Site icon ETHIO12.COM

ኬኒያ፤ ትህነግ አሸባሪ መባሉ በፓርላማው ሊነሳለት ይገባል አለች

ሐሙስ ዕለት የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ በመከረበት ወቅት የኬኒያው ተወካይ ትህነግ አሸባሪ መባሉ ሊነሳለት ይገባል አሉ።

ኢስቶኒያ፣ ፈረንሳይ፣ አየርላንድ፣ ኖርዌይ፣ ዩናይትድ ኪንግደምና አሜሪካ በጠሩት በዚህ ስብሰባ ላይ የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ጸኃፊአንቶኒዮ ጉቴሬዝ ንግግር አድርገው ነበር። ዋና ጸሃፊውም በሰሜኑ የኢትዮጵያ ያለው ግጭት ሊቆም እንደሚገባው በመጠቆም ንፁሀን እየተጎዱ ስለሆነ ሰብዓዊ ዕርዳታ ሊያገኙ የሚገባቸው ምቹ ሁኔታ ባለመፈጠሩ እንዳላገኙ አስረድተዋል።

ከዋና ጸሃፊው ንግግር ቀጥሎ የስብሰባው ጠሪዎች በተከታታይ ተናግረዋል። እንቆምለታለን የሚሉትን ዴሞክራሲ በገሃድ መቀመቅ በመክተት ከኢስቶኒያ እስከ ሜክሲኮ ያሉት አገራት በአሜሪካና አውሮጳ የታዘዙትን እንደ በቀቀን በመድገም ሎሌነታቸውን በዓለምአቀፍ መድረክ አስመስክረዋል።   

በአንጻሩ የራሺያዋ ተወካይ ለሞራል ልዕልና እና ሐቅ በመቆም በምዕራባውያኑ የተዘነጋውን እውነታ በማጉላት ኢትዮጵያ የራሷን ችግር የመፍታት ዐቅምና ብቃት እንዳላት በመጥቀስ ጣልቃገብነትን ተቃውመዋል። የኢትዮጵያ የግዛት አንድነት፣ ሎዓላዊነትና ክብር በምንም መገሠሥ እንደሌለበት የጠቆሙ ሲሆን ይህንን አቋማቸውን ሕንድና ቻይና አስተጋብተውታል።

በኢትዮጵያ ምርጫ መካሄዱን ያስታወሱት የራሺያዋ አምባሳደር፤ በዚህም ምርጫ ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ አብላጫ ሊያስተዳድራቸው የሚገባውን ፓርቲ መምረጣቸው አገሪቷና የማትከፋፈል፤ ሕዝቧም በአንድነት የቆመ መሆኑ ማሳያ ነው ብለዋል። ይህ የራሺያ አምባሳደር ንግግር ኢትዮጵያ ልትበታተን ነው የሚለውን የምዕራቡ ተወካዮችና የአጨብጫቢዎቻቸውን ትርክት ገደል የከተተ ነበር።

ከዚህ በአንጻሩ የኬኒያው ተወካይ ንግግራቸውን ኢትዮጵያን በመክሰስ ወይም በማንኳስ ነበር የጀመሩት። የዛሬው ስብሰባ የሚያሳየን እና ችግሩ እየተባባሰ መሄዱ ኢትዮጵያ የግጭት መከላከልና ማስወገድ ስልቶች የሌላት መሆኑን ነው በማለት ነበር በንግግራቸው መግቢያ ላይ የተናገሩት።   

ከቅኝ ገዢ ጌቶቻቸው ጋር በአንድ መድረክ መታየቱን እንደ ትልቅ ዕድል የቆጠሩት የሚያስመስልባቸው የኬኒያው ተወካይ በአንድ በኩል የጌቶቻቸውን ቃል ለመጠበቅ በሌላ በኩል የኢትዮጵያን ጉርብትና ላለማጣትና ንግግራቸው የሚያስከትለውን በማሰብ አገም ጠቀም የሚባል ንግግር ነበር ያደረጉት። ተወካዩ በአቋመቢስ የበታችነት ወይም የተገዢነት ምስቅልቅሎሽ ሲሰቃዩ ተስተውለዋል።   

ተወካዩ በንግግራቸው ጌቶች እንዳይቆጡ ኢትዮጵያን ሲያብጠለጥሉ ይቆዩና ቀጠል ሲያደርጉ ደግሞ ኢትዮጵያ የነጻነት ቀንዲል፣ የጸረዘረኝነት ትግል ፋና ወጊ፣ ወዘተ በማለት ለማለሳለስ በብዙ የስቃይ ውጣውረድ ውስጥ አልፈዋል። ቅኝ ገዢዎቻቸው በቀደዱላቸው ቦይ ብቻ በመፍሰስ የትኛውም የትህነግ አመራር አንዴ እንኳ ያልተነገረውን ተናገሩ።

በንግግራቸው ማጠናቀቂያ ላይ ሊደረጉ የሚገባቸው ነገሮች በማለት የተወሰኑ ነጥቦችን ከጠቀሱ በኋላ ለኢትዮጵያ ፓርላማ ምክር ቢጤ ትዕዛዝ ሰጡ። “ፓርላማው በትህነግ ላይ የጣለውን አሸባሪ የሚለውን መጠሪያ ሊያነሳ ይገባል” በማለት ጌታቸው ረዳ እንኳን እስከዛሬ ደፍሮ ያልተናገረውን ተናግረዋል። “ጦርነት አማላይ ነው” በማለትም ኅልውናውን ለማስከበር በተነሳው የሕዝብ ሠራዊት ላይ ተሳልቀዋል።  

ዲፕሎማቱ ልክ ትዕዛዝ እንደፈጸመ አገልጋይ ይህቺ ንግግራቸው የምታስከፍላቸውን ዋጋ በመገመትም በስተመጨረሻ ላይ ኢትዮጵያን በመካብ ንግግራቸውን አጠናቅቀዋል። 

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Exit mobile version