Site icon ETHIO12.COM

የአዳም የማምረቻ መሳሪያዎች ፋብሪካ 1.9 ቢሊዮን ብር በትኖ መሰብሰብ አልቻለም

የአዳማ የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪ ያጋጠሙትን ችግሮች በፍጥነት ፈትቶ አርሶ-አደሩ የቴክኖሎጅ ተጠቃሚ እንዲሆን መስራት እንዳለበት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገቢ፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። የአርሶ-አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ ችግሩን መፍታት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ማምረቻ ኢንዱስትሪው ለሰባት አመታት በዱቤ ሸጦ ያልሰበሰበው ገንዘብ ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል፤ የእርሻ መሳሪያ ክምችቱ በገንዘብ ሲገመት ከ3 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ይዘው መቀመጣቸው ተገልጿል፡፡

ኮሚቴው በአዳማ የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪ የስራ እንቅስቃሴን አስመልክቶ የመስክ ምልከታ አካሂዷል።በምልከታውም የተሰብሳቢ ሂሳቦች ወቅታቸውን ጠብቀው አለመሰብሰባቸው፣ የእርሻ መሳሪያዎች ሃብት ክምችት ወደ ግብርናው ክፍለ-ኢኮኖሚ አለመድረሱ፣ አርሶ-አደሩ በቴክኖሎጅ ታግዞ ስራውን መስራት እንዳልቻለ የቡድኑ አስተባባሪ አቶ አያሌው አይዛ ተናግረዋል፡፡ማምረቻ ኢንዱስትሪው ለሰባት አመታት በዱቤ ሸጦ ያልሰበሰበው ገንዘብ ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል፤ የእርሻ መሳሪያ ክምችቱ በገንዘብ ሲገመት ከ3 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ይዘው መቀመጣቸው ተገልጿል፡፡

የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪው ባጋጠሙት ችግሮች ቴክኖሎጂን ወደ አርሶ አደሩ ማድረስ ላይ አፈጻጸሙ ዝቅተኛ መሆኑን አስተባባሪው ጠቅሰው፣ ከውጭ ወደ ሃገር ከገቡ የቆዩና በቂ መለዋወጫ የሌላቸው ትራክተሮች መኖራቸውን አቶ አያሌው ተናግረዋል። የማምረቻ ኢንዱስትሪው ያጋጠሙትን ችግሮች በፍጥነት ፈትቶ አርሶ-አደሩ የቴክኖሎጅ ተጠቃሚ እንዲሆን ቋሚ ኮሚቴው አስፈላጊውን እገዛ እንደሚያደርግላቸው አስተባባሪው ጠቅሰዋል ፡፡

የኢንዱስትሪው ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ድሪባ ሁንዴ በበኩላቸው የእርሻ መሣሪያዎቹ ሲገዙ ተጨባጭ የሀገሪቱን መልክዓ-ምድር ነባራዊ ሁኔታ ላይ ጥናት ሳይደረግ ግዥ መከናወኑ ቴክኖሎጅዎቹ ወደ አርሶ- አደሩ አለመሰራጨታቸውን ገልጸዋል፡፡የተገዙት የትራክተር ተቀጽላዎች የጥራት ችግር ያለባቸውና ከትራክተሮች ቁጥር ጋር በአሃዝ ተመጣጣኝ አለመሆናቸውንም አቶ ድሪባ ተናግረዋል። ችግሮቹን ከሚመለከተው አካል ጋር በመወያየት ፈትተው የአርሶ-አደሩን የቴክኖሎጅ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰሩ መናገራቸውን ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

EPD

Exit mobile version