Site icon ETHIO12.COM

«አልረሳውም! እኔም የኢትዮጵያ ሰራዊት ነኝ!»

መንግስት የህወሃት የሽብር ቡድን በመከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ ጥቃት የፈጸመበት ቀን “አልረሳውም! እኔም የኢትዮጵያ ሰራዊት ነኝ!” በሚል መሪ ቃል ታስቦ እንዲውል ውስኔ አስተላለፈ፡፡

አሸባሪው የህወሃት ቡድን አገሪቷን ለ27 ዓመታት ሲበዘብዝ ከኖረ በኋላ በህዝብ ትግል ከስልጣን ተባሮ መቀሌ በመመሸግ የተለያዩ አሻጥሮችን ሲሸርብ ቆይቷል፡፡ ይህ ቡድን ብሄርን ከብሄር፣ ሐይማኖትን ከሐይማኖት ሲያጋጭ የቆየ ሲሆነ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከውስጥም ሆነ ከውጭ ሃይል ጋር በማበር የአገሪቷን ሰላም ለማደፍረስ ሲሰራ ቆይቷል፡፡

የህወሃት የሽብር ቡድን ኢትዮጵያን ለማፍረስ የመጨረሻ ያለውን እርምጃ ጥቅምት 24 በመከላከያ ሰራዊት ላይ በመፈጸም በኢትዮጵያውያን ላይ ግልጽ ክህደት ፈጽሟል፡፡ ጥቅምት 24 የህወሃት የሽብር ቡድን ለሁለት አስርት ዓመታት ሲጠብቀው የኖረውን፣ ቤተሰቡን ሲደጉም እና ሲያግዝ የኖረውን የመከላከያ ሰራዊት ላይ ክህደት በመፈጸም የሰራዊት አባላት፣ የጦር መኮንኖች እና የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ንብረት የሆነው የጦር መሳሪያ በመዝረፍና ከባድ ጥቃት በማድረስ ኢትዮጵያን ያፈራርሳል ያለውን እርምጃ ወስዷል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት የሽብር ቡድኑ የፈጸመውን አገር ክህደት ለመቀልበስ በወሰደው እርምጃም የታገቱ የጦር አዛዦችን በማስለቀቅ፣ የተዘረፉ መሳሪያዎች እንዲወድሙ እና ገሚሶቹ ደግሞ እንዲመለሱ በማድረግ አገርን ከመፍረስ ለመታደግ ተችሏል፡፡

ይህ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የህወሃት የሽብር ቡድን ጥቃት የፈጸመበት ጥቅምት 24 ቀን የኢትዮጵያ መንግስት በልዩ ሁኔታ ቀኑ ታስቦ እንዲውልም ተወስኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሉዓላዊነትን ለመንካት በሽብር ቡድኑ የተወሰደው እርምጃ መቼም የሚረሳ ባለመሆኑ ይህ ቀን በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ ታስቦ ይውላል፡፡ መከላከያ ሰራዊታችን ከፍ ተብሎ የሚታሰብበት ቀንም ይሆናል፡፡

ኢትዮጵያውያን ቀኑን ሲያስቡ “አልረሳውም! እኔም የኢትዮጵያ ሰራዊት ነኝ!” በሚል መሪ ሃሳብ በሰራዊታችን ላይ የተፈጸመውን ግፍ አልረሳውም፤ እኔም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መስክ ሰራዊት ነኝ በሚል መሰለፍ ይገባዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን በሁሉም ዘርፍ ተደራጅቶ አገሩን ከአደጋ መጠበቅ ይገባዋል፡፡

ጥቅምት 24 በመላው አገሪቱ የሚገኙ የመንግስት ተቋማት ያሉ ሰራተኞች እና ማህበረሰቡ አንድ ላይ በመሆን ለ45 ሰኮንዶች እጃቸውን ደረታቸው ላይ አድርገው አስበው እንዲቆዩ ይደረጋል፡፡ ህወሃት በአፈቀላጤው በኩል መብረቃዊ ጥቃት ያለውን በ45 ደቂቃ የፈጸመ በመሆኑ የደም ልገሳን ጨምሮ የሻማ ማብራት ፕሮግራም ይካሄዳል፡፡

ቀኑ የሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን በማሰብ እኛም ሰራዊት በመሆን ቃል የምንገባበት እንዲሆን ይጠበቃል፡፡ አሁን የኢትዮጵያ ጠላቶች አንገታቸውን የሚደፉበት ኢትዮጵያውያን ግን ቀና የሚሉበትና አገራቸውን ለመጠበቅ ቃላቸውን የሚያድሱበት መሆን ይገባዋል፡፡
ህወሃት አገር ለማፍረስ ያሰለፈውን መንጋ መመከት የሚቻለው እንደ ህዝብ በመንቀሳቀስ ነው፡፡ ህወሃት እየዘረፈ እና እየገደለ አገር ለማዳከም የሚያደርገውን እንቅስቃሴ በጋር መግታት ያስፈልጋል፡፡

ህወሃት የፈለፈላቸው ሸኔን የመሰሉ ድርጅቶችን ጨምሮ አገር ለማፍረስ የቋመጠውን ሃይል እንደ ህዝብ መግታት ያስፈልጋል፡፡
የሽብር ቡድኑ ጥቅምት 24 የፈጸመው ግፍ መዳረሻው አገር ማፍረስ በመሆኑ ተስፋ የቆረጠና ለመሞት የተዘጋጀ ቡድን በማሰለፍ እንዲሁም ሰርጎ ገቦችን በማደራጀት አገርን የማወክ እንቅስቃሴውን ቀጥሎበታል፡፡ ይህ ቡድን ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከሚፈልግ የወጭም ሆነ የውስጥ ሃይል ጋር በማበር የጀመረውን እኩይ ተግባር መግታት የሚቻለው በጋራ በመሰለፍ በመሆኑ በሁሉም የአገሪቱ አቅጣጫ ያለው ኢትዮጵያዊ አገርን ከወራሪዎች ለመታደግ ቆርጦ ሊነሳ ይገባዋል፡፡

አልረሳውም! እኔም የኢትዮጵያ ሰራዊት ነኝ!

በኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኑኬሽን አገልግሎት

Exit mobile version