ETHIO12.COM

በአዲስ አበባ ብልፅግናን በመወከል ለፓርላማ እና ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የሚወዳደሩ ዕጩዎችን ማስተዋወቂያ መርሃ ግብር ተካሄደ ።

በመርሃ ግብሩ ላይ ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ባስተላለፉት መልዕክት በለውጥ የተገኘው ብልፅግና የሁሉም ኢትዮጵያዊ ፓርቲ መሆኑን አስረድተዋል።

እጩዎቹ በግልፅ መስፈርት የተለዩ መሆኑን ያመላከቱት ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች በችግር ውስጥ ተፈትኖ ውጤት ማስመዝገብ፣ ባስመዘገቡት ውጤት እረክተው የማይቆሙ፣ ህዝብን ዝቅ ብሎ የማስተናገድ ስነምግባር ያላቸው፣ የፆታ የብሄር የእምነት ስብጥሮችን የጠበቁ ኢትዮጵያን የሚያንፀባርቁ መሆናቸውን አብራርተዋል።

ተወዳድሮ ከማሸነፍ በተጨማሪ እንደ መንግስት ምርጫው ዴሞክራሲያዊ ፣ ፍትሃዊና በህዝብ ዘንድ ታማኝነት ያለው የማድረግ ተጨማሪ ሃላፊነት እንዳላቸው የገለፁት ወ/ሮ አዳነች እጩዎቹ ቅርርባቸውን በማጠናከርና በመደጋገፍ
ለብልፅግና አሸናፊነት እንዲተጉም አሳስበዋል።

የአዲስ አበባ ብልፅግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መለሰ ዓለሙ በበኩላቸው መድረኩ ከምርጫ በፊት በተለያዩ የምርጫ ተግባራትና ስልቶች ላይ የጋራ ምክክር ለማድረግ ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ገልፀዋል።

6ተኛው አገር አቀፍ ምርጫ የፖለቲካ ምህዳሩ ሰፍቶ ተዋንያኑ በበዙበት፣ የዴሞክራሲ ተቋማትን በገለልተኛነት መምራት በተጀመረበት፣ ብልፅግና ውህድ አገራዊ ፓርቲ ሆኖ የአገራችን የዴሞክራሲ ስብራት ለመጠገን እየሰራ ነው ብለዋል ።

በተለይም በሚዲያው ዘርፍ ዜጎች ሁሉ ጋዜጠኛ እስከመሆን በደረሱበት፣ ጁንታው ቢወገድም እርዝራዦቹ ለጥፋት የሚረባረቡበት መሆኑ ለየት እንደሚያደርገው ኃላፊው አስረድተዋል።

በተጨማሪም የእጬዎች ዝግጅት በማዕከል የተዘጋጀውን መመሪያና የከተማችንን ልዩ ባህሪ ያገናዘበ መሆኑን የገለጹ አቶ መለሰ የእጩ ሂደቱ ህግን፣ ብቃትንና የህዝብ ተቀባይነትን እንዲሁም የተዋፅኦ መስፈርቶችን ያሟላና ከ500 ሺህ በላይ አባላትና ደጋፊዎች የተተቹ መሆኑንም አስረድተዋል።

እጩዎች ለሰርግ እንደታጨ/ች ሙሽራ ዝግጁ መሆንና የዕጩ ተመራጭነት ሚናቸውን እንዲወጡ አቶ መለሰ አሳስበዋል።
ለእጩዎች በቀጣይ ስልጠና እንደሚሰጣቸውና የጋራ ግንኙነት እንደሚኖራቸው የአዲስ አበባ ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት አስታውቋል።

Exit mobile version