Site icon ETHIO12.COM

❝የአሸባሪውና ወራሪ የመጨረሻ ግብዓተ መሬት የምንፈፅምበት ጊዜ ሩቅ አይደለም❞ ጄነራል ብርሃኑ ጁላ

❝እኛ የምንዋጋው ኢትዮጵያን ለማዳን ነው፤ የሕልውና ጦርነት ነው፤ ጠላት የሚዋጋው ኢትዮጵያን ሊያፈራርስ ነው፤ ከአማራ ላይ ሒሳብ ሊያወራርድ ነው፤ የውጭ ኮሪደር ከፍቶ ኢትዮጵያን ለውጭ ጠላት ለመስጠት ነው❞

❝የአሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ቡድንን የመጨረሻ ግብዓተ መሬት የምንፈፅምበት ጊዜ ሩቅ አይደለም❞ ጄነራል ብርሃኑ ጁላ

የ2014 ዓ.ም አዲስ ዓመት የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት በማይጠብሪ ግንባር ተከብሯል። በበዓሉ ላይ ንግግር ያደረጉት የምዕራብ እዝ አዛዥ ሜጄር ጄኔራል መሠለ መሠረት ሽብርተኛው ትህነግ በከፈተው ጦርነት ድባቅ መትተነው በዓሉን ስናከበር ኩራት ይሰማናል ነው ያሉት። በተሰጣቸው ግዳጅ ሁሉ የሀገርን ክብርና ጥቅም በሚያስጠብቅ መልኩ በድል እየተወጡ መሆናቸውንም ገልጸዋል። አንዲትና መተኪያ በሌላት ኢትዮጵያችን ምለን ፣ ደማቅ ታሪክ ሠርተን፣ የሀገር አንድነታችንን አስጠብቀን፣ ሕዝባችችን አኩርተን፣ በጀግንነት ተዋግተን በጀግኖች ደምና አጥንት የሕዝባችንን አደራ ጠብቀናልም ብለዋል።

ሜጄር ጄኔራል መሠለ በሀገር የመጡብንን ጠላቶች ዳግም እንዳይመለሱ አድርገን ድባቅ መትተናልም ነው ያሉት። እልህ አስጨራሽ ትግል በማድረግ የጠላትን ኃይል መደምስሳቸውን ተናግረዋል። ከራስ በፊት ለሕዝብና ለሀገር ብለን ጠላትን እያመከንን ነውም ብለዋል።

የምእራብ እዝ ትንታጎች መቀሌን በመቆጣጠር፣ የአሸባሪው ትህነግ ቁንጮ አባላት ከመቀሌ ሸሽተው ተንቤን ሲገቡ እየተከታተሉ መደምሰሳቸውን፣ መማረካቸውን አስታውሰዋል።

አሸባሪው ቡድን ሀገሪቱን ለማተራመስ የመረጠው ቦታ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እንደሆነ ያነሱት አዛዡ በአካባቢው ሽብር ለመፍጠር ጥረት ቢያደርግም በጀግናው ሠራዊት መቆጣጠር መቻሉን ነው ሜጄር ጄኔራል መሠለ የተናገሩት።

የሽብር ቡድኑን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመደምሰስ የምእራብ ትንታጎች እየገሰገሱ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

አሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ኀይል በዳባት ቆርጦ ወደ ጎንደር ለመገስገስና የሑመራን ቀጠና ለማስከፈት ያደረገውን ጥረት በምዕራብ እዝ ትንታጎች ፣ በአማራ ልዩ ኃይል፣ ፋኖ፣ ሚሊሻ፣ በኦሮሚያ ሚሊሻ እና በአካባቢው ሕዝብ መደምሰሱን ነው የተናገሩት።

በማይጠብሪ የገባውን የሽብርተኛው ትህነግ ወራሪ ቡድን፣ ከቅማንት ፅንፈኛ ቡድን፣ ከኦነግ ሸኔ አፍራሽና ከሱዳን የመለመለውን ቡድን አሰልፎ ቢመጣም ደምስሰነዋል ነው ያሉት።

የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄነራል ብርሃኑ ጁላ ከሠራዊቱ ጋር በዓልን በማሳለፋቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።

❝እኛ የምንዋጋው ኢትዮጵያን ለማዳን ነው፤ የሕልውና ጦርነት ነው፤ ጠላት የሚዋጋው ኢትዮጵያን ሊያፈራርስ ነው፤ ከአማራ ላይ ሒሳብ ሊያወራርድ ነው፤ የውጭ ኮሪደር ከፍቶ ኢትዮጵያን ለውጭ ጠላት ለመስጠት ነው❞ ብለዋል። ለፍትሐዊ ዓላማችን ነው የምንዋጋው ነው ያሉት።

ጀነራሉ እንዳሉት ጠላቶች እኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት ሕፃናትን በጦር ሜዳ እያሰለፉ ነው፤ የወዳጆቻቸውን አንገት ይቆርጣሉ፤ አዛውንቶችን ወደ ጦርነቱ ይማግዳሉ። ሽብርተኛው ትህነግ አሁን ላይ ስለተመታ 30 ሺህ ሚሊሻ አምጡ እያሉ ሕዝቡን እያወከቡት ነው ብለዋል። ኋላቀር የሆነ የውጊያ ስልት ተከትለው ቢመጡም ሠራዊቱ ❝እምሽክ❞ አድርጓቸዋል ነው ያሉት፡፡

ሠራዊቱ አዲስ ዓመትን ብቻ ሳይሆን የድል ቀኑን እያከበረ እንደሆነ ጀነራሉ የገለጹት።

በአፋር በኩል መንገድ ሊያስከፍት የነበረው የሽብርተኛው ትህነግ ወራሪ ቡድን ተሸንፎ ወጥቶ አፋርን በፈቃዴ ለቅቄያለሁ እያለ ስለመሆኑም አንስተዋል።

በወሎ አድርጎ ወደፊት ለመገስገስ የሞከረው ኃይልም ውጊያ ጀምሮ ጠልቆ ቀርቷል፤ ኃይላቸው ከጥቅም ውጭ ሆኗል፤ የተረፈውን ነው እየለቃቀምን ያለነው ብለዋል።

ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ እንዳሉት የሽብርተኛው ትህነግ ዓላማ የወደቀ፣ የሞተ፣ የግለኝነት፣ የምቀኝነት ነው፤ የእኛ ዓላማ ግን አንድነት ነው። ኮምቦልቻን ለመያዝ ያሰበው ተቀጥቅጧል ብለዋል።

ሽብርተኛው ትህነግን ለመጨረሻ ጊዜ አከርካሪውን ለማፍረስ እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል።

በጥሞና ጊዜው ያልተጠቀመ፣ እየወረደና እየሞተ ያለ ቡድን ነውም ብለዋል።

የሽብርተኛው ትህነግ ወራሪ ቡድን በወረራቸው አካባቢዎች ከፍተኛ ጥፋት መፈፀሙን ነው ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ የተናገሩት። ትምህርት ቤቶችን፣ ጤና ጣቢያዎችንና መሰል ተቋማትን አውድሟል ያሉት ጄነራል ብርሃኑ ለኢትዮጵያ ነቀርሳ ስለሆነ መጥፋት አለበት ብለዋል።

የአሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ቡድን የመጨረሻ ግብዓተ መሬት የምንፈፅምበት ጊዜ ሩቅ አይደለም ነው ያሉት።

ዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ ደባርቅ(አሚኮ)

Exit mobile version