Site icon ETHIO12.COM

አብን በክልሉ ክተት አወጀ – ” ተፈጥሯዊ ራስን የመከላከል መብትህን ተጠቀም” ብሏል፤ የክልሉ መንግስት ይጠበቃል

“ሕዝባችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጋረጠበትን መንግስታዊ ሽብር በተደራጀ አግባብ እንዲከላከል ጥሪ እናቀርባለን!” የሚለው የአብን ክተት የአማራ ክልል መንግስትን ” ከተፈጥሯዊውና መደበኛው የታዛዥነት መንፈስ ያልወጣ” ሲል በገሃድ ያንኳሠዋል። አብን ያስተላለፈው ክተት ኦሮሚያ ብልጽግናን ጠቅሶ ተጠያቂ ያደርጋል። በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ከኦነግ ሸኔ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው ጠቅሶ ወንጅሏቸዋል። “እጣፋንታችንን በራሳችን እጆች እንጽፋለን! ” ብሏል።

” አብን የአማራ ሕዝብ ትግል ከተለመደው አካሄድ ተላቆ ኅልውናውን የመታደግና የማስከበር የተቀናጀና የተጠናከረ የትግል ምዕራፍ ውስጥ መግባት አለበት የሚል ድምዳሜ ደርሷል። ትግሉንም ለመምራት ንቅናቄያችን ከፊት ይሰለፋል” ያለው አብን ” ከመድበኛው አካሄድ ተላቆ” ያለውን በግልጽ ስም ጠርቶ አላብራራም። ነገር ግን ሕዝቡ “የተፈጥሮ መብቱን” ይጠቀም ሲል ጥሪ አቅርቧል። ” እጣፋንታችንን በራሳችን እጆች እንጽፋለን! ” ያለውን ግን አላብራራውም።

“መላው የአማራ ሕዝብም የተከፈተበትን አጠቃላይ የኅልውና አደጋ በመገንዘብ እና ለደኅንነቱ የሚያስብለት መንግስት እንደሌለው በመረዳት ራሱን የመከላከል ተፈጥሯዊ መብቱን እንዲሰራበት አብን በአጽንዖት ያሳስባል። ሕዝባችንም በዚህ ፈታኝ ወቅትም ወዳጅ መስለው በጠላትነት በቆሙ ቡድኖችና ግለሰቦች ግፊት ፈተና ላይ እንዲወድቅ የሚፈለገውን አንድነቱን አጠናክሮ እንዲጠብቅ እናሳስባለን” ይላል አብን።



አማራ የሚያስብለት መንግስት እንደሌለ ጠቅሶ ህዝቡ የተፈጥሯዊ መብቱን በመጠቀም ራሱን እንዲከላከል ከተት ያወጀው አብን፣ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ድጋፍ እንዲያደርግ ተማጽኗል።

አብን የሰሜን ሸዋውን የከፋ የተባለ ወረራና እልቂት ተከትሎ ህዝቡ ራሱን እንዲከላከል ጥሪ ከማቅረቡ በፊት፣ ዳግም ያገረሸው እልቂት ከመካሄዱ አስቀድሞ የባልደራስ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ኤርሚያስ ለገሰ ” ጄኖሳይድ እንዳይደርስ የመከላከል ንቅናቄ” በሚል ርዕስ በ360 አማካይነት ሰፊ ማብራሪያ ሲያቀርብ እንደነበር ይታወሳል። አብንና ባልደራስ በጥምረት እየሰሩ ያሉ ድርጅቶች መሆናቸውም አይዘነጋም።

በተደጋጋሚ ወቀሳ የሚሰነዘርበት የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ጉዳዩን አስመልክቶ እስካሁን የሰጠው መግለጫ የለም። ይሁን እንጂ የድርጅቱ መሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ቀደም ሲል “የኦነግ ከፍተኛ አመራሮች እንዳይታሰሩ አስቀድሜ መረጃ ሰጥቻለሁ” በሚል በገሃድ መናገራቸውን እንደ አንድ መነሻ ዋቢ አድርጎ ” ኦነግ ሸኔን ይመራሉ” ሲል አብን መክሰሱ ጉዳዩን ሊያካርረው እንደሚችል ተገምቷል።

የአማራ ክልል ለዓመታት መሬቱን ተነጥቆ፣ በተነጠቀው መሬት አማራ መሆን እንደ ነውር ተቆጥሮ መከራ ሲደርስባቸው የነበሩ የህብረተሰብ ክፍሎችንና ” ተነጠቀ” የተባለውን መሬት እንዲመለስ፣ ህዝቡም ነጻ እንዲወጣ፣ ከዛም አልፎ ህጋዊ ይዘት እንዲኖረው አመራር እያሰጡ ያሉ መሪን በዚህ ደረጃ አውርዶ ከአንድ ሽፍታ ቡድን ጋር ማመሳሰል ተቀባይነት እንደሌለው አስተያየት የሰጡ ገልጸዋል።

“አብን ጉዳዩን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው” ቢልም አጣዬ ነዋሪ የሆኑ ለቢቢሲ አማርኛ ” ጥቃቱን የፈጸሙት ኦነግ ሸኔና ሌሎቹ ህወሃቶች ናቸው ” ምስክር መሆናቸውን የሚጠቁሙ የአብን ክስ “ጠቅላይ ሚኒስትሩና ህወሃት አብረው እየሰሩ ነው” ብሎ እንደመፈረጅ መሆኑንን ገልጸዋል። አያይዘውም በሰሜን ሸዋ የሆነው ሁሉ የሚወገዝ፣ የሚያስጠይቅ፣ ስሜት የሚነካ መሆኑ ለክርክር የሚበቃ ባይሆንም፣ መግለጫው ” እረኛውን ምታ መንጎቹ ይበተናሉ” የሚለውን የትህነግ መፈክር ያጎላና አጋጣሚውን ለተፈጠሩበት ዓላማ ማዋላቸውም የታየበት እንደሆነ አስተያየት ሰጪው ገልጸዋል። አብን በአማራ ክልል አመራሮች ግድያ እጁ እንዳለበት በስፋት የሚነገርበትና ልክ እንደ ኦነግ ሁሉ ጽንፈኘት መገለጫው ነው የሚባል ድርጀት እንደሆን በርካቶች ይናገራሉ። መግለጫው ሙሉውን እንደሚከተለው ይነበባል። አብን ያወጣውን የክተት ጥሪ አስመልክቶ የክልሉ መሪ ድርጅት ያለው ነገር የለም።

ሕዝባችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጋረጠበትን መንግስታዊ ሽብር በተደራጀ አግባብ እንዲከላከል ጥሪ እናቀርባለን!

ድርጅታችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን) በአንድ በኩል በሕዝባችን ላይ ለበርካታ አስርተ ዓመታት የቀጠለውን ሕግና መዋቅር ሰራሽ የፖለቲካ ሸፍጥ በዘላቂነት ለመቅረፍ፣ በሌላ በኩል ሕዝባችንና አገራችን ከተጋረጠባቸው የኅልውና አደጋዎች ለመታደግ በሚደረገው አገራዊ የበጎ ኃይሎች ጥምረት አካል በመሆንና በትጋት በመስራት ላይ የሚገኝ መሆኑን በኃቅ የሚፈርድ ሁሉ የሚረዳው እውነታ ነው።

ምንም እንኳን ትጋታችን ለማንም አካል በመታያነት የቀረበ ባይሆንም፣ እጅግ ፈታኝ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ እንኳ ሆነን «የተሻለ ነገ» ሊመጣ ይችላል የሚል እሳቤን አንግበን እዚህ ደርሰናል። ቀደም ሲል በተደጋጋሚ ለመንግስት እንዳሳሰብነው መሰረታዊ የሆኑ የለውጥ ኃሳቦችን መሬት ለማስረገጥና የተሳሳተውን የማደራጃ ትርክት፣ የተዛነፈውን መዋቅራዊና ሥርዓታዊ ማእቀፍ በማስተካከል ሕዝብን ለዘላቂ ሰላምና ሥልጣን ለማብቃት የበኩላችንን ያልተቋረጠ ጥረት ከማድረግ ጎን ለጎን በተለይ አገራችንና ማዕከላዊ ሥርዓቱ እንዳይፈርሱ ለማድረግ በተደረጉ ጥረቶች ሁሉ አብንና የአማራ ሕዝብ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል። ሆኖም፦

1/ መንግስታዊ ሽብሩን በማባባስ፣ በመደገፍ እና ትእዛዝ በመስጠት ጭምር የሚሳተፉት የአገራችን ጠቅላይ ሚንስቴርና የሚመሩት የኦሮሞ ብልጽግና ክፍል መንግስታዊ መዋቅርንና የአገር ኃብትን በመጠቀም የአማራን ሕዝብ የማሸበር ተግባር አጠናክረው ቀጥለዋል። ሕዝባችንን ለማሸበር የተከፈተው መጠነ-ሰፊ የዘር ፍጅት በመንግስት መዋቅር በቀጥታ የሚደገፍና የሚመራ መሆኑን አብን ያምናል። ለዚህም የሚከተሉትን ነጥቦች በጉልህ ማሳያነት ማቅረብ ይቻላል።

ሀ/ በአማራ ሕዝብ ላይ የተቀናጁ የጅምላ ፍጅት ጥቃቶችን የከፈተው በተለምዶ «ኦነግ ሸኔ» ተብሎ በጠቅላይ ሚንስትሩ የሚጠራው አካል ከመነሻው ከነትጥቁ ወደ አገር ቤት የገባበትን አሻጥር፣

ለ/ ከዚያ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጭምር እንደገለጹት ከተጠቀሰው ድርጅት ጋር የነበራቸው መረጃን የመለዋወጥ ድብቅ ግንኙነት የሚታወቅ በመሆኑ ከልጅነት እስከ እውቀት አጋር የሆናቸውን ድርጅት አሁንም በልዩ ስልት የማደራጀት፣ የመደገፍ እና የመንከባከብ ሚናቸውን እየተጫወቱ እንደሆነ ንቅናቄያችን በጽኑ ያምናል።

ሐ/ የ«ኦነግ ሸኔ» ኮር ስትራቴጂክ አመራር በመሐል አዲስ አበባ ውስጥ ተቀምጦ እየመራ ባንኮችን ጭምር በጠራራ ፀሐይ በመዝረፍ ኃይል እንዲያጎለብት የተፈቀደበትና የተመቻቸበት አግባብ መኖሩ፣

መ/ በአማራ ሕዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለውን ተደጋጋሚ የዘር ጥቃት ማስቆም ይቅርና ጅምላ ፍጅቱ በአገር ደረጃ ለኃዘን መግለጫ እንኳ እንዳይበቃ የተደረገ ከመሆኑም በላይ በኃዘን ድንኳናችን ላይ ቀይ ምንጣፍ አንጥፈው ሕንፃ እና አበባ የሚመርቁበት አስደንጋጭ ማኅበራዊ ስላቅ ሳይቋረጥ መቀጠሉ፤

ሠ/ በአማራ ሕዝብ ላይ የተከፈተው ዘር ተኮር ጥቃት የታቀደና የተቀናጀ ሲሆን የመንግስት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጭምር የዘር ማጥፍት ወንጀል ለማስፈጸም አመላካች የሆኑ የመግቢያ ንግግሮችን በይፋ ሲያሰሙ መቆይታቸውና ለዚህም ምንም አይነት አስተዳደራዊም ይሁን ፖለቲካዊ እርምት አለመሰጠቱ፤ጠቅላይ ሚንስትሩና የሚመሩት መንግሥት በዚህ የአማራን ሕዝብ የማሸበርና የዘር ፍጅት እንቅስቃሴ ውስጥ ሚና አላቸው ብሎ ንቅናቄያችን ለማመን ተገዷል።

2/ የአማራ ክልል መንግስት ከተፈጥሯዊውና መደበኛው የታዛዥነት መንፈስ አለመውጣቱ፣ ደንታ ቢስነቱና አቅመ ቢስነቱም እየበረቱበት መሆኑ ሕዝባችንን አቻ ለማይገኝለት ማኅበራዊ ውርደት ያበቃ በመሆኑ፤አብን የአማራ ሕዝብ ትግል ከተለመደው አካሄድ ተላቆ ኅልውናውን የመታደግና የማስከበር የተቀናጀና የተጠናከረ የትግል ምእራፍ ውስጥ መግባት አለበት የሚል ድምዳሜ ደርሷል። ትግሉንም ለመምራት ንቅናቄያችን ከፊት ይሰለፋል።መላው የአማራ ሕዝብም የተከፈተበትን አጠቃላይ የኅልውና አደጋ በመገንዘብ እና ለደኅንነቱ የሚያስብለት መንግስት እንደሌለው በመረዳት ራሱን የመከላከል ተፈጥሯዊ መብቱን እንዲሰራበት አብን በአጽንዖት ያሳስባል።

ሕዝባችንም በዚህ ፈታኝ ወቅትም ወዳጅ መስለው በጠላትነት በቆሙ ቡድኖችና ግለሰቦች ግፊት ፈተና ላይ እንዲወድቅ የሚፈለገውን አንድነቱን አጠናክሮ እንዲጠብቅ እናሳስባለን።በአገር ውስጥም ይሁን በውጭ አገራት የምትገኙ ወገን ወዳድ ኢትዬጵያውያን በመሰረቱ ያንዣበበው አደጋ በአማራ ሕዝብ ላይ ብቻ ተወስኖ የሚቆም አለመሆኑን በመገንዘብ በአማራ ሕዝብ ላይ በተቀናጀ ሁኔታ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ጥቃት እንድታወግዙና የመልሶ ማቋቋም ሥራዎችን እንድታግዙ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን። በተለያዩ ስምሪቶች በቅንነት አገራችሁን የደገፋችሁ መስሏችሁ ለሥርዓቱ እገዛ የምታደርጉ ወገኖች ሂደቱን በመገምገም ጥያቄ እንድታነሱና ከተገፉ ወገኖች ጎን እንደትሰለፉ ጥሪ እናቀርባለን።

በአገር ውስጥም ይሁን በውጭ አገራት የምትኖሩ የአማራ ተወላጆች በእያንዳንዱ ቀን የአማራ ሕዝብ ደም እንደጅረት የሚፈስበት አገር መሆኑን በመረዳት፣ አማራው ለአጠቃላይ የኅልውና አደጋ የተጋለጠ መሆኑን በመቀበልና መሰረተ ቢስና መናኛ ከሆኑና የሞራልና የታሪክ ተጠያቂነት ከሚያስከትሉ ልማዳዊ የፖለቲካ ዘይቤዎች በአስቸኳይ በመላቀቅ ሰብዓዊ፣ ወገናዊና ኃቀኛ የሆነ የፖለቲካ አቋም በመውሰድ ሕዝብ የመታደግ ድርሻችሁን እንድትወጡ የሚል ታሪካዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

ኅልውናችንን በትግላችን እናስከበራለን!

እጣፋንታችንን በራሳችን እጆች እንጽፋለን!

ክልሉ አጋጣሚውን ለፖለቲካ ገበያ ለማዋል የሚጠቀሙ እንዳሉ አመልክቷል። የደረሰውን በድለም ዘርዝሯል። የአማራ ህዝብ አንግ እንዲሆን አመልክቷል።

Exit mobile version