Site icon ETHIO12.COM

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በምርጫው ተፈጻሚ መሆን አለባቸው ያላቸውን ባለስድስት ነጥብ አጀንዳዎች ይፋ አደረገ


የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፣ ፓርቲዎች እና ከተለያዩ የምርጫ ተሳታፊዎች ጋር እያካሄደ በሚገኘው ውይይት ላይ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለ በምርጫው ወቅት ተግባራዊ መደረግ አለበት የተባሉትን ባለስድስት ነጥብ አጀንዳዎች አስተዋውቀዋል።

አጀንዳው በመጀመሪያ ደረጃ በምርጫው የሚሳተፉ ፓርቲዎች ከሰብአዊ መብቶች ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን እና የሚወስዷችውን እርምጃዎች በተመለከተ በምርጫ መወዳደሪያ ጥሪ ሰነዳቸው (ማኒፌስቷቸው) ውስጥ እንዲያካትቱ ይጠይቃል። በሁለተኛ ደረጃ ፓርቲዎች በአባላቶቻቸውና ደጋፊዎቻቸው የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን እንደማይታገሱ በይፋ ማሳወቅ እንዳለባቸው የሚጠይቅ ነው።

በሶስተኛ ደረጃ ምርጫው ለስርዓተ ፆታ ምላሽ ሰጪ መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለባቸው ተቀምጧል።

ኮሚሽኑ በአራተኛነት በኢትዮጵያ ለሰብአዊ መብት ጥሰት ምክንያት የሆኑ ህጎችን ፖሊሲዎችን እና አስተዳደራዊ ጉዳዮችን ለመፈተሽ እና ለማሻሻል በይፋ ቃል እንዲገቡ ጠይቋል። በአምስተኛ ነጥቡ የመንቀሳቀስ፣ የመደራጀት፣ መረጃ የማግኘትና ሃሳብን በነጻነት መግለጽ መብንት በሁሉም ተሳታፊ አካላት፣ በመንግስት ኃይሎች እና በመገናኛ ብዙሃን ጭምር ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ ኮሚሽኑ አስታውቋል።

የሰብአዊ መብት ኮሚሽን በስድስተኛ ነጥብ እንዳስገነዘበው፤ ከግጭት ቀስቃሽና የጥላቻ ንግግር እንዲሁም ከኃይል እርምጃዎች ሙሉ በሙሉ መቆጠብ ይገባል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም ኮሚሽኑ ያወጣቸው ባለስድስት ነጥብ አጀንዳዎችን እንደሚደግፍ እና ለተፈጻሚነታቸውም እንደሚሰራ አስታውቋል። via EPA

Exit mobile version