገድደናል፡፡

  1. በረሃብ አድማ ላይ የሚገኙ አባሎቻችን በአሁን ጊዜ የረሃብ አድማው ከረሃብ አድማ በላይ አልፎ የመታመም ደረጃ ላይ ያደረሳቸውና ሕይወታቸውም አስጊ ሁኔታ ላይ እንድወድቅ ስላደረገ መንግስት አስቸኳይ የሕይወት ማዳን ሥራ ሰርቶ ግዴታውን እንዲወጣ አበክረን እንጠይቃለን፡፡ እነዚህ ወገኖቻችን ተገቢ የሕክምና ዕርዳታ ካላገኙ ሕይወታቸው አደጋ ላይ የሚወድቅ ከሆነ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መንግስት በሕግም ሆነ በታሪክ ተጠያቂ ነው፡፡
  2. የኢ. ፈ. ዲ. ሪ. መንግስት በፈጠራ ክስ ያሰራቸውን አባሎቻችንና ወገኖቻችንን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታ አጥብቀን እንጠይቃለን፡፡
  3. መላው የኢትዮጵያ ሕዝቦች፣ በተለይም የኦሮሞ ሕዝብ፤ መላው የዓለም ሕብረተሰብ፤ በአገራችን ሕዝቦች ላይ እያንጃበበ ያለው እልቂት እንዲወገድ በተለያዩ ስልቶች በኢ. ፌ. ዲ. ሪ መንግስት ላይ አስፈላጊውን ጫና በማድረግ፤ መንግስቱ እየወሰደ ያለው የኃይል እርምጃዎችን እንዲያስቆሙ እየጠየቅን፤ ፓርቲያችን ከሚያካሂደው የመብትና ነፃነት ማስከበር ትግል ጎን እንድትቆሙና እንድትደግፉን የከበረ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

ሠላማዊ የሕዝቦች ትግል ያሸንፋል!
የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ)
ፊንፊኔ፤ የካቲት 5/2013 ዓም

Exit mobile version