Site icon ETHIO12.COM

“እያንዳንዳችን ሰላምን አጥብቀን የምንሻና የምንኖራት እንሁን”ጠ/ሚ አብይ አህመድ

– በነገ ብሩህ ተስፋና ተዝቆ የማያልቅ እድል ላይ አነጣጥረን የመጭውን ትውልድ ብልፅግና እውን ማድረግ አለብን

በነገ ብሩህ ተስፋና ተዝቆ የማያልቅ እድል ላይ አነጣጥረን የመጭውን ትውልድ ብልፅግና እውን ለማድረግ በዛሬ ላይ ሳንታክት መትጋት ይገባናል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአዲስ አበባ ከመስቀል አደባባይ እስከ ማዛጋጀ ቤት የሚዘልቀውና በ2 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር የተገነባውን ፕሮጀክት መርቀዋል።

በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ባስተላለፉት መልእክትም የትናንት አሻራን በማጥናት የነገ ተስፋን በመሰነቅ የዛሬን አድል በመጠቀም ኢትዮጵያን ማሻገር ይገባል ብለዋል።

ለዚህም በነገ ብሩህ ተስፋና ተዝቆ የማያልቅ እድል ላይ አነጣጥረን የመጭውን ትውልድ ብልፅግና እውን ለማድረግ በዛሬ ላይ ሳንታክት መትጋት ይገባናል ነው ያሉት።

ታሪክ ትናንት በዛሬ ላይ ጥሎት ያለፈ አሻራ ወይም ጠባሳ በመሆኑ የትናንት ጠባሳ የነገ አበሳ እንዳይሆን መትጋት ከሁላችንም ይጠበቃል ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ።

ጤናማ ግለሰብና ቤተሰብ ከሌለ ሀገር መቀጠል ስለማይችል ከሁላችንም ሰላማዊ ንግግርና ሰላማዊ ግብር ያስፈልገናል ብለዋል።

እያንዳንዳችን ሰላምን አጥብቀን የምንሻና የምንኖራት እንሁን በማለትም ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

የአፍሪካዊያንን የስልጣኔ አሻራዎች በማንሳት ኢትዮጵያም አንዷ የስልጣኔና የበርካታ ታሪኮች ባለቤት በመሆን ተጠቃሽ አገር መሆኗን አብራርተዋል።

አፍሪካዊያን የሚታደስም አዲስ ስልጣኔም መፍጠር እንችላለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የአፍሪካን ቀንድ የአፍሪካ ክንድ እናደርጋታለን” ብለዋል። via ሰኔ 6 ቀን 2013 (ኢዜአ)

Exit mobile version