ETHIO12.COM

ፖሊስ አዲስ አበባ “በጁንታው ደጋፊ ንግድ ቤቶች” ድንገተኛ አሰሳ አካሂዶ መሳሪያ፣ ወታድራዊ ትጥቅ፣ሀሺሽ፣ገንዘብ፣የትህነግ የስብሰባ ቃለ ጉቤ … አገኘ መረጃው ተያይዟል

የአዲስ አበባ ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት በጥናት ላይ በመመስረት እና ከህዝብ የደረሰውን መረጃ መሰረት በማድረግ በከተማችን በስጋትነት በተለዩ የተለያዩ ንግድ ቤቶች እና ድርጅቶች ላይ ባደረገው ብርበራ እና ፍተሻ ልዩ ልዩ የጦር መሳሪዎችን፣ ሰነዶችን እና የፀጥታ አካላት የደንብ አልባሳትን በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገለፀ፡፡

መንግስት የህግ የበላይነትን ለማስከበር በህወሃት ጁንታ ቡድን ላይ እርምጃ መውሰዱን ተከትሎ ህግ የማስከበር ዘመቻው በድል ተጠናቆ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መቀሌን ጨምሮ መላው ትግራይን መቆጣጠሩ ይታወቃል፡፡


የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ሐምሌ 11 ቀን 2013 ዓ/ም በሰጡት መግለጫ እንዳብራሩት በዚህ ሀገርን የማዳን እና ትግራይን የመታደግ ዘመቻ አብዛኞቹ የጁንታው አመራሮች ሲማረኩ ፣ የተወሰኑት ደግሞ ተደምስሰዋል፡፡
ወቅቱ የእርሻ በመሆኑ የትግራይ አርሶ አደሮች በእርሻ ስራቸው ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ እና ለህዝብ ሰላም ሲባል መንግስት የተናጠል ተኩስ ማቆም እርምጃ መውሰዱን ኮሚሽሩ አስታውሰው ነገር ግን ጁንታውና የጁንታው ደጋፊዎች የመንግስትን የተናጠል የተኩስ አቁም እርምጃ እንደ ፍርሃት በመቁጠር ልዩ ልዩ ሚዲያዎችንና ማህበራዊ ትስስር ገፆችን በመጠቀም የበሬ ወለደ አሉባልታ በማናፈስ ሀገርን የማተራመስ ሴራቸውን እንደ አዲስ ለማስቀጠል ላይ ታች ሲሉ መሰንበታቸውን ገልፀዋል፡

በጁንታው የአገዛዝ ዘመን ልዩ ተጠቃሚ የነበሩ እና ለውጡ ስጋት ላይ የጣላቸው የጁንታው ናፋቂዎችና ደጋፊዎች ቀደም ባለው ጊዜ ህግ የማስከበር ዘመቻውን ለማደናቀፍ ብሎም ለውጡን ለመቀልበስ ከጁንታው ተልዕኮ ተቀብለው ቢንቀሳቀሱም በፀጥታ ኃይላችን ጥረት በህዝባችን ቅን ተባባሪነት ሴራቸውን ማክሸፍ ተችሏል ብለዋል የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ፡፡
በህግ ማስከበሩ ዘመቻ ወቅት በአዲስ አበባ ብቻ ከጁንታው ተላላኪዎች እጅ በርካታ የጦር መሳሪያዎችና ልዩ ልዩ ወታደራዊ ቁሳቁሶች በቁጥጥር ስር መዋላቸው የሚታወቅ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት በጥናት ላይ በመመስረት እና ከህዝብ የደረሰውን መረጃ መሰረት በማድረግ ከሰኔ 19 እስከ ሐምሌ 8 ቀን 2013 ዓ/ም በሁሉም ክፍለ ከተሞች ባከናወነው ህግን የማስከበር ተግባር አሸባሪው ህወሃት በሀይል መቀሌን እንደተቆጣጠረ አስመስሎ ያናፈሰውን ሀሰተኛ መረጃ በማስተጋባት እንዲሁም በከተማችን ብጥብጥና ረብሻ ለማስነሳት ከጁንታው ተልእኮ ተቀብለው ሲንቀሳቀሱ የተገኙ 325 ግለሰቦች በህግ አግባብ ተይዘው ምርመራ እየተጠራባቸው እንደሚገኝ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ገልፀዋል፡፡ በተጨማሪም በስጋትነት በተለዩ ግሮሰሪዎች ፣ ጭፈራ ቤቶች ፣ ሆቴሎች እና ሌሎች ንግድ ቤቶች በድምሩ 793 ተቋማት ላይ ፖሊስ ባደረገው ብርበራ እና ፍተሻ 126 ልዩ ልዩ ሽጉጦች ፣ 918 የሽጉጥ ጥይት እና 124 የሽጉጥ ካርታዎች፣ 3 ክላሽ ኢንኮቭ ጠመንጃ ፣ 390 የክላሽ ጥይት ከ4 ካርታ ጋር፣ 1 ኤስ.ኬ.ኤስ እና 1 ኡዚ መሳሪያ በኤግዚቢትነት ተይዘዋል፡፡
ከተጠርጣሪዎቹ እጅ በርካታ የሀገር መከላከያ ሰራዊት የቀድሞ የደንብ ልብስ፣ የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ፣ የፌዴራል እና የአዲስ አበባ ፖሊስ የደንብ ልብስ ፣ የፖሊስና የሀገር መከላከያ ማዕረጎች እንዲሁም ልዩ ልዩ መለዮዎች እንደተያዙም ኮሚሽነር ጌቱ አብራርተዋል፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪ ለፖሊስ ምርመራ የሚረዱ መረጃዎች የተገኘባቸው ላፕቶፕ ኮምፒውተሮች ፣ ፍላሾች ፣ ታብሌት ስልኮች ፣ የባንክ የሂሳብ ደብተሮች ፣ ሲም ካርድ ፣ የፋክስ ማሽን እንዲሁም ጂ.ፒ.ኤስ እንደተያዙ ኮሚሽነር ጌቱ ጠቅሰዋል፡፡
የጁንታው ቡድን አባላት ውይይት ሲያደርጉበት የነበረ ቃለ ጉባኤ እና የህወሃት መተዳደሪያ ደንብ እንዲሁም የጁንታው መልዕክት የተጫነባቸው ሞባይል ስልኮች መገኘታቸው የጁንታው ተላላኪዎች አደረጃጀት ፈጥረው እና ተልዕኮ ተቀብለው ሲንቀሰቀሱ እንደነበር በምርመራ መረጋገጡን ኮሚሽነሩ አብራርተዋል፡፡ ፖሊስ ባደረገው ክትትልና ምርመራ ከ175 ሺ በላይ ብር እና 11 ሺ የአሜሪካ ዶላር እንዲሁም የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች ከጁንታው ተላላኪዎችና ደጋፊዎች እጅ ተይዟል፡፡
በከተማችን አዲስ አበባ መንግስት የወሰደውን የሰላም ዕርምጃ ከሽንፈት የቆጠሩ ተሸሽገውና አንገታቸውን ደፍተው የነበሩ የጁንታው ተላላኪዎች በአንዳንድ መዝናኛ እና ጭፈራ ቤቶች ሰንደቅ አላማችንን በሚያዋርድ መልኩ ያልተገባ ድርጊት እየፈፀሙ ሲጨፍሩ ተይዘው ምርመራ እየተጣራባቸው ይገኛል፡፡
ምንም እንኳን የጁንታው አፈ-ቀላጤዎች በተለመደው የሐሰት ፕሮፖጋንዳ አሸንፈናል እያሉ መቃዠታቸው ለሁሉም ግልፅ ቢሆንም ጥቂት የማይባሉ ከእኛው ጋር የሚኖሩ፣ ሰላማቸው ተጠብቆላቸው የጥይት ድምፅ ሳይሰሙ በሠላም ውለው በሠላም እያደሩ እኛው መሐል ሆነው የሽብርተኛ ቡድኑ አጋር መሆናቸውን በግልፅ አሳይተዋል፡፡
የከተማችን ሰላም ወዳድ ነዋሪ ለዘመናት በገነባው ጨዋነት እና አርቆ አስተዋይነት ግለሰቦቹ የጁንታው ተላላኪዎች መሆናቸውን በተግባራቸው ቢያረጋግጥም ለሚመለከታቸው የፍትህ አካላት ጥቆማ በመስጠት ህጋዊ የዜግነት ኃላፊነቱን ከመወጣት ውጪ እንደ እነሱ ስሜታዊነት አላሸነፈውም ፤አንዳችም ህገወጥ ተግባር አልፈፀመም፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሠላም ወዳድ ለሆነው ለከተማችን ነዋሪ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው በራሳቸው እና በአዲስ አበባ ፖሊስ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በመጨረሻም መላው የከተማችን ነዋሪዎች በተደራጀ እና በነቃ ትብብር አካባቢያቸውን እንዲጠብቁ ፣ ከፖሊስ እና ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር ያላቸውን የመረጃ ልውውጥ እንዲያጠናክሩ ፣ ወቅታዊ መረጃን በየዕለቱ ከትክክለኛው የመረጃ ምንጭ እንዲከታተሉ እና አጠራጣሪ ሁኔታ ሲያጋጥም ወዲያውኑ ለፀጥታ አካላት ጥቆማ በመስጠት ትብብራቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ጥሪያቸውን አስተላፈዋል፡:

Exit mobile version