ETHIO12.COM

ጌታቸው ረዳ “ገዢ መሬት ይዘናል” አሉ፤ የትህነግ ሰራዊት መበተኑ ተሰማ

የአገር መከላከያ ሰራዊት የመልሶ ማጥቃት እንዳልጀመረ ማስታወቁን ተከትሎ አቶ ጌታቸው ረዳ ” ገዢ መሬቶችን ይዘናል” በሚል ቢናገሩም የጀርመን ራዴዮ የትግራይ ነጻ አውጪ ግንባር ሰራዊት በተስፋ መቁረጥ እየተበተነ መሆኑንን ሃላፊዎች አናግሮ አስታውቋል። መንግስት ከተሞች መውደማቸውን ይፋ አድርጓል።

አቶ ጌታቸው በግል የቲውተር አምዳቸው ማለዳ ላይ ባሰራጩት መልዕክት ” መሬት እናት ነች፤ ጥሩ መሬት የያዘ ያሸንፋል” በሚል ኤታማዦር ሹሙ ብርሃኑ ዱላ ለኢሳት ቃለ ምልልስ ሲሰጡ የተናገሩትን በመጥቀስ ” ከሞላ ጎደል ሁሉንም ገዢ መሬቶች ይዘና” ብለዋል። አያይዘውም ጀነራሉን በሽርደዳ አመስግነዋል።

እሳቸው ” በከፊል” ሲሉ ገሺ መሬቶች የተባሉት በትህነግ ሃይሎች ስር መሆኑንን ቢያስታውቁም፣ ለወትሮው ወገንተኛ በመሆን የም፣ኢታወቀው የጀርመን ራዲዮ “የሕወሃት ቃል አቃባይ በአማርኛና በእንግሊዝኛ የሚሰጡት መግለጫ «የተምታታ» ነው” ሲሉ አንድ አስተያየት ሰጪ ነገሩኝ ብሎ ባሰራቸው ዜና ትህነግ ሽንፈት እየደረሰበት መሆኑንን አመልክቷል።

ትህነግ በወረራ በያዛቸው የአማራ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትና የአማራ ክልል ኃይሎች መልሶ ማጥቃት እያደረጉ መሆኑን የዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደርና የሰሜን ወሎ ዞን ባለስልጣናት ባልስልጣኖችን ጠቅሶ የጀርመን ሬዲዮ እንዳለው የትህነግ ሰራዊት በደረሰበት ምት በተስፋ መቁረጥ እየተበተነ ነው።


READ MORE STORIES



ሕወሓት በወረራ በያዛቸው የአማራ ክልል አካባቢዎች የመንግስት ጦር የመልሶ ማጥቃት ጦርነት መጀመሩን የሕወሓት ቃል አቃባይ ለውጭ የመገናኛ ብዙኃን ማስታወቃቸውና በትናንትናው ዕለት ” ለትግራይ ሕዝብ የምትደርሱለት ሰዓት አሁን ነው” የሚል መግለጫ ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ማሰራጨታቸው ይታወሳል።
ሮይተርስ የዜና ወኪል የህወሓትን ቃል አቀባይ ጌታቸው ረዳን ጠቅሶ ትናንት እንደዘገበው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትና የአማራ ክልል ኃይሎች በቅንጅት በሁሉም ግንባሮች በታጣቂዎቻቸው ላይ ጥቃት እንደከፈቱባቸው፣ ጥቃቱም በአየርና በምድርና በከባድ መሳሪያ የታገዘ ስለመሆኑ አስታወቀው ነበር። በውጊያው የትህነግን ሃይል ሊያሸንፍ የሚችል፣ የትህነግ ሃይል ያሻውን ከማድረግ የሚያግደው ምድራዊ ሃይል እንደሌለ ሲናገሩ የነበሩት አቶ ጌታቸው፣ በምድር ላይ ያለው እውነት ሌላ ቢሆንም ድሉ በጃቸው እንደሆነ ደጋግመው እየገለጹ ነው።
“በአማራ ክልል ወገል ጤና፣ ውርጌሳና ሐሮ በተባሉ ግንባሮች ውጊያ ቢኖርም መከላከያ ያሰበውን ሳያሳካ የትህነግ ሃይል ተጨማሪ ቦታዎችን መያዙን አቶ ጌታቸው መናገራቸውን ከውጭ ሚዲያዎች ተውሶ የዘገበው የጀርመን ሬዲዮ የትህነግ ሃይል እየሸሸ መሆኑንን አመልክቷል።
በአማራ ክልል የዋግኽምራ ብሔረሰብ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ተስፋዬ ገብሬ ለዶይቼ ቬለ በስልክ እንደተናገሩት መንግስት በትህነግ የተያዙ አካባቢዎችን ለማስለቀቅ ውጊያ እንደጀመረ አረጋግጠዋል። “ጠላት” ሲሉ የጠሩት ኃይል ላይም ከፍተኛ ጉዳት መድረሱንና እየደረሰ እንዳለ አስታውቀዋል።
ቡድኑ በደረሰበት ምት የተነሳ የያዛቸውን አካባቢዎች በጦርነትም፣ ተስፋ በመቁረጥም ጥሎ እየሸሸ እንደሆነና አስተዳዳሪው አስታውቀው፣ “በተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ መሆኑንን የሚያሳይ ተግባር እያከናወነ ነው” ብለዋል። እሳቸው ባይገልጹትም ከተለቀቁት ስፍራዎች የተገኘ መረጃን ዋቢ አድርጎ መንግስት ባወጣው መግለጫ ትህነግ የህዝብ የኢኮኖሚና የልማት ተቋማትን፣ የህክምና ጣቢአዎችን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ የግለሰብ ማሳዎችንና የተከማቸ ዕህል፣ ንበረት … ከዘረፋ የተረፈውን ማውደሙን አስታውቋል። በሰሜን ወሎና ጎንደር የህዝብና የአገር ሃብት፣ የግለሰብ ሳይቀር ሙሉ በሙሉ መትህነግ ሃይል መውደሙ ይፋ ሆኗል።
በአማራ ክልል የሰሜን ወሎ ዞን የአስተዳደርና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ ኮሎኔል ኃይለማሪያም አምባዬ በበኩላቸው የሕወሓት ኃይል በሁሉም ግንባሮች በመልሶ ማጥቃት ውጊያ እየተመታ እንደሆነ ነው አስታውቀዋል። ነገር ግን የተጠቃለለ መረጃ ለመስጠት ጊዜው ገና መሆኑን ነው ያመለከቱት።
በግንባር ስላለው ጉዳይ የአማራ ክልል ከፍተኛ ሃላፊዎችም ሆኑ መንግስት እስካሁን ያሉት ነገር የለም። ይሁን እንጂ በፓርቲና በአገር ደረጃ በተያዘው ዕቅድ መሰረት በጋው ሲወጣ ጦርነቱን ለመጨረስ የተያዘው ዕቅድ መጀመሩን ማስተባበል በማይቻልበት ደረጃ ላይ ነው።

“ኢትዮጵያ እየሄደችበት ያለው የእድገት ጎዳና ያሰጋናል በሚሉ የውጭ ጠላቶቻችን ከውስጥ ባንዳዎች ጋር በማበር ህዝባችን ላይ የደቀኑትን አደጋ በመቀልበስ ለኢትዮጵያ ህዝብ ድል የምናበስርበት ቀን ሩቅ አይሆንም ”ሲሉ የኢፌዲሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሜ/ጄ ይልማ መርዳሳ14ኛው የሰንደቅ ዓላማ ቀን በኢፌዲሪ አየር ኃይል ጠቅላይ መምሪያ በተለያዩ ዝግጅቶች ሲከበር ተናግረዋል። የእግረኛው ሰራዊት ውጊያ ከመጀመሩ በፊት አየር ሃይሉ ሰፊ ስራ መስራቱን ሲያስታውቁ “አሁን እያካሄድነው ባለው የህልውና ዘመቻ አየር ኃይል የጁንታውን አከርካሪ እየሰበረ ይገኛል” ነው ያሉት።

የጀርመን ሬዲዮ ለምን አቶ ጌታቸውን ወይም ሌላ ሃላፊን ትግራይ ባለው ዘጋቢው አማካይነት አነጋገሮ እንዳላካተተ አልገለጸም። ይሁን እንጂ የአማራ ክልል ባለስልጣናትና መንግስት ማብራሪያ እንዲሰጡት ጠይቆ እንዳልተሳካለት አመልክቷል።

የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር የደረሰበትን ጥቃት ተከትሎ ይህ እስከታተመ ድረስ መልስ አልሰጠም። ወይም በይፋ ያስታወቀው ነገር ስለመኖሩ አልተሰማም። አቶ ጌታቸው ግን ባለስፈው ዓርብ ” እናሸንፋለን” ሲሉ ማስታወቃቸው አይዘነጋም።

Exit mobile version