Site icon ETHIO12.COM

ከብሔራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

በዓለም ላይ ያለው ጨለማ ሁሉ የአንዲት ሻማን ብርሃን ሊያጠፋ አይቻለውም። የፈተናዎች ብዛትም የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ አያስቆመውም። የቤታችን ጉዳይ የቤታችን ብቻ ነው። በርዘግተን፣ ማዕድ ከብበን እንፈታዋለን። የቤታችን ጉዳይ አደባባይ ላይ አስጥተን ለጠላት መምቻ፣ ለጎረቤት መተረቻ፣ የምናቀብል ሞኞች አንሆንም። የኢትዮጵያን ጥንካሬና ልዕልና ላለማየት የተሳሉ ብዙዎች የቻሉትን ጫና ሁሉ እያጎረፉት ነው።

የተከበራችሁ የሀገራችን ሕዝቦች፣የሀገራችን ችግሮች ተናጥላዊ አይደሉም። ውስብስብና የተሣሠሩ ናቸው። ፖለቲካው ከኢኮኖሚው፣ ዲፕሎማሲው ከማኅበራዊጉዳዮቻችን ጋር ጥብቅ ቁርኝት አላቸው።ሀገራችን ቀደም ባሉት ጊዜያት ተከታታይ ዕድገቶችን ማስመዝገብ ብትችልም ዕድገቱ የመጣበት መንገድ ጤና ባለመሆኑ የዕድገት ጥራት ጉድለት ዋነኛው ችግራችን ሆኖ ቆይቷል።

በዚህ የተነሣ የኢኮኖሚያችን ምርታማነት በጣም ዝቅተኛ ነው፤ ዜጎች ከዕድገቱ በቂ ጥቅም ሊያገኙበት ቀርቶ የፈሰሰበትን መዋዕለ ንዋይ በበቂ አልመለሰም።በአኃዝ የተጠቀሰው ዕድገትም በብድር ጫና ምክንያት ራሱን ማስቀጠል አልቻለም።ለውጡን ተከትሎ በወሰድነው ርምጃ ኢኮኖሚው ዜጎችን በፍትሐዊነት ተጠቃሚ እንዲያደርግ፣ ዕድገቱ በእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ጎጆ ውስጥ እንዲገባ፣ በብልሹ አሠራርና በዘፈቀደ የባከነው የሀገራችን ሀብት በጥብቅ ቁጥጥርና የፕሮጀክት አፈጻጸም ዲሲፕሊን እንዲመራ፣ በዕዳ ጫና ተንገራግጮ የቆመው ኢኮኖሚ ከገባበት ማጥ ተመንጥቆ እንዲወጣ፣ የተራገፈው የሀገራችን ካዝና እንዲሞላ ግልጽ ግቦችን አስቀምጠን፤ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ቀርጸን ተንቀሳቅሰናል።አሁን በዕዳ ጫና ጎብጣ የነበረች ሀገራችን በመጠኑ ቀና ብላለች።

በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሊቆም የደረሰው ኢኮኖሚያችን ሞተሩ መንቀሳቀስ ጀምሯል።በስግብግብነት ሰፊ የሀገር ሀብት እየተመዘበረባቸው በአደባባይ ምንም ሳይሠሩ ሸረሪት ያደራባቸው ፕሮጀክቶች ነፍስ ዘርተው ወደ ፍጻሜ እየደረሱ ነው። ተኮላሽተው የነበሩ እንደ ሕዳሴ ግድብ እና ስኳር ፋብሪካዎች የመሳሰሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶቻችን በጥብቅ ግምገማና ዲስፕሊን ግንባታቸው ተቀላጥፏል።     ተንገራግጮ የቆመው ኢኮኖሚያችን እጅግአስቸጋሪ የነበረውን ጊዜ አልፎ፣ በዘርፉ መሪዎች ጥንቃቄና በዜጎች ትብብር ወደ ጎዳናው ማስገባት ችለናል።

በተለይም ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በተመደበው ጊዜና ሀብት የማጠናቀቅ ልምድ በሀገራችን እንዲፈጠር፣ ያቀዱትን የማሳካት ጉዳይ ተቋማዊም ሀገራዊም የባህል መሠረት እንዲኖረው ሰፊ ሥራዎች ተሠርተዋል። ኢትዮጵያ ሐሳብ የሚወጠንባት ብቻ ሳትሆን የሚተገበርባት፣ ሥራዎች ተጀምረው የሚጠናቀቁባት ሀገር እየሆነች መምጣቷን እያየን ነው።የተበላሸውን ማረም፣ የተደፋውን ማቃናት ብቻውን ሀገራችንን ከኋላቀርነት ሊያላቅቃትና ወደ ብልጽግና ማማ ሊያደርሳት አይችልም።

ቀና ብሎ ትልቁን ሕልም አይቶ፣ በሩቁ አልሞ፣ ረጅሙን ተራራ ለመውጣት ድፍረትና ወኔ፣ ቁርጠኝነትና ጽናት ይጠይቃል። ይህም የተደፋውን ከማቃናትና፣ የተበላሸውን ከማረም ይጀምራል። ከዚያም ወደ ነገ የሚያሻግረንን፣ ለልጆቻችን የበለጸገችና የሚኮሩባት ኢትዮጵያን የሚያስረክብልንን የብልጽግና ዕቅድ ማለም ይገባናል።ሕልሞች ሩቅ በመሆናቸው እስክንደርስ ድረስ ለቅርብ ተመልካቾች አይታዩም። ግቦቻችን ውስብስብ ስለሆኑ ቀላሉን ለሚያሳድዱ ወንድሞቻችን በቀላሉ አይረጋገጡም። የቱሪዝም ሴክተሩ መነቃቃት እንዳለበትና ሀገራችን ያላትን በቱሪዝም የመልማት ዕምቅ ዐቅም መጠቀም እንደሚያስፈልግ ብዙዎች ይስማማሉ።ሴክተሩ እስከዛሬ ውል በሌለው ገመድ ተተብትቦ አመርቂ ውጤት ሊያመጣ አልቻለም።

ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ሀገራችን ብዙዎች በምኞት የሚጎበኟትና በቱሪዝም ዘርፍ ከአፍሪካ ግንባር ቀደም ለማድረግ ዘርፉን የሚያነቃቁ በርካታ ፕሮጀክቶች ተሠርተዋል፤ ሊሆኑ አይችሉም የተባሉ ሕልሞች እውን መሆን ጀምረዋል። በአዲስ አበባና በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ተግባራዊ በመሆን ላይ ናቸው።

የሀገራችንን ኋላ ቀር የግብርና ምርት ሂደት መቀየርና እስከዛሬ ያልተጠቀምንባቸውን መሬቶች ወደ ምርት ሂደት ማስገባት የኢኮኖሚ ማሻሻያ አንዱ ግባችን ነበር። በዝናብ ላይ ጥገኛ ከሆነውና በዓመት አንዴ በማምረት ብዙ መሬትና ዐቅም ከሚያባክነውዘልማዳዊ አሠራራችን ተላቅቀን ኢትዮጵያ ስንዴ ከውጭ የምትገዛበትን ሁኔታ ለመቀየር ቆርጠን ሠርተናል። በዚህም መሠረት ከመቶ አርባ አምስት ሺህ ሄክታር በላይ መሬቶችን በስንዴ በማልማት ሕልማችን ከግቡ እንደሚደርስ በአጭር ጊዜ ውስጥ አረጋግጠናል።

ዘርፉ የተተበተበበትን የግብዓት አቅርቦት በመፍታት፣ ዘመናዊ የእርሻ ቴክኖሎጂዎችን በማቅረብ፣ እርጥበትን በአግባቡ በመጠቀም እና በኩታ ገጠም በማምረት ግብርናን ለማዘመን የያዝነው ዕቅድ ተስፋ ሰጭ ውጤቶችን ማስመዝገብ ጀምሯል።ውድ ኢትዮጵያውያን፣ ከለውጡ ማግሥት ከገጠሙን ፈተናዎች መካከል እነዚህ ሦስቱ ይጠቀሳሉ።

የዓለምን ኢኮኖሚ ያንኮታኮተው የኮቪድ-19 ወረርሽኝ፣ በሀገራችንና በቀጣናው ተከሥቶ ከፍተኛ እህል ያወደመው የአንበጣ መንጋ፣ በሕግ አልገዛም ያሉ እብሪተኞች በሁሉም አቅጣጫ የከፍቱት ጦርነት።ሌሎችም ፈተናዎች ነበሩ። ሆኖም የኮቪድ አደጋንም ሆነ ሌሎች ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎችን ለመቋቋም በጥንቃቄና በተጠና መንገድ ኢኮኖሚያዊ ርምጃዎችን ለመውሰድ ችለናል። በዚህም ምክንያት ፈተናዎችን መቋቋም ብቻ ሳይሆን ለረጅም ጊዜ ማነቆ የነበሩብንን ኢኮኖሚያዊ ችግሮች መፍታት መቻላችንን የሚያረጋግጡ በርካታ ድሎች አስመዝግበናል።ለአብነት ያክልም፣ እጅግ አነስተኛ የሆነው የሀገር ውስጥ ቁጠባ አድጓል።

በዚህም በተደጋጋሚ ዓመታት በጥሬ ገንዘብ እጥረት ሲፈተን የነበረውን የኢኮኖሚ ችግር እየቀረፍን መጥተናል። ይህም ከፍተኛ ብድርን ለግሉ ዘርፍ ማቅረብ እንድንችል አድርጎናል።የወጪ ንግድ በተከታታይ ዓመታት ከነበረበት የቁልቁለት ጉዞ በመውጣት ከአምና ጀምሮ ወደ ተከታታይ ዓመታት እድገት ገብቷል።ዘንድሮ የ21 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ ለመጀመሪያ ጊዜ አሥረኛው ወር ላይ ሳይደረስ የወጪ ንግድ ገቢ ከ2 ቢልዮን ዶላር ሊሻገር ችሏል። ይህም ካፈው ዓመት የ10 ወራት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የ17 በመቶ ብልጫ አለው።

የሥራ ዕድል ፈጠራ ከግሉ ሴክተር መነቃቃት ጋር እንዲሁም የቆሙ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ ከመግባታቸው ጋር ተያይዞ ከፍተኛ ዕድገትን እያስመዘገበ ይገኛል።የኢኮኖሚው ችግሮችን ለማረም ባደረግነው ከፍተኛ ጥረት አብዛኛው የዓለም የኢኮኖሚ ዕድገት ከዜሮ በታች በሆነበት ጊዜ፣ የሀገራችን ኢኮኖሚ አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በመቋቋም አዎንታዊ ዕድገት ለማስመዝገብ ችሏል። ያም ሆኖ፣ የተለያዩ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች በኢኮኖሚው ላይ ጫና ሳይፈጥርበት አልፏል ማለት አይቻልም። በተለያዩ የመፍትሔ አማራጮች ተጽዕኖችን ለማጥፋት ቢሞከርም ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ግን አልተቻለም።

ከተጽዕኖዎቹ አንዱ የዋጋ ንረት ነው። የዋጋ ንረት ለረጅም ጊዜ የሀገራችን ኢኮኖሚ ችግር ሆኖ ቆይቷል። የገጠሙንንን ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ፈተናዎችን ተቋቁመን፣ የኑሮ ውድነት ሕዝባችንን አደጋ ላይ እንዳይጥለው ለማድረግ፣ ፈተናዎቹ ከተከሠቱባቸው ቀናት ጀምሮ አስፈላጊዎቹን ርምጃዎች ሁሉ ስንወስድ ነበር።ሆኖም ችግሩ ከሀገራዊና ከዓለም አቀፍ ችግሮች ጋር የተገናኘ በመሆኑ ችግሩን ተቆጣጥረን ለመቆየት ያደረግነው ጥረት የምንፈልገውን ያክል ውጤታማ ሆኖ አልተገኘም።

ይህም በሕዝባችን ኑሮ ላይየፈጠረውን እክልና አደጋ በመረዳት የኑሮ ውድነቱን ሊቀርፉ የሚችሉ ርምጃዎችን በተጠና መንገድ መውስድ ጀምረናል።የግል ባለ ሀብቱ መሠረታዊ ሸቀጦችን በቀላሉ ወደ ሀገር እንዲያስገባ የሚያስችሉ አሠራሮችን በመዘርጋት በአጭር ጊዜ ውስጥ የኑሮ ውድነቱን ለመቆጣጠር እየተንቀሳቀስን እንገኛለን።መንግሥት በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የወሰዳቸውና እየወሰዳቸው ያሉ ርምጃዎች ኢኮኖሚውን ከነበረበት ችግር ውስጥ አውጥተው ወደ ፊት የሚያስፈነጥሩና የኢትዮጵያን ብልጽግና የሚያረጋግጡ እንደሚሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም።ሆኖም ሀገራችን ከውጭም ከውስጥም በጠላቶች በተወጠረችበት በዚህ ጊዜ ችግሮቻችንን ለመፍታት በአንድ ላይ መቆምና መተባበር እንደሚያስፈልገን ነጋሪ አያሻውም። በምንወስዳቸው ርምጃዎችና የኢኮኖሚውን ፈተናዎች ለመቅረፍ በምናደርገው ጥረት ሁሉ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ከጎናችን እንዲቆም ጥሪያችንን እናቀርባለን።

መዳረሻችንን የሚያሳየን መነሻችን ነው። በመነሻችን ያስመዘገብናቸውን ስኬቶች አጎልብተን ለብልጽግና እንደምንበቃ፣ ሀገራችንንም ከፍ ካሉት ተርታ እንደምናሰልፋት ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን። በዓለም ላይ ያለው ጨለማ ሁሉ የአንዲት ሻማን ብርሃን ሊያጠፋ አይቻለውም። የፈተናዎች ብዛትም የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ አያስቆመውም። የቤታችን ጉዳይ የቤታችን ብቻ ነው። በርዘግተን፣ ማዕድ ከብበን እንፈታዋለን። የቤታችን ጉዳይ አደባባይ ላይ አስጥተን ለጠላት መምቻ፣ ለጎረቤት መተረቻ፣ የምናቀብል ሞኞች አንሆንም። የኢትዮጵያን ጥንካሬና ልዕልና ላለማየት የተሳሉ ብዙዎች የቻሉትን ጫና ሁሉ እያጎረፉት ነው።በአንድነት ጸንተን፣ እያራገፍነው እንደምንሄድ በዚሁ አጋጣሚ ልንነግራቸው እንወዳለን።

የብሔራዊ ማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴሚያዚያ 22፣ 2013 ዓ.ምአዲስ አበባ



Exit mobile version