Site icon ETHIO12.COM

የጀግናው ኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ የመታሰቢያ ሐውልት ቆመ

በደቡብ ክልል በሀዲያ ዞን ሆሳዕና ከተማ የጀግናው ኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ የመታሰቢያ ሐውልት ቆመ። ዛሬ ጥቅምት 7 ቀን 2014 የቆመው የጀግናው ሐውልት ያረፈበት ስፍራ ኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ አደባባይ በመባል ይታወቃል።


ኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ ማንናቸው?

…በዚህ ጊዜ ከጠላት ወገን በተተኮሰ አየር መቃወሚያ የሚያበረው ኤፍ 5 ኢ ተዋጊጀት ተመታ፡፡ ይኼኔ እሱ በዥንጥላ ወርዶ ህይወቱን ማትረፍ ነበረበት፡፡ ነገርግን የሚያበረውንም ጀት ጭምር እንጂ የራሱን ህይወት ብቻ ማትረፍ አልፈቀደም፡፡ እናም የሚያበረውን ጀት በቆራጥነት እየቀዘፈ ወደ ደብረዘይት አየር ማረፊያ ገስግሶ በሰላም አረፈ፡፡ የተመታውም ጀት ተጠግኖ እንደገና ለግዳጅ ተሰማራ፡፡

ሐምሌ 30 ቀን 1969 ዓ.ም በነገሌ ቦረና ግንባር የተሰማራውን የሶማሊያ ጦር የቦንብ ናዳ በማውረድ ጠላትን ብትንትኑን ማውጣቱን ቀጠለ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ሁለት የሶማሊያ ጦር ጀቶችን በአየር ላይ አጋይቶ ጣለ፡፡ የሚገርመው አንዱን የሶማሊያ ጦር ጀት ያጋየው ሶማሊያ ግዛት ውስጥ ዘልቆ ገብቶ መሆኑ ነው፡፡
አሁንም የጀግናው ገድል ይቀጥላል፡-

ሐምሌ 27 ቀን 1969
በዚያ ወቅት ትምክህተኛው የዚያድ ባሬ መንግስት በምስራቅ ኢትዮጵያ ግዙፍ ወታደራዊ ወረራ ይፈፅሞ ነበር፡፡ ይህንን ወረራ ለመመከት ከተሰማሩት የአየር ኃይል (አሜሪካ ሰራሽ ኤፍ 5 ኢ) ተዋጊ ጀቶች መሃል አንዱን የያዘው ይህ ጀግና ነበር። እናም በኦጋዴን ሐረዋ፣ አይሻ፣ በእነኖሜጢ እና በሌሎችም ቦታዎች የሮኬት ናዳ በማውረድ ወራሪውን የሶማሊያ ጦር ባለበት እንዲገታ ከማድረግ ባሻገር፣ 8 የጠላት ታንኮችን ከእነምድብተኛው ረመረመ፡፡ ይህንን ታላቅ ጀግንነት ባስመዘገበ በ10 ሰዓት ልዩነት እንደገና ወደምስራቅ ጦር ግንባር በመብረር የኢትዮጵያን አየር ኃይል ብቃት ያስመሰከረም ነው፡- ይህ ጀግና።


የሶማሊያ ጦር ጀቶች ድሬደዋ ከተማ ላይ ጥቃት ፈፀሙ፡፡ ይኼኔ ለጥቃቱ የአፀፋ መልስ እንዲሰጡ የኢትዮጵያ አየር ኃይል ተዋጊዎች ታዘዙ፡፡ ከታዘዙት ተዋጊዎች መሃል አንዱ ይህ ጀግና ነበር፡፡ እናም ጀቱን እየቀዘፈ የአየር ላይ ትርዒት ጭምር በማሳየት ጀግናው ገድሉን ቀጠለ፡፡ እናም የሶማሊያን ሚግ 21 ተዋጊ ጀት ከነአብራሪው በአየርላይ አጋይቶ በሰላም ወደ ደብረዘይት ተመለሰ፡፡ እነሆ ይህ ጀግና እንዲህ ያለ አኩሪ ገድል የፈፀመ ነው፡፡

ማነው?
ይህ ጀግና ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ይባላል፡፡ (በነገራችን ላይ ኮሎኔል በዛብህ፤የፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ወንድም ነው፡፡) ከላይ የጠቀስነውን ጀግንነት በፈፀመ ጊዜ የሻለቅነት ወታደራዊ ማዕረግ ነው የነበረው፡፡ የሆነ ሆኖ የጀግናችንን አኩሪገድል መተረካችንን እንቀጥል፡፡

ሕዳር 3 ቀን 1970 ዓ.ም፡፡
የሶማሊያ ተዋጊ አውሮፕላኖች ወደ ኢትዮጵያ ገብተው ጥቃት ፈፅመው ተመለሱ፡፡ ይኼኔ ሁለት የኢትዮጵያተዋጊዎች (ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ እና ኮሎኔል ለገሰ ተፈራ) ተከትለዋቸው ገሰገሱ፡- እስከ ሞቃዲሾ ድረስ፡፡ የሶማሊያ አውሮፕላኖች ሞቃድሾ አየር ማረፊያ ደርሰው ለማረፍ ዝቅ ሲሉ፤ ጀግኖቹ ሻለቃ በዛብህና ኮሎኔል ለገሰ ተፈራ እዚያው ደፍቀው አጋዩአቸው፡፡ እናም በሰላም (እየሸለሉ) ወደ ቢሾፍቱ ተመለሱ፡፡ ይህ የጀግኖቻችን ተግባር ለሶማሊያውያን ዘላለማዊ ውርደት ያከናነነበ እንደ ነበር ታሪክ ይመሰክራል፡፡

የጀግናው በዛብህ ጴጥሮስ ገድል ይቀጥላል፡-
ታህሳስ 13 ቀን 1970 ዓም በዛብህ፤ ቶጎ ውጫሌ በሚባል ቦታ ላይ የሚገኝን የሶማሊያ ጦር መሳሪያ ግምጃ ቤት እና መካናይዝድ ክፍለ ጦር መምሪያ በቦንብ እያጋየ ሳለ ከጠላት ወገን በተተኮሰበት አየር መቃወሚያ ጥይትየሚያበረው አውሮፕላን ሞተር ክፍል ተመታበት፡፡ በዛብህ ጴጥሮስ አውሮፕላኑ ክፉኛ ቢመታም አልተደናገጠም፡፡ የተመታውን አውሮፕላን መልሶ ደብረዘይት ለማሳረፍ ታላቅ ጥረት አደረገ፡፡ ሆኖም ጥረቱ አልተሳካም የአውሮፕላኑ ነዳጅ አለቀበት፡፡ በዚህ የተነሳ ደብረዘይትና ሞጆ መሃል በሚገኝ ገላጣ ሜዳ ላይ አውሮፕላኑን አሳርፎ ድርብ ጀግንነቱን አስመሰከረ፡፡

ጀግናው በዛብህ ጴጥሮስ፤ በኢትዮጵያና በሶማሊያ ድንበር ተፈሪ በር በተባለ የጦር መንደር ላይየሚገኘውን (በጥር ወር 1970) የከባድ መሳራያ ግምጃ ቤት እና የጠላት ጦርም ድባቅ መታ፡፡ በዚህ ወቅት 5 የጠላት ታንኮችን ከነምድብተኛቸው ደመሰሰ፡፡ ይሁን እንጂ አሁንም ከጠላት በተተኮሰ ፀረ አውሮፕላን ጥይት ተመቶ የሚያበረው አውሮፕላን በእሳት ተያያዘ፡፡ ጀግናው ይህም ጥቃት አላሸበረውም፡፡ እሳቱን በመከላከያ በማጥፋት ወደመጣበት ተመለሰ፡፡ አሁን ግን ደብረዘይት መድረስ አልቻለም፡፡ አውሮፕላኑን ድሬደዋ አየርማረፊያ አሳረፈው፡፡ አውሮፕላኑም ተጠግኖ እንደገና ለግዳጅ በቃ፡፡

ይህ ጀግና ፤ ከሚያዝያ ወር 1970 ጀምሮ ኤርትራ ወደ ሚገኘው 2ኛው አየር ምድብ እንዲዛወር ተደረገ፡፡ ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ የሶማሊያን ወረራ ለመቀልበስ ከሐምሌ ወር 1969 እስከ የካቲት ወር 1970 በተደረገ የመከላከልም ሆነ የማጥቃት ውጊያ 191 ጊዜ ወደ ጠላት ወረዳ በርሯል፡፡ በዚህ የላቀ እና ታላቅ ሀገራዊ ተጋድሎ ላበረከተው አስተዋፅኦ በወቅቱ የነበረው የኢትዮጵያ መንግስት መስከረም 3 ቀን 1972 ዓ.ም “የላቀ የጦር ሜዳ ጀብዱ ሜዳይ” ሸልሞታል፡፡

እዚህ ላይ ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ ህዳር 21 ቀን 1972 ዓም ለንባብ በበቃው “ታጠቅ” የተሰኘ የሰራዊቱ ጋዜጣ ላይ ከሰጠው ቃለምልልስ የሚከተለውን መጥቀስ ይገባል፡፡ እነሆ፡-

“… እኛ ብንሞት ሌላ ሰው ይተካናል፤ መተኪያ የሌላት ኢትዮጵያ ከሞተች ግን ተተኪው ትውልድ ስለሚሞት ዋጋ አይኖረውም፡፡ የሀገርን ሉአላዊነት በአስተማማኝነት መጠበቅ ቆራጥነት እና ልበ ሙሉነት ይጠይቃል፡፡ እኛ በሕይወት ቆመን እያየን ጠላት አንዲት ስንዝር መሬት ቆርሶ መሄድ ቀርቶ በአንድ እግሩ እንኳ ሊቆምባት አይችልም፡፡ ከሀገር ወዲያ ሌላ መኖሪያ ዋሻ ስለሌለ በሃገርና በነፃነት ጉዳይ ምንም ቀልድ ሊኖር አይችልም፡፡…”

ይህ ጀግናችን የተናገረውን ካለማወላወል በተግባር የፈፀመ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጅ ነው፡፡ ከሶማሊያ ወረራ በኋላ ወደ ኤርትራ ዘምቶ እስከ 1977 ድረስ ግዳጁን በአግባቡ የተወጣ አርበኛ ነው፡፡ በ1977 ዓም ግን ከሻዕቢያ ጋር በናቅፋ ግንባር እየተዋጋ ሳለ አውሮፕላኑ ተመታ፡፡ አሁን ግን ወደ ተነሳበት ቦታ መመለስ አልቻለም፤ በሻዕቢያ እጅ ወደቀ ጀግናችን እስረኛ ሆነ፡፡ በ1983 ዓም ከእስር ተለቆ ከቤተሰቡ ጋር መቀላቀልም ችሎ ነበር፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላ በ1990 ዓም የኢህአዴግ ወዳጅ የነበረው ሻዕቢያ ጠላት ሆኖ መጣ ተባለ፡፡ ባድመን ወረረም ተባለ የኢትዮጵያውያን ቁጣ ነደደ፡፡ የሦሥት ወንዶች እና የሁለት ሴቶች አባት የሆነው ኮሎኔል በዛብህ የሀገሩን ክብር ለማስመለስ እና ሻዕቢያን ለመደምሰስ ዳግም ዘመተ፡፡ እንደ ልማዱ ተዋጊ አውሮፕላኑን እየሰገረ የሻዕቢያን ጦር አከርካሪ መሰባበሩን ቀጠለ፡፡

ግንቦት 5 ቀን 1990 ዓም ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ወደ ኤርትራ ምድር ዘልቀው ከገቡ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ተዋጊዎች አንዱ ነበር፡፡ የሚያበረውን አውሮፕላን ዝቅ፤…. እጅግ ዝቅ….. አድርጎ የኤርትራን እያጠቃ ሳለ አውሮኘላኑ ተመቶ ተያዘና ለእስር ስለመዳረጉ የአንዳንድ ምንጮች ዘገባ ይጠቁማል።

የኢትዮጵያ መንግስት ከኤርትራ ጋር እርቀ ሰላም ካወረደ ከአንድ ዓመት በላይ ቢያስቆጥርም የኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ ጉዳይ በኤርትራ በኩል በይፋ የተገለፀ ነገር የለም።

ምንጭ፡- (የአናብስት ምድር – ደራሲ ታደሰ ቴሌ ሳልቫና፣
የቀድሞ የኢትዮጵያ ሠራዊት ገፅና ሌሎች)

©️ Dire Tube

አብዮታዊውሰራዊትገፅ

Exit mobile version