Site icon ETHIO12.COM

የምግብ ሸቀጦችን በድብቅ አከማችተው የተገኙ 197 የነጋዴ መጋዘኖች ታሸጉ

በምስራቅ ሐረርጌ ዞን የዋጋ ንረት እንዲፈጠር ዘይትና የተለያዩ የምግብ ፍጆታቸውን አከማችተው የተገኙ 197 የነጋዴ መጋዘኖች  እንዲታሸጉ መደረጉን  የዞኑ ንግድ ጽህፈት ቤት ገለጸ።

የጽህፈት ቤቱ ተወካይ አቶ መሐመድዚያድ ከድር እንዳሉት  በዞኑ በምግብ ሸቀጦች ላይ የሚስተዋለው  ህገ ወጥ ተግባር ለመከላከል የፍትህ አካላትና  ህብረት ስራ ማህበራት በአባልነት የሚገኙበት  ግብረ ሃይል አቋቁመው  ወደ ስራ ገብተዋል።

ግብረ ሃይሉ በአንድ ሳምንት ባከናወነው እንቅስቃሴም የምግብ ፍጆታ ሸቀጦችን በድብቅ የማከማቸት እና  ያልተገባ የዋጋ መጨመር ህገ ወጥ ድርጊት መታየቱን አስረድተዋል።

በዞኑ የተለያዩ አካባቢዎች  በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ በ197 መጋዘኖችን ውስጥ ዘይት፣ ስኳር፣ዱቄት፣ ሩዝ፣ማካሮኒንና  ሌሎች የምግብ ሸቀጦች  በህገ ወጥ መንገድ አካማችተው በመገኘታቸው እንዲታሸጉ መደረጉን ገልጸዋል።

በተለይ በሐረማያ ወረዳ አዴሌ ከተማ በሚገኝ 3 መጋዘኖች ውስጥ ግምቱ 30 ሚሊየን ብር የሚጠጋ ከ34ሺህ ሊትር በላይ  የምግብ  ዘይት፣1ሺህ 850 ኩንታል ሩዝ፣1ሺህ 450 ኩንታል ማካሮኒን፣300 ኩንታል ዱቄትና ሌሎችም የምግብ ሸቀጦች ተከማችተው ማገኘታቸውን ጠቅሰዋል።

የተሸጉ መጋዘኖች ባለቤቶች ላይ በአቃቢ ህግ በኩል ክስ በመመስረት ፍርድ ቤት በሚሰጠው ውሳኔ መሰረት  እርምጃ እንደሚወሰድባቸው ያመለከቱት  አቶ መሐመድዚያድ  ህገ ወጥ ተግባር የመቆጣጠርና ገበያውን የማረጋጋት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

የሐረማያ ወረዳ ንግድ ጽህፈት ቤት የቁጥጥርና ኢንስፔክሽን ባለሙያ አቶ ኤልያስ ኡስማን የፍጆታ ሸቀጦችን አለአግባብ  በመጋዘን  ያከማቹና የተጋነነ ዋጋ በጨመሩ ነጋዴዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ኢዜአ ዘገቧል።


Exit mobile version