Site icon ETHIO12.COM

መንግስት እና የፖለቲካ ፓርቲዎች ለሰላም በሃላፊነት ስሜት እንዲንቀሳቀሱ የኢ/ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ጥሪ አቀረበ

ሰርቶ ለመኖር ቅድሚያ የሀገርን ሰላም ማስጠበቅ ተገቢ በመሆኑ መንግስት እና የፖለቲካ ፓርቲዎች በሃላፊነት ስሜት እንዲንቀሳቀሱ የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ጥሪ አቅርቧል።

የኮንፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ በሰጡት መግለጫ የተረጋጋ ኢንዱስትሪን በመፍጠር እና ምርታማነትን በማረጋገጥ ሀገርን ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ በቅድሚያ ሰላምን ማስፈን ይገባል ብለዋል።
በትግራይ ክልል በነበረው የህግ ማስከበር ሂደት በግል ድርጅቶች ላይ በደረሰው ከፍተኛ ጉዳት ሳቢያ በርካታ ሰራተኞች ከስራ ገበታቸው እንዳራቀ ያነሱት ፕሬዝዳንቱ መንግስት ችግር ላይ ለሚገኙ ሰራተኞች ድጋፍ እንዲያደርግ እና የመልሶ ማቋቋም ስራ እንዲሰራ ጥሪ አቅርበዋል።

በሌላ በኩል ኮንፌዴሬሽኑ ሰራተኞች በግል ድርጅቶች በተለይም በኢንዱስትሪ ፓርኮች መብት እና ጥቅማቸው እየተከበረ አለመሆኑን አንስቷል።

በስራ ቦታ ደህንነት እና ጤናን ለመጠበቅ የወጡ ህጎችም በአሰሪዎች እየተተገበሩ አለመሆኑንም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

በሌላ በኩል ኮንፌዴሬሽኑ በ6ኛው ሃገራዊ ምርጫ ሰራተኞች ዲሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀም የመራጮች ካርድ ከወዲሁ እንዲወስዱም አሳስቧል።

ኮንፌዴሬሽኑ እነዚህን መልክቶች በማንገብ ሚያዚያ 23 በኢትዮጵያ ለ44ኛ ጊዜ የሰራተኞች ቀንን (ሜይዴይ) እንደሚከበርም አስታውቋል።

በበአሉ ከዚህ ቀደም ለሰራተኞች መብት መከበር መስዋት የሆኑ ቀደምት ሰራተኞች የሚዘከሩ ሲሆን የእለቱ መሪ ሃሳብም በመደራጀት ለሰላምና ለምርታማነት እንስራ የሚል ነው። Via EBC

Exit mobile version