ETHIO12.COM

ዐቢይ አህመድ “የኢትዮጵያን የአፍሪካ ቀንድን የአፍሪካ ክንድ እናደርጋለን “

“የኢትዮጵያን አንድነት ከማስጠበቅ አልፈን ” አሉ የበሻሻዋ መንደር ፍሬ አብይ አሕመድ፣ “የአፍሪካ ቀንድን የአፍሪካ ክንድ እናደርጋለን ” ሲሉ በሙሉ ጀዝም ጅማ ላይ ሆነ ለዓለም ተናገሩ። አብረዋቸው የነበሩት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ “… ይህን አገር ወዳድ፣ቆራጥ፣ የፍቅር ሰው፣ አሻጋሪ መሪ ወልዳችሁ ስለሰጣችሁን አናመሰግናለን” አሉ። ደመቀመ መኮንን ” አስተዋይ” ሲል ህዝቡን አመሰገኑ። አደም ፋርህም በኦሮምኛ አወጉ። ጅማ ስታዲየም ሰከረ።

ቦታ አግኝቶ ከገባው ይልቅ፣ ከደጅ የፈሰሰው ደጋፊ የጅማን ፍሬ ” አቢቹን” ሲያነግስና ስም እየጠራ ሲዘምር የአህመዲን ጀበል ከምርጫ መውጣት በነብይነት የሚያሸልም እንጂ በፈሪነት የሚያስወቅስ እንዳልሆነ ያሳያል።

የጅማ ከተማና አካባቢዋ ነዋሪዎች ብልጽግና ፓርቲን በመደገፍ ዛሬ ለመጨርሻ ጊዜ ባካሄዱት ሰልፍ ላይ ባልተቤታቸውንና ባልደረቦቻቸውን ይዘው ወደዛው ያቀኑት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ፣ “የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት የጀመርነውን ስራ ለማሳካት የሚያቆም ኃይል የለም” ሲሉ አድናቆቱ ገኖ ይሰማ ነበር። በግጥም፣ በቀደም አባባል፣ በአካባቢ ፈሊጥ፣ ከምሁራኖች አባባል፣ ከባህላዊ ዘዬ እያጣቀሱ የጅማን ሕዝብ ተንተርሰው ለመላው ሕዝብ ሃሳባቸውን ያደረሱት አብይ አሕመድ፣ ያንን ሁሉ የስም ማጥፋት ዘመቻ ወደ እንዲህ ያላ ትዕንት መቀየራቸው አስደማሚም፣ አስገራሚምም ነው።

“የኢትዮጵያን ህዝብ ይዘን ከኢትዮጵያ አልፍን ለአፍሪካ ብርሃን እናመጣለንም ” ሲሉ ኢትዮጵያዊነትን እየተከሉ የደሰኮሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ለዘመናት አስታዋሽ ያጣውንና ውበቱን አገጩ ስር ቀርቅሮ ዳዋ ለበላው የአወይቱ መናፈሻ ብርሃን በመሆናቸው ህዝብ ተደስቷል።

“ኢትዮጵያ ከመፍረስ እንድትድን ያደረግናት በአንድነት፣ በህብረትና በመደማመጣችን ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “የአፍሪካ ቀንድን የአፍሪካ ክንድ” ማድረግ አዳጋች እንደምያሆን አመልክተዋል።

“በምርጫው ዴሞክራሲን እንተክላለን፣ ዛፍም እንተክላለን” ሲሉ ቃል የዘሩት አብይ ” መላው ዓለም በምርጫ ቀን ይጋጫሉ ብሎ ሲጠብቅ፤ እኛ ደግሞ ችግኝ ተክለን ፍቅርን እናስተምራለን ” ሲሉ የተከሉትን ቃል ልምላሜ እዛው አሳይተዋል። ” ቃል ያለው እውቀት አለው” እንዲሉ በመጨረሻው የምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ላይ ለጥሞና ጊዜ የሚሆን አሳብን አሲዘዋል።

አብይ አህመድ “ለኢትዮጵያ ብልጽግና፣ ልማት፣ አንድነትና ህብረት ለሚሹ ፖለቲካ ፓርቲዎችም መልካም ዕድል” ሲሉ ምኞታቸውን የገለጹት ” ከብልጽግና ባልተናነሰ” በማለት ነው። “ግን ” አሉ አብይ አሕመድ ” ብልጽግናም ሆነ ሌላው ጋር ሌባ አያስፈልግም” ሲሉ ደጋግመው አሳስበዋል።

የጅማ መገለጫ የሆነችው ባለ ሶስት እግር መቀመጫም ፍቅር፣ ሰላምና አንድነት ትርጓሜ እንዳላትም በዚሁ መድረክ ላይ   የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ፤ ለኢትዮጵያ ብሎም ለመላው አፍሪካዊያን ሰላምና ብልፅግና ተመኝተዋል።

የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመለስ አብዲሣ በበኩላቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአመራርነታቸው ኢትዮጵያ የተከበረች፣ የአንድነትና የእኩልነት አገር እንድትሆን ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ እዚህ ደረጃ ላይ እንዲደርስና በብዙ መሰናክሎች ውስጥ በማለፍም ”ድንቅ” ብቃታቸውን አሳይተዋል ብለዋል።

Exit mobile version