Site icon ETHIO12.COM

መንግስት ከትህነግ አሸባሪ ሃይል ጋር ለድርድር እንደማይቀመጥ ይፋ አደረገ

በሰሜናዊ የአገሪቱ ክፍል የሚገኘውን አብዛኛውን የትግራይ ክልል ከተቆጣጡሩት ከህወሓት አማጽያን ጋር ለወራት በዘለቀ ጦርነት ውስጥ የቆየው የኢትዮጵያ መንግሥት ሽብርተኛ ካለው ቡድን ጋር እንደማይደራደር አስታውቋል።

ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ ከቢቢሲ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት የአሸባሪው ኃይል አመራሮች አንዱ የሆኑት ጄነራል ጻድቃን ገ/ትንሳይ ያቀረቡት ቅድመ ሁኔታ ተቀባይነት አግኝቶ የተኩስ አቁሙ እንዲደረግና ሁሉን አቀፍ ፖለቲካዊ ውይይት ተደርጎ የሽግግር ሂደት መጀመር አለበት ማለታቸው ይታወሳል።

ይህን አስመልክቶ ለቢቢሲ ምላሽ የሰጡት የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሚኒስትር አቶ ዛዲግ አብረሃ መንግሥት ከአሸባሪው ትህነግ አመራሮች ጋር ለድርድር እንደማይቀመጥ ገልጸዋል።

አሁን በሰሜኑ የአገሪቱ አካባቢ ያለውን ሁኔታ በሚመለከትም መንግሥት በተናጠል ተኩስ አቁም ውስጥ መሆኑን ጠቅሰው “አሁን ከአሸባሪው ትህነግ በኩል የሚታየው ነገር ራስን አጋኖ ከማየት የመነጨ ነው” ብለዋል።

ነገር ግን መንግሥት ትዕግስቱ ሲሟጠጥ ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ “አቅማችንን ማየት ከፈለጋችሁ የተወሰኑ ሳምንታት መጠበቅ ይኖርባችኋል። ትዕግስታችን የተሟጠጠ ዕለት እንዴት ከእያንዳንዱ ከተማና መንደር ጠራርገን እንደምናስወጣቸው ታያላችሁ። ጦርነት ከሆነ ፍላጎታቸው….ያገኙታል” ሲሉ ተናግረዋል።

ሚኒስትሩ ጨምረውም መንግሥታቸው ከየትኛውም ወገን ጋር ቁጭ ብሎ በመነጋገር ችግሮችን ለመፍታት ዝግጁ መሆኑን ጠቅሰው ነገር ግን “ህወሓት ሽብርተኛ ድርጅት በመሆኑ” ከሌሎች የትግራይ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በመነጋገር መፍትሔ ለመፈለግ እንደሚጥር አመልክተዋል።

የእርዳታ አቅርቦትን በተመለከተ መንግሥት ችግር ያለበት በቁጥር ውስን ካሏቸው የትህነግ አመራሮች ጋር እንጂ ከትግራይ ሕዝብ ጋር እንዳልሆነ ጠቅሰው “መንግሥት ወደ ክልሉ የሚገባ የሰብአዊ እርዳታን ፈጽሞ አላገደም ይልቁንም ከየትኛውም የእርዳታ ሰጪ በላይ መንግሥት አብዛኛውን ድጋፍ ለክልሉ ሕዝብ እያደረገ ነው” ብለዋል።

ጄነራል ጻድቃንም ሆነ ህወሓቶች “እርዳታ ለሕዝቡ እንዳይደርስ ተገድቧል” የሚለት የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብንና የመገናኛ ብዙኃን ለጉዳዩ ያለቸውን ትኩረት ለመሳብ የተደረገ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

አክለውም “መንግሥት ከትግራይ ለቆ ወጥቷል፤ ስለዚህ ለሕዝቡ እርዳታ ሊቀርብ ይችላል። የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት እገዳን በተመለከተ ህወሓቶች የሌለ ነገር ነው እየጠየቁ ያሉት።”

አማጺው ህወሓት ለተኩስ አቁም ካቀረባቸው ቅድመ ሁኔታዎች መካከል በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ በሚለው ላይ ምላሽ የሰጡት አቶ ዛዲግ፣ከጥቂት ዓመታት በፊት ከለውጡ ጋር ተያይዞ የፖለቲካ አስረኞች በሚፈቱበት ዋነኛው ተቃዋሚ ህወሓት እንደነበር ጠቅሰው ያነሱትን ጥያቄ አጣጥለውታል።

የፈደራል መንግሥቱ ሰኔ 21/2013 ዓ.ም “ሰብዓዊነትን መሰረት ባደረገና ተጨማሪ ጉዳት በማያስከትል መልኩ” የተናጠል የተኩስ አቁም አውጆ ሠራዊቱን ከትግራይ ክልል አስወጥቻለሁ ማለቱ ይታወሳል።

ነገር ግን የህወሓት ኃይሎች የጥቃት አድማሳቸውን ወደ አጎራባቾቹ የአማራና የአፋር ክልሎች በማስፋት ባለፉት ሳምንታት ውጊያዎች መካሄዳቸው ተነግሯል።

የአማጺው ኃይል አመራር የሆኑት ጄነራል ጻድቃን እንደተናገሩት ኃይሎቻቸው ጥቃቱን ያካሄዱት “በትግራይ ክልል ላይ ያለውን መዘጋት (ብሎኬጅ) በመስበር” መውጫ መንገድ ለማግኘት እንዲሁም ቡድኑ ለተኩስ አቁም ያስቀመጠውን ቅድመ ሁኔታ መንግሥት እንዲቀበል ጫና ማሳደር መሆኑንን አስታውቀው ነበር።

የትግራይ ክልልን ለ30 ዓመታት ሲያስተዳድር የቆየው ገዢ ፓርቲ ህወሓት ኃይሎቹ በፌደራሉ ሠራዊት ላይ ጥቃት መሰንዘራቸውን ተከትሎ በተካሄደ ወታደራዊ ግጭት ከመንበሩ ከተወገደ በኋላ የፌዴሬሽን ምክር ቤት የክልሉን አስተዳደር ሕገ ወጥ በማለት ሲበትነው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ደግሞ ህወሓትን ሽብርተኛ ቡድን ብሎ ሰይሞታል።

ማስታወሻ – ዜናው የቢቢሲ ሲሆን የስም ማስተአካከያና ዕርዕ ተቀይሯል።


Exit mobile version