Site icon ETHIO12.COM

ዶክተር አዲስ አለም ባሌማ፣ አቶ ስብሃት ነጋ፣ አምባሳደር አባይ እና ሌሎችም ተጠርጣሪዎች ማረሚያቤት እንዲወርዱ ታዘዘ

ዶክተር አዲስ አለም ባሌማ፣ አቶ ስብሃት ነጋ፣ አምባሳደር አባይ እና ሌሎችም ተጠርጣሪዎች ማረሚያቤት እንዲወርዱ ታዘዘ።

ተጠርጣሪዎቹ ማረሚያቤት እንዲወርዱ የታዘዘው ዐቃቤ ህግ በመዝገብ ቁጥር 220866 የቅድመ ምርመራ መዝገብ በመክፈቱ ተከትሎ በቂሊንጦ ማረሚያቤት እንዲወርዱ ያቀረበውን አቤቱታ ተከትሎ ነው።

ዛሬ ረፋድ ላይ ከወይዘሮ ኬሪያ ኢብራሂም ውጪ ያሉት ሁሉም ተጠርጣሪዎቹ በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ አንደኛ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት ቀርበው ጉዳያቸው ታይቷል።

ወይዘሮ ኬሪያ ኢብራሂም በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ህግ 28 መሰረት በዋስ መለቀቃቸው በችሎት ተገልጿል።

በዚህ ጊዜም የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ምርመራ ቡድን ተጠርጣሪዎቹ በተጠረጠሩበት ህገመንግስቱንና ህገመንግስታዊ ስርአቱን ለመናድ ሙከራ ወንጀል ሲከናወን የነበረውን ምርመራ ማጠናቀቁን ለችሎቱ አስታውቋል።

ዐቃቤ ህግ በችሎት ተገኝቶ በስነ ስርአት መዝገብ 5ኛ ተጠርጣሪ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት የነበሩት ወይዘሮ ሕርይቲ ምህረተአብ እና 8ኛ ተጠርጣሪ የክልሉ መንግስት አማካሪ የነበሩት ወልደጊዮርጊስ ደስታ እንዲሁም በእነ አምባሳደር አባይ ወልዱ መዝገብ 8 ተጠርጣሪ የክልሉ ቅሬታ ሰሚ ቢሮ ሃላፊ የነበሩት አቶ አምደማርያም ተፈራ፤ ወደ ፊት ምርመራ ቢደረግባቸው መቅረብ እንዲችሉ በቂ ዋስ ጠርተው ቢለቀቁ አልቃወም ማለቱን ተከትሎ ፍርድቤቱ እያንዳንዳቸው በ30 ሺህ ብር ዋስ እንዲወጡ አዟል።

ዐቃቤ ህግ በሌሎች ተጠርጣሪዎች ላይ ሕገ መንግስታዊ ስርዓትን በኃይል መናድ እና በሽብር ወንጀል ክስ እንደሚመሰርትባቸውም ለፍርድ ቤት ገልጿል፡፡

የቅድመ ምርመራ መዝገብ መክፈቱን ተከትሎ የጊዜ ቀጠሮ መዝገቡ እንዲዘጋለት እና ተጠርጣሪዎቹ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ ጠይቋል።

የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው በተጠርጣሪዎቹ ላይ የወንጀል ተሳትፏቸው ባልተለየበት ሁኔታ ቅድመ ምርመራ መዝገብ ተከፍቷል መባሉ አግባብነት የለውም የሚሉ መቃወሚያ ነጥቦችን አንስተው ተቃውመዋል።

ፍርድ ቤቱም ተሳትፏቸውን መዝገቡን አስቀርቦ ይመልከት በማለት ተጠርጣሪወቹ፥ በዋስ ወጥተው ቀዳሚ ምርመራ ሲሰማ መቅረብ ይችላሉ ሲሉ የዋስትና ጥያቄ አንስተዋል።’

ዐቃቤ ህግ በዋስ ይውጡልኝ ያላቸው ሶስቱ ተጠርጣሪዎችም ምንም ማስረጃ እንዳልተገኘባቸው በመጥቀስም፥ ስለዚህ በዋስ ሳይሆን በነጻ መሰናበት አለባቸው ሲሉም መቃወሚያ አቅርበዋል።

ዐቃቤ ህግም በተነሳው መቃወሚያ ላይ ምላሽ የሰጠ ሲሆን ለማሳያ የተወሰኑትን ተጠርጣሪዎች ተሳትፎ ለችሎቱ አብራርቷል።

1ኛ ተጠርጣሪ አቶ ስብሃት ነጋ ከግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን ጥገኛ መንግስት አያስፈልግም መወገድ አለበት በሚል በሃይል ለማስወገድ ስምምነት አድርገው የትግራይ ወታደራዊ ኮማንድ እና ዲፕሎማሲያዊ ቡድን በሚስጥር በማቋቋም በጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በሃገር መከላከያ ሰራዊት ላይ ጦርነት በመክፈት በርሃ ላይ መያዛቸውን ጠቅሷል።

2ኛ፡ 6ኛ፣ 7ኛ እና 9ኛ ተጠርጣሪዎች ማለትም በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አባባ ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊ የነበሩት ዶክተር ሰለሞን ኪዳኔ፣ የኤፈርት አመራር የነበሩት አምባሳደር አባዲ ዘሙ፣ የደደቢት ማይክሮ ፋይናንስ ሃላፊ ተክለወይኒ አሰፋ እና ሌሎችም ከሰኔ ወር 2012 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ወራት ሚስጥራዊ ኮሚቴ በማቋቋም ከምግብ ጀምሮ ለክልሉ ልዩ ሃይል ድጋፍ ሲያደርጉ እና ልዩ ሃይሉን ሲመሩ ነበር ያለው ዐቃቤ ህግ በተለይም ተክለወይኒ አሰፋ 50 ሚሊየን ብር ከደደቢት በማውጣት በረሃ ይዘው መሄዳቸውን ጠቅሷል፡፡

ነዳጅ ተዘርፎ መሬት ውስጥ ተቀብሮ መገኘቱንም አመላክቷል ዐቃቤ ህግ።

በዚህ ወንጀል የግፍ ግድያ መፈጸሙን፣ ቀዳሚ ምርመራ መደረጉ የግድ ነው ምስክሮቻችን ሊጠፉብን ስለሚችሉ መሰማት አለበት፣ በሃገራዊ ግዴታ ላይ ያሉ ምስክሮችም አሉን ብሏል ዐቃቤ ህግ።

በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርአት ህግ 63 ስለክስ እንደሚያስረዳ በመጥቀስ፥ በጠበቆች ዋስትና አያስከለክልም መባሉ ስህተት ነውም ብሏል፡፡

ከዚህ ባለፈም ሃገር ለማፍረስና ስልጣን በሃይል ለመያዝ ጦርነት ከፍተው የሰው ህይወት ማጥፋታቸውን በማንሳትም ይህም ዋስትና ያስከለክላል ሲል በዋስትና ጥያቄያቸው ላይ ማብራሪያ ሰጥቷል።

ጠበቆቻቸው በበኩላቸው ደንበኞቻቸው ቂሊንጦ ማረሚያቤት ለደህንነታቸው ያሰጋቸዋል ሲሉ አቤቱታ ያሰሙ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ማመልከቻ አቅርቡ ብሏል።

የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግም በአዲስ አባባ ማረሚያቤት እንዲቆዩ ፍርድ ቤቱ አዟል።

በታሪክ አዱኛ via FBC

Exit mobile version