Site icon ETHIO12.COM

የአዲስ አበባን ሰላምና ፀጥታ ያቀረበውን ጥሪ ተከትሎ ሕዝብ መረጃ እየሰጠ ነው

በአዲስ አበባና አካባቢዋ ሕዝብ ከፍተኛ በሚባል ደረጃ መረጃ እየሰጠና አካባቢውን ነቅቶ ለመጠበቅ እየተደራጀ መሆኑ ተሰማ። የአዲስ አበባ ተባባሪ ዘጋቢያችን የፖሊስ ሃይሎችን ጠቅሶ እንዳለው ነዋሪዎች በሚገርም ሁኔታ መረጃና ጥቆማ በማድረስ ላይ ናቸው።

በምስል የተደገፉ መረጃዎች ሳይቀሩ ለህግ አስከባሪው አካልና መዋቅር ዜጎች እያደረሱ መሆኑንን ተከትሎ መንግስት የመለየት ስራ እየሰራ መሆኑንን፣ ፋታ በማይሰጡ ጉዳዮች ላይ መመሪያ በማስተላለፍና በቅርብ ክትትል የሚደረግባቸውን ለይቶ እየሰራ መሆኑንን የመረጃው ሰዎች ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ አስተዳደር ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ያቀርበውን ጥሪ ተከትሎ ሕዝብ እያሳየ ያለው ተሳትፎ አኩሪ መሆኑን የጸጥታ አካላት በደፈናው አስታውቀዋል። አስተዳደሩ ያወጣው መግለጫ የሚከተለው ነው

ከዚህ በተጨማሪም ግብረ ኃይሉ ሽብርተኛው ቡድንና ደጋፊዎቹ ህብረተሰቡን ለማደናገርና የጥፋት ተልዕኮአቸውን እውን ለማድረግ ይረዳቸው ዘንድ የተለያዩ የፀጥታ አካላትን የደንብ ልብስ በመልበስ ለመንቀሳቀስ ዕቅድ እንዳላቸው የደረሰበት መሆኑን እየገለፀ ይህንን መሰል አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙት በአካባቢው ላለ የጸጥታና የደህንነት ተቋም በአስቸኳይ እንዲያሳውቅ ጠይቋል

መግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፡

የአዲስ አበባን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ የተቋቋመው የደህንነትና የፀጥታ ግብረ ኃይል በሽብርተኛው ህወሃት ደጋፊዎችና ናፋቂዎች ላይ እየወሰደ ያለውን ህጋዊ እርምጃ አጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቋል፡፡ የህዝብ ድጋፍ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባልም ብሏል፡፡

የአዲስ አበባን ሰላምና ፀጥታ በሚፈታተኑ ጉዳዮች ላይ የማያዳግም ህጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን የደኅንነትና የፀጥታ የጋራ ግብረ ኃይሉ አስታውቋል።

ግብረ ኃይሉ በጥምረት በመስራቱ የአዲስ አበባ ከተማን ሰላምና ደህንነት ማስጠበቅ ችሏል፡፡ይህ የተቋቋመው ግብረ ኃይል አሸባሪው የህወሃት ቡድን አገሪቱን ወደ ግጭትና ትርምስ በመክተት ኢትዮጵያን ለማፍረስ የጎነጎነውን ሴራ ለማክሸፍ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል፡፡የኢትዮጵያ ቀንደኛና አደገኛ የሰላም ስጋት የሆነው ይህ አሸባሪ ቡድን ህዝቡን ለማሸበር እና ለማደናገር አሁንም የተዛቡና ሀሰተኛ መረጃዎች እያሰራጨ ይገኛል፡፡

የሽብር ቡድኑ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ/ም በሰሜን ዕዝ ላይ ከፈፀመው ጥቃት ባለፈ ሀገር የማፍረስ ዓላማውን አጠናክሮ በመቀጠል ሀገሪቷን የእልቂት አውድማ ለማድረግ መረቡን ዘርግቶ ቢንቀሳቀስም በህዝብና በፀጥታ አካላት ትብብር ዓላማው እየከሸፈ ነው፡፡

ቡድኑ ለ27 ዓመታት ሲያደርገው እንደነበር ዛሬም በህዝቦች መካከል የተለያዩ የጥላቻና የልዩነት ወሬዎችን በማናፈስ ህዝብ በህዝብ ላይ እንዲነሳ ልዩ ልዩ ሴራዎችን ሸርቦ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ለሁሉም ግልፅ ነው፡፡ የጥፋት ኃይሉ በተደጋጋሚ ባስተላለፈውና ደጋፊዎች ባናፈሱት የተዘባ መረጃ በአማራ እና በአፋር ክልል በርካቶችን ከቀዬቻው አፈናቅሏል በደረሰበት ቦታ ሁሉ ንፁሃንን ገድሏል፡፡

ሽብርተኛ ቡድኑን ሙሉ በሙሉ ለመደምሰስ መንግስት እየወሰደ ያለው ህጋዊ እርምጃ ውጤታማ እንዲሆን የነቃ የህዝብ ተሳትፎ ወሳኝ ስለሆነ መኖሪያ ቤት ተከራይተው በጋራ የሚንቀሳቀሱ፣ ሰዋራ ስፍራ በመምረጥ ግንኙነት የሚያደርጉ የሽብር ቡድኑ ደጋፊዎችና ናፋቂዎች መኖራቸውን ህብረተሰቡ ተገንዝቦ መኖሪያ ቤት፣ ንግድ ቤት፣ መጋዘን እና ተሽከርካሪ ያከራያችሁ ግለሰቦችና ድርጅቶች የተከራዮችን ማንነት በጥንቃቄ በማጣራት መረጃውን በአስቸኳይ ለፖሊስ እንድታሳወቁ ግብረ ኃይሉ ያሳስባል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ግብረ ኃይሉ ሽብርተኛው ቡድንና ደጋፊዎቹ ህብረተሰቡን ለማደናገርና የጥፋት ተልዕኮአቸውን እውን ለማድረግ ይረዳቸው ዘንድ የተለያዩ የፀጥታ አካላትን የደንብ ልብስ በመልበስ ለመንቀሳቀስ ዕቅድ እንዳላቸው የደረሰበት መሆኑን እየገለፀ ይህንን መሰል አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙት በአካባቢው ላለ የጸጥታና የደህንነት ተቋም በአስቸኳይ እንዲያሳውቅ ጠይቋል።

የአዲስ አበባን ሰላምና ደህንነት ለማስጠበቅ በሽብርተኛው የህወሃት ደጋፊዎችና ናፋቂዎች ላይ የሚወስደውን ህጋዊ እርምጃ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የጋራ ግብረ ኃይሉ እያስታወቀ ሀሰተኛ መረጃ የሚያስተላለፉ እና የሚያስተጋቡ አካላት ከህገወጥ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጥብቅ መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡

ለከተማችን ሰላምና ደህንነት እየተጋ የሚገኘው የፀጥታ አካላችን በሽብርተኛው ህወሃት ደጋፊዎችና ናፋቂዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን ህዝቡ ተገንዝቦ በየአካባቢው በመደራጀትና በመቀናጀት ለፀጥታ አካሉ እየሰጠ ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል የጋራ ግብረ ኃይሉ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ህብረተሰቡ አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙት ወይም የፖሊስ አገልግሎትን ማግኘት ሲፈልግ በ011-1-11-01-11 ወይም በነፃ ስልክ መስመር 991፣ 997 መጠቀም እንደሚችል የደህንነትና የፀጥታ የጋራ ግብረ ኃይሉ አስታውቋል፡፡

ጥቅምት 23 ቀን 2014 ዓ.ም

አካባቢዎን ይጠብቁ!

ወደ ግንባር ይዝመቱ!

መከላከያን ይደግፉ!

Exit mobile version