Site icon ETHIO12.COM

ኢዜማ ሊሰፋ የሚችል ችግር ውስጥ እንዳለ እየተሰማ ነው፤ የፓርቲው ሊቀመንበር የሺዋስ እጩ ተወዳዳሪ አልተደረጉም

ኢዜማ ያወጣው መግለጫ የውስጥ ግለቱን አክሮታል፤ ዛጎል ኦንላይን

አቶ የሺዋስ ለጊዜው አስተያየት አልሰጥም ብለዋል


የዜግነት ፖለቲካ ላይ ትክረት ሰጥቶ እየሰራ ያለውና በመላው አገሪቱ የምርጫ ጣቢያዎች ለመወዳደር አቅድ የያዘው ኢዜማ ሊሰፋ የሚችል የውስጥ ቀውስ እንደገጠመው ስለ ልዩነቱ የሚያውቁ ለኢትዮ 12 ገልጸዋል። ፓርቲው በቅርቡ ያወጣው መግለጫ የነበረውን አለመግባባት አብሶታል።

መረጃውን ያካፈሉን ክፍሎች እንደሚሉት ኢዜማ “ ልሂቃን ነን፤ ሃሳብ አመንጪዎች ነን” የሚል እሳቤ ያላቸው ሌሎችን ይጫናሉ። ፓርቲያቸው ሰማያዊን አክስመው ኢዜማን የመሰረቱት አቶ የሺዋስና እሳቸው ዙሪያ ያሉ በዚህ እሳቤ ቅር ከተሰኙት መካከል ናቸው።

መረጃውን ለማጥራት የአዲስ አበባ ዘጋቢያችን ለአቶ የሺ ዋስ ደውሎ “ በዚህ ጉዳይ ለጊዜው መልስ አልሰጥም” ብለዋል። ዘጋቢው ሊያናግራቸው የፈለገው አቶ የሺዋስ የፓርቲው መሪ ሆነው ሳለ ስለምን የምርጫ እጩ አልሆኑም በሚለው ጉዳይ ነበር። ፈቃደኛ ሲሆኑ አሁንም ሃሳባቸውን ለማካተት እንሞክራለን። ወይም ጹሁፍ ከላኩ እናስተናግዳለን። ያም ሆኖ “የፓርቲው ሊቀመንበር ስለሆኑ ህጉ አይፈቅድላቸውም” ሲሉ የድርጅቱ ደጋፊዎች በጎንዮሽ ገልጸዋል።

ሲቀናጅ ሁሌም እንከን የሚገጥመው የፕሮፌሰር ብርሃኑ ፓርቲ እንደተባለው ችግር ገጥሞት እንደሆነ ለማጣራት የህዝብ ግንኙነት ሃላፊውን ለማናገር ተሞክሮ ስልካቸው ጥሪ ሲደረግለት ወደ መልዕክት ማስቀመጫ ስለሚልክ ሊሳካ አልቻለም። እሳቸውም የሚሉት ነገር ካለ ለማስተናገድ ዝግጅት ክፍሉ ፈቃደኛ ነው። የዜናው ምንጮች ደጋግመው የሚያሳስቡት ኢዜማ በምርጫ ዋዜማ ራሱን ከውስጥ ችግር እንዲያጸዳ ለማሳሰብ እንጂ ሌላ ፍላጎት እንደሌላቸው አስታውቀዋል። አለያ ችግሩን ካልቀረፉ ምርጫ ሲቃረብ ሊጎዳቸው ይችላል ባይ ናቸው። አብን ኢዜማ ውስጥ እጃቸው እንዳለበት ለውጭ ሚዲያዎች መናገራቸውንም ያስታውሳሉ።

ይህንን ያንብቡ – አብን “ስውሩ ትህነግ!” ወይስ “የአማራው ልብ?”

ከሰሞኑ ፓርቲው ባወጣው መግለጫ ላይ የኤርትራ መከላከያ ከኢትዮጵያ መከላከያ፣ ከአማራ ልዩ ሃይል፣ ከአማራ ሚሊሻና ራሳቸውን ካደራጁ የአካባቢው ወጣቶች ጋር በመሆን የትህነግ ሰራዊት ላይ በህብረት ጥቃት በመክፈታቸው ጦርነቱ በአጭር ጊዜ ሊጠናቀቅ እንደቻለ መስማቱን ጠቅሶ የዘገበው ሙሉ ስምምነት እንዳላገኘ ተሰምቷል። በዚህ ቅር የተሰኙ በቅርቡ ሃሳባቸውን እንደሚሰጡ ጠቁመዋል። በሁመራ አካባቢ የአማራ ክልል በሌሎች ብሄር አባላት ላይ መድልዎ እንደሚደረግ ጠቅሶ አስተያየት ያሰፈረው መግለጫ ሌላው ልዩነት የተነሳበት ጉዳይ ሆኗል።

ስማቸው ለጊዜው እንዲደበቅላቸው የጠየቁ “ኢዜማ የኢትዮጵያ መንግስትና ሰራዊት ከኤርትራ መከላከያ ሰራዊት ጋር ተባብሮ ትህነግን ደመሰሰ የሚል መግለጫ በማውጣት ቀዳሚ መሆኑ አስደንግጦናል። የህግ ማስከበር ዘመቻውን በገሃድ የኤርትራ መከላከያ ተሳትፎበታል የሚል ምስክርነት የሰጠ ፓርቲ በመሆን መመዝገቡ ሃዘን ፈጥሯል” ሲሉ መግለጫውን ሲመከከቱ እሳቸውን ጨምሮ የደነገጡ እንዳሉ አመልክተዋል።

በተለያዩ ጉዳዮች ላይ መረጃ የሰጡ ክፍሎች ስም አንስተው ቢናገሩም ለጊዜው ከማተም ተቆጥበናል። መግለጫውን “ ነጮችን ለማስደሰት የተደረገ ነው” ሲሉ ያሰፈሩትንም ሃሳብ ለጊዜው ይዘነዋል። አቶ ናትናኤል ፈለቀ ምላሻቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ ከሆኑ አካተን ሙሉውን እናቀርባለን።

Exit mobile version