Site icon ETHIO12.COM

“ደሴ ተያዘች” የሚል ዜና ለማሰራጨት ሰርገው የገቡ ሙሉ በሙሉ ተመቱ፤ የተያዙም አሉ፤ ቦሩ ሜዳና አካባቢው ወገን እጅ ነው

የትህነግ ደጋፊዎችና አባላቶች ደሴ በቁጥጥር ስር እንደዋለች አድርገው እየተናገሩና፣ የአብን አመራሮችን ጨምሮ ከተማዋን ለቀው እንደኮበለሉ፣ መከላከያም እጁን እንደሰጠና ሃይላቸው በወሎ ዩኒቨርስቲ በኩል ወደ ከተማዋ እየዘለቀ እንደሚገኝ በማህበራዊ ሚድያዎቻቸው በሚታወቅም በማይታወቅም ስም የድል ወሬ እያሰራጩ ውለዋል። አሁን ማምሻውን መንግስት ባሰራጨው መግለጫና ከስፍራው ያሉ እንዳሉት ሰርገው የገቡ ጥቂት የትህነግ ሰራዊቶች ግርግር ለመፍጠር ሞክረው ወዲያው ተደምሠዋል። በቦሩ ሜደአም ተቆርጠው የነበሩና ለቀናት ጥሻ ውስጥ የከረውሙ ረሃብና ወሃ ጥም ጠንቶባቸው ተኩስ መክፈታቸው፣ በአጻፋውም ወዲያው መደምሰሳቸው ተገልጿል።

በተቃራኒው ኮበለለ የተባሉት የአብን አመራር አቶ የሱፍ “በቦሩ አቅጣጫም በወንዝ፣ በጢሻና በየሸለቆው ተደብቀው የከረሙት አሁን ረሀብና ውሃ ጥም ሲከብዳቸው ከጉድጓዱ የግድ እየወጡ እሩምታ በመተኮስ ለማደናገር ሞክረው ነበር። እያንዳንዷን የጥይት ተኩስ በሽህ እያባዙ ፕሮፖጋንዳ የሚነፉት ናቸው የወያኔ ቀሪ ጉልበት ለመሆን እየሞከሩ ያሉት። ዛሬ ካስተኳሾች ጋር በርካታ የወሬ ሸቃጮችም በቁጥጥር ስር ውለዋል።ከምር! ሁሉም ነገር በስርዓት ተይዟል፣ በወሬ ተኩስ ከተማ አይገባም! ደግሞ እነሱ ትንኝ ናቸው እንደ ሳይታዩ ገቡ፣ ገቡ፣ ገቡ፣ የሚባለው?” ሲል ወሬ ብቻ መሆኑንን አመልክተው ነበር።

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት “አሸባሪው ሕወሐት መሣሪያዎቹን ሲጨርስ ምላሱን መተኮስ ጀምሯል! ሲል ባሰራጨው መረጃ ” በየጢሻውና በየሸለቆው ተደብቆ ከርሞ ነበር። ለቀናት ከተደበቀ በኋላ ርሃብና ውኃ ጥም ሲከብደው የእሩምታ ተኩስ በመክፈት ከጉድጓድ እየወጣ የአካባቢውን ሕዝብ ለማደናገር ሞክሯል” ያለው ሃይል ጠኔ አንፈራግጦት ለማምለጥ ካደረገው ሙከራ ውጭ ሌላ ይህ ነው የሚባል ጉዳይ እንዳልሆነ አመላክቷል።

ሰሞኑን በደረሰበት ከባድ ምት ከተበታተነው ወራሪ ኃይል መካከል በጣት የሚቆጠረው በቦሩ ሜዳ አቅጣጫ በየወንዙ፣ በየጢሻውና በየሸለቆው ተደብቆ ከርሞ ነበር። ለቀናት ከተደበቀ በኋላ ርሃብና ውኃ ጥም ሲከብደው የእሩምታ ተኩስ በመክፈት ከጉድጓድ እየወጣ የአካባቢውን ሕዝብ ለማደናገር ሞክሯል። አይጥ ከጉድጓዷ በራቀች ቁጥር እንደምትመታው፣ ይሄም የተቆረጠ አሸባሪ ወዲያው ተመትቷል።

የተቆረጠው ኃይል ወደ ሲኦል እየተሸኘ ባለበት፣ በውስጥ ያሠረጓቸው ኃይሎች ጁንታው ወሎ ዩኒቨርስቲ አካባቢን እንደተቆጣጠረ በማስመል የውሸት ፕሮፓጋንዳ እየነዙ ይገኛሉ። ጀግናው መከላከያና መላው የጸጥታ ኃይላችን እነዚህን ባንዳዎች በመልቀም ርምጃ እየወሰደ ነው። ቦሩ ሜዳም ሆነ ከቦሩ ሜዳ ራቅ ያሉት አካባቢዎች በጀግናው የመከላከያ ሠራዊታችን እጅ ላይ ይገኛሉ።

ኅብረተሰቡ የሐሰተኛ ወሬ ፈጣሪዎችንም ሆነ አስተላላፊዎችን ለሕግ እያቀረበ አካባቢውንና ቀዬውን አሁንም በንቃት መጠበቅ ይኖርበታል። የደሴ ከተማ ሕዝብ የሽብር ቡድኑን የሚያሸንፈው በጽናትና በትግል ብቻ ነው።

በወሬ የተገነባ ከተማ ስለሌለ፣ በወሬ የሚያዝ ከተማ አይኖርም! ሊኖርም አይችልም!

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

Exit mobile version