Site icon ETHIO12.COM

“ብልጽግና በለውጥ ውስጥ የተወለደ፣ ለለውጥ የሚተጋ፣ የዛሬ እና የነገ ፓርቲ ነው”


መጪውን ምርጫ ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ በማድረግ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን አሸናፊ የሚሆኑበት ማድረግ እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመደ አሳሰቡ።

ብልጽግና ፓርቲ የምርጫ ማኒፌስቶውንና የመወዳደሪያ ምልክቱን ይፋ አድርጓል።

የምርጫ 2013 የብልጽግና ፓርቲ ማኒፌስቶና የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት “ሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነት ለጋራ ብልጽግና” በሚል መሪ ሃሳበ ይፋዊ የእውቅና መድረክ በሸራተን አዲስ ተካሂዷል፡፡

በመርሃ ግብሩ የብልፅግና ፓርቲ ፕሬዚደንት ዶክተር አብይ አህመድን ጨምሮ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ተገኝተዋል።

የፓርቲው የምርጫ ምልክት የሚበራ አምፑል መሆኑ ይፋ ሲሆን ምክንያቱ ደግሞ ፓርቲው የለውጥና የተስፋ በመሆኑ በብርሃን ለመመሰል ነው ሲሉ የፓርቲው የምርጫ ሃላፊ አቶ ዛዲግ አብርሃ ገልፀዋል።

አገሪቷ ከአስቸጋሪ ሁኔታ ወጥታ ወደ ብልጽግና የምታደርገው ጉዞ ከጨለማ ወደ ብርሃን መሆኑን የሚያመላክት፣ ፍትሃዊነትና እኩልነትንም የሚያሳይ መሆኑንም አብራርተዋል።

የብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ብናልፍ አንዱዓለም ምርጫው ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ከሁሉም ጋር በትብብር እንደሚሰራ ተናግረዋል።

ፓርቲው በምርጫው አሸንፎ ለመውጣት በዴሞክራሲያዊ መንገድ በውድድር ይሰራል ያሉት አቶ ብናልፍ ለዚህ ይረዳው ዘንድ ማኒፌስቶና የምርጫ መወዳደሪያ ምልክቱን ይፋ አድርጓል ብለዋል።

የፓርቲው ፕሬዚደንት ዶክተር አብይ አሕመድ የፓርቲውን ማኒፌስቶና የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት ይፋ ሲያደርጉ ‘ማኒፌስቶው ከሕዝባችን ጋር የምንገባው ኮንትራት ሳይሆን ቃል ኪዳን ነው’ ብለዋል።

ይህ ቃል ኪዳን እውን እንዲሆን እያንዳንዱ የብልጽግና አባል በፍፁም ፈቃደኝነት ራሱን በመስጠት አገልጋይ መሆን እንደሚጠበቅበትና ከሕዝቡም ድጋፍ እንደሚጠብቅ ተናግረዋል።

በሚሰራው ስራ የምትታሰበዋን የበለፀገች ኢትዮጵያ እውን ማድረግ እንደሚቻል አንስተው የፓርቲው ማኒፌስቶ ድርሰት ሳይሆን ከአንድ ዓመት በላይ መረጃ በመሰብሰብና ከሕዝቡ ጋር በመወያየት የተገኙ ግብዓቶችን በማካተት መዘጋጀቱን ገልፀዋል።

ፓርቲው ባለፉት ሦስት ዓመታት በርካታ ስኬቶችን እያስመዘገበ መምጣቱን ጠቅሰው ከብዙ መከራና ፈተና በተግባር እየተማረ አሁን ያለበት ደረጃ የደረሰ መሆኑን ተናግረዋል።

ብልፅግና መጀመር ብቻ ሳይሆን መጨረስ እንደሚቻል ያሳየ ስብስብ መሆኑን የገለፁት ዶክተር አብይ ፓርቲው ኢትዮጵያዊያንን ከባዕዳን አይዲዮሎጂ ነፃ ያወጣና የመደመር መንገድ ያመጣ መሆኑን አክለዋል።

ለዚህም የሕዳሴ ግድብን የመጀመሪያ የውሃ ሙሌት በስኬት መጠናቀቅን፣ የሸገርና እንጦጦ እንዲሁም የአንድነትና የመስቀል አደባባይን ጨምሮ ሌሎች በስኬት የተጠናቀቁ አገራዊ ፕሮጀክቶችን ለአብነት ጠቅሰዋል።

በኢኮኖሚ፣ በእርሻ፣ በቱሪዝምና ሌሎች መስኮች የተከወኑ የሪፎርም ስራዎች ውጤት እያሳዩ መምጣታቸውን የገለፁት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የተጀመሩ የተግባር ልምድና እውቀት ስራዎችን ማስፋት ከተቻለ “ኢትዮጵያ ወደ ብልጽግና ማማ ትወጣለች” ብለዋል።

ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና ማድረስ የሚቻለው የተረኝነት አስተሳሰብን በማስወገድ በአንድ ልብ ተሳስሮ በጋራ መቆም ሲቻል ብቻ መሆኑንም አስገንዝበዋል።

መጪው አገራዊ ምርጫ ሠላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ብልጽግና መሠረት የሚጥል መሆኑንም ተናግረዋል።

ምርጫውን ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ በማድረግ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን አሸናፊ የሚሆኑበት ማድረግ እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት።

ለምርጫው ሠላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ሆኖ መጠናቀቅ ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

የብልጽግና ፓርቲ ማኒፌስቶ ሕብረ ብሔራዊ ፌዴራላዊ ስርዓት ላይ የተመሰረተ አገረ መንግስት የመገንባት ራዕይ አለው።

ከምግብ ዋስትና ጥያቄ የተሻገረ የዜጎችን የምርጫ አድማስ የሚያሰፋ የበለጸገ ኢኮኖሚ መገንባት፣ የሕዝቡን ፍላጎት የሚያሟላ ፍትሃዊ የማኅበራዊ አገልግሎት ስርዓት መዘርጋትም በማኒፌስቶው ተቀምጧል።

የኢትዮጵያን ጥቅምና የዜጎችን ክብር የሚያስጠብቅ የውጭ ግንኙነትና ተቋማት መገንባትም በማኒፌስቶው ከተቀመጡ አንኳር ነጥቦች መካከል ነው።

OBN

Exit mobile version