Site icon ETHIO12.COM

አሸባሪው ትህነግ ሕጻናትን ለጦርነት በማሰለፉ ዓለም አቀፍ የትዊተር ዘመቻ ተከፈተበት፤

አሸባሪው የሕወሓት ቡድን ህፃናትን ለጦርነት በማሰለፍ የሚፈፅመውን ወንጀል ለማውገዝና ተጠያቂ እንዲሆን የሚጠይቅ ዓለም አቀፍ የትዊተር ዘመቻ እየተካሄደ ነው። በመላው ዓለም የሚገኙ የትዊተር ማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ የሆኑ ኢትዮጵያዊንና የኢትዮጵያ ወዳጆች እንዲሁም ዳያስፖራዎች የአሸባሪውን የሕወሃት ቡድን ድርጊት በመቃዎም ነው ዘመቻውን እያደረጉ ያሉት።

ቡድኑ በትግራይ ክልል እያደረሰ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትና ህፃናት ለጦርነት ማሰለፉን በተመለከተ ለዓለም ማህበረሰብ ለማሳወቅ እና ድርጊቱን በይፋ ለማውገዝ የተጀመረ የትዊተር ዘመቻ ነው።

ቡድኑ ህፃናትን አደንዛዥ ዕፅ በማስጠቀም ወደ ጦር ግንባር እንዲሰለፉ እያደረገ ያለበት ሁኔታ የአለም አቀፉን የህፃናት መብት የሚጣረስ የጦር ወንጀል ነው የሚል መዕልክት ትዊት እያደረጉ ነው።

የአለም አቀፉ ማህበረሰብ፣ ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑ የኢትዮጵያ ወዳጆች እዲሁም አለም አቀፍ ተቋማት ሕወሓት በሕፃናት ላይ እያደረሰ ያለውን ድርጊት እንዲያወግዘ ጥሪ አቅርበዋል። አንዳንድ የዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሃን አሸባሪው ቡድን ህፃናትን ለጦርነት በማሰለፍ እያደረገ ያለውን ድርጊት ለማስተባበል መሞከራቸው እንዳሳዘናቸው ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትሕ ኢዜማ መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሕወሓት ሕጻናትን ለውጊያ እየመለመለና እያሰማራ እንደሚገኝ በርካታ ዘገባዎች እየወጡ እንደሚገኝ በትዊተር ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት አስተያየት ገልጸዋል።

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ጣሒር መሐመድ “ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለትግራይ ሕዝብ ተጨንቀናል በማለት ሀሳቡን ሲገልጹ የቆዩ ቢሆንም፤ በወታደራዊ ግጭት አሸባሪው ሕወሓት ሕጻናትን ለውትድርና ሲጠቀም ዝምታን መርጠዋል” ብለዋል። ሕወሓት እየፈጸመ ያለው ድርጊትም የጦር ወንጀል መሆኑን ነው የገለጹት።

የሴቶች ሕጻናትና ወጣቶች ሚኒስቴር የእናቶችና ሕጻናት ጤና እና የስርዓተ ምግብ ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም፤ ሕጻናትን በጦርነት ውስጥ ማሳተፍ የጦር ወንጀል ነው፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሕጻናት መብት ኮንቬንሽን የጣሰ ነው ብለዋል። ሁሉም በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም አይነት ትዕግስት ሊኖረው እንደማይገባ ገልጸዋል።

በሌላ በኩል የህወሃት አሸባሪ ቡድን ህፃናትን ለጦርነት በማሰለፍ እየፈፀመ ባለው ከባድ ወንጀል ተጠያቂ እንዲሆን የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /ትዴፓ/ ጥሪ አቀረበ።

የፓርቲው ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተሻለ ንጉሴ በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት ህፃናትን ለጦርነት ማሰለፍ በኢትዮጵያም ይሁን በዓለም ህግ በከባድ ወንጀል ያስጠይቃል። የህወሃት አሸባሪ ቡድን ይህንን ህግ በመተላለፍ ህፃናትን በመመልመል ለጦርነት በማሰለፍ ወንጀል በመፈፀም ላይ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በመሆኑም ቡድኑ እየፈፀመ ባለው ከባድ ወንጀል ተጠያቂ ሊሆን ይገባል ብለዋል አቶ ተሻለ። የህወሃት የጥፋት ቡድን የተለያዩ ወንጀሎችን የመፈፀምና አገር የማፍረስ ተልእኮ ይዞ የሚንቀሳቀስ መሆኑን ያስታወሱት የትዴፓ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አሁን ላይ ደግሞ ህፃናትን ወደ ጦርነት መማገዱን ተያይዞታል ብለዋል።

በመሆኑም ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የህወሃትን ቡድን በዓለም አቀፍ ህግ ተጠያቂ እንዲያደርግ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

የትግራይ ሕዝብም ምንም አይነት አላማና ምክንያት አልባ በሆነ ጦርነት ሕፃናት ልጆቹን ማጣት ስለሌለበት የቡድኑን እኩይ አላማ መቃወምና ማውገዝ አለባቸው ነው ያሉት።

በአሁኑ ወቅት በተለይ የግብረሰናይ ድርጅቶች የሽብር ቡድኑ በሕፃናት ላይ የሚያደርሰውን ወንጀል እያዩ ዝምታን መምረጣቸው የሚያሳዝን ነው ብለዋል።

በአሸባሪ ቡድኑ ተግባር መላው ሕዝብ ጉዳት የሚደርስበት ቢሆንም በተለይ የትግራይ ሕዝብ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ በመሆኑ እንዲታገለው አቶ ተሻለ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

ልጆችና ቤተሰቦቹን በውጭ አገራት እያኖረ የድሃ ልጆችን ወደ ጦርነት እየማገደ ያለውን የህወሃት ቡድን የትግራይ ሕዝብ ሊቀበለው አይገባም ነው ያሉት።

የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /ትዴፓ/ የህወሃት የሽብር ቡድን በህፃናት ላይ እየፈፀመ ያለውን ወንጀል በመቃወም በቅርቡ የአቋም መግለጫ እንደሚያወጣም አቶ ተሻለ ጠቁመዋል።

በተባበሩት መንግሰታት የህፃናት መብት ኮንቬንሽን አንቀፅ 38 እንደተመለከተው ህፃናት ለጦርነት ያለመመልመል፣ ያለመሳተፍ እና የመሳሰሉት መብቶች አሏቸው፡፡


Exit mobile version