Site icon ETHIO12.COM

“የውጭ መገናኛ ብዙኃንና የዲፕሎማቶች የትግራይ ጉብኝት የጁንታውን ፕሮፓጋንዳ ሐሰትነት አረጋግጧል”ተፎካካሪ ፓርቲዎች

(ኢዜአ) የውጭ መገናኛ ብዙኃንና ዲፕሎማቶች በትግራይ ያደረጉት ጉብኝት የጁንታው ፕሮፓጋንዳ ሐሰት መሆኑን ማረጋገጡን የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ገለጹ፡፡

አቶ የሺዋስ አሰፋ ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ /ኢዜማ/፣ ኢንጂነር ግደይ ዘርዓጽዮን ከትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /ትዴፓ/ እንዲሁም ዶክተር ያሬድ ተሾመ ከብልጽግና ፓርቲ በወቅታዊ ጉዳዮች ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡

የትዴፓ አማካሪ ኢንጂነር ግደይ ዘርዓጽዮን እንዳሉት መንግሥት የውጭ መገናኛ ብዙኃን ትግራይ ክልል ገብተው እንዲዘግቡ ማድረጉ ትክክለኛ አቋም ነው፡፡

መገናኛ ብዙኃኑ በክልሉ ያለውን እውነታ መዘገባቸው ጁንታው ክልሉን አስመልክቶ የሚያራግበው ፕሮፓጋንዳ እንደማይገናኝ አሳይቷል ብለዋል፡፡ 

ሆኖም መንግሥት አጥፊው ቡድን በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ማድረሱንና ሕግ ለማስከበር የተካሄደውን ዘመቻ ሂደት በተለያዩ መንገዶች ለዓለም ማሳየት እንደሚገባው አመልክተዋል፡፡

የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር ዶክተር ያሬድ ተሾመም አንዳንድ የውጭ መገናኛ ብዙኃን ያስተላለፏቸው አሉታዊ ዘገባዎች መሬት ላይ ያሉ ሳይሆኑ መገናኛ ብዙኃኑ የሚገኙባቸው አገራት በኢትዮጵያ ላይ ያላቸውን አቋም ያሳዩ እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡

አንዳንድ ዲፕሎማቶችና መገናኛ ብዙኃን ወደ ክልሉ ያቀኑት እንደተፈለገው ለሕዝቡ ሠብዓዊ ድጋፍ ለማቅረብ ሳይሆን ሌላ ዓላማ አንግበው እንደሆነም ነው የተናገሩት፡፡

አብዛኞቹ መገናኛ ብዙኃንና ዲፕሎማቶች ግን የክልሉን ትክክለኛ ገጽታ ማሳየታቸውን ዶክተር ያሬድ ጠቅሰዋል፡፡

ኢንጂነር ግደይ አንዳንድ ምዕራባዊያን አገራት የራሳቸውን ፍላጎት ለማሟላት በኢትዮጵያና በሕዝቦቿ ላይ ተጽዕኖ ለማድረግ እንደሚሞክሩም ጠቁመዋል፡፡

ለዚህም “ኢትዮጵያ የሱዳን ጦር ወደ ድንበሬ አልፎ ገብቷል” ብላ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ብታሳውቅም በርካታ ምዕራባዊያን አገራት ትኩረት አለመስጠታቸውን በማሳያነት አቅርበዋል፡፡

ኢትዮጵያዊያን ሁኔታውን በመገንዘብ የአገሪቷን ሉዓላዊነት ለማስከበርና ጥቅሟን ለማስጠበቅ መቆም እንደሚጠበቅባቸውም ኢንጂነር ግደይ አመልክተዋል፡፡

የኢዜማ ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ አሠፋ በበኩላቸው በኢትዮጵያ ጉዳይ አሉታዊ አስተሳሰብ ያላቸው አገራት እንዳሉ ሁሉ እንደ ሩሲያ፣ ሕንድና ቻይና ደግሞ ከጎኗ መቆማቸውን ተናግረዋል፡፡

አገራቱ በኢትዮጵያ ላይ የሚያራምዱት አቋም ጣልቃ ገብነት መሆኑን እንደመሰከሩ ገልጸው፤ ኢትዮጵያ እውነትና ፍትህን በመያዟ ሁሌም አሸናፊ ናት ብለዋል፡፡

Via – ENA

Exit mobile version