Site icon ETHIO12.COM

ጨለማውን እያጠራን ያለነው፣ ብርሃናማ እውነት ስለያዝን ነው!

የአሜሪካ ህዝብ ይጠይቅ!

ትህነግ በጫረው እሳት እየነደደ ብቻ አይደለም። እየተቃጠለ ነው። እንደ ትህነግ እሳት እጭራለሁ የሚል ካለም ነድዶ እንደሚያርር ጭምር በግላጭ እያየን ነው። መላው ኢትዮጵያ አሸባሪውን ህወሓት ከነግብረአበሮቹ ሊቀብር ‘ሆ’ ብሎ ተነስቷል። የአገሩ መወረር ህመም ፈጥሮበታል። መጠቃት አንገብግቦታል። በየከተማ ገጠሩ ጁንታውን እያወገዘ፣ ለአገሩ ለመዝመትና ለመሰዋት ‘ሆ’ እያለ ኢትዮጵያዊነቱን እያስመሰከረ ነው።

ኢትዮጵያዊ እንዲህ ነው!! መቼም በማታውቀው ሁኔታና አጋጣሚ ትሞታለህ። ይህ የተፈጥሮ ህግ ነው። አንተ፣ አንቺና እኔ እያለን ግን ሀገራችን ስትጠፋ፣ እያየን ከምንም በላይ ከንቱ በሆነ አልባሌ ሁኔታ እንድንሞት አንፈቅድም።

የከንቱዎች ከንቱ ሞት የምትሞተው፣ ካጋጣሚና ከሁኔታ የዘለለ ውርደት የምትዋረደው አንተ በህይወት ኖረህ አገርህ የጠፋች እንደሆን ነው። አገር አጥፊ በሆነው ተላላኪው ትህነግ አገራችን ስትጠፋ አንመለከትም፤ በቁም እስክንሞት አንጠብቅም ብለው ኢትዮጵያውያኖች ከያሉበት ‘ሆ’ ብለው ተነስተዋል። ጁንታውን እያሳደዱ መቅበሩንም ተያይዘዋል።

ትህነግም እንደ ልማዷ በውጭ አገራት ጩሀቷን ማቅለጡን ተያይዛዋለች። ከጥቂት ቀናት በኋላ ደግሞ ሜዳ ለሜዳ መንከባለሏን ትቀጥላለች። የሚያድናት አንዳች ሀይል ግን የለም።

አሸባሪውን ቡድን ከገባችሁበት ትቀበራላችሁ ያላቸው የኢትዮጵያ ህዝብ በያሉበት ይቀብራቸው ይዟል። ላይጨርስ አይጀምርምና፣ ሳይጀምር በተደጋጋሚ አስጠንቅቋል። አሁን ግን ጀምሯል፣ በድልም ይጨርሳል!!

ይህ የአድዋ ያህል የገዘፈ ታሪካዊ ጠላትን ድባቅ የመምቻ ዘመቻ የሽብር ቡድኑ ላአንዴና ላይመለስ የሚቀበርበት ታላቅ የአገር ህልውና ማረጋገጫ ዘመቻ ነው። ይህ ዘመቻ ከአሸባሪው ትህነግ ጋር በሚደረግ ፍልሚያ ብቻ የሚጠናቀቅ ሳይሆን ብዙ ጦርነቶችን ማሸነፍ የግድ የሚል ነው። ጦርነቱን በድል ለማጠናቀቅ አንድነታችንን ማዝለቅ ቀዳሚው ነው። በዚህ የጠነከረ አንድነት ድርስ አደጋ የሆነውን ተላላኪና ግብረአበሮቹን በያሉበት መደምሰስ ወሳኝ ነው።

በብልሃት ዙሪያ ገባውን በማየት ከወዳጅ አገራትና መንግስታት ጋር ግንኙነትን ማጠናከር የግድ የሚል ነው። ከጁንታው የወገኑ አሰላሳይ አገራትና መንግስታት እየተሳሳቱ መሆኑን በአስረጂ እያቀረቡ ከገቡበት የተሳሳተ መንገድ እንዲወጡ በዲፕሎማሲ መጫንና መስራት አስፈላጊ ነው። ትርፍና ኪሳራቸው ከኢትዮጵያ ህልውናና ህዝብ በታች መሆኑን አውቀው ከጣልቃ ገብነት እጃቸውን እንዲሰበስቡ አልያም በሉዓላዊ ምድራችን ላይ ቅንጣት መፈፀም እንደማይችሉ፣ ለዚህም ህዝቡ እንደማይታገሳቸው ማሳወቅና በፅኑ ማስገንዘብ የግድም ነው።

ኢትዮጵያ የደስታ ጊዜ ብቻ ሳይሆን የመከራ ጊዜም አገራችን ናትና ዜጎች በበሬ ወለደ ትርክት ሳንረበሽ፣ በታማኝነትና በፍፁም አገራዊ ስሜት ለአገራችን ሁሉን መክፈል ያለብን ዛሬ ነው። ከኢትዮጰያ ሊጠቀሙ የመጡ ባለሃብቶችና የውጭ ኢንቨስተሮች በችግራችንም ወቅት አብረው በመሆን መስራት ያለባቸው መሆኑን በጽኑ ማስገንዘብም ይገባል። ዛሬ የዳመነ የመሰላቸው ፀሃይዋ ቅርብ ነችና ለብርሃኗ ድምቀት አብረው ይስሩ፣ አብረውንም ይዝለቁ።

የረድኤት ድርጅቶች ነን የሚሉ አካላት ለአገራችን ከሰጡት ይልቅ የወሰዱት ይበልጣልና በዚህ አጋጣሚ መንግስት ትርፍና ኪሳራችንን አስልቶ እውነቱን ለህዝቡ ያሳውቅ። አንዳንድ ኤምባሲዎች ሳይቀሩ በቪዛና ኮቴ ሰበብ ከአገራችን ህዝቦች የሚሰበስቡት ረብጣ “በእኛ ርጥባን ነው የምትኖሩት” ብለው እንደሚፎክሩት እንዳልሆነ ያስረዳልና፣ ይልቁንም ከህዝባችን የሚወስዱት ገንዘብ እኛ እየረዳናቸው እንደሆነ ያስገነዝባልና ይፈተሽ። ትርፍና ኪሳራችንም ይለይ።

በተለይ በተለይ በዚህ ህልውናችንን ለማረጋገጥ በቆምንበት ወቅት፣ የአሜሪካ መንግስት አይናችሁን ጨፍኑና ላሞኛችሁ አይነት ብሂሉን ይተወን። ከአሸባሪው ትህነግ ጋር ያለውን ተዛምዶ በፍጥነት ይመርምር። በአሜሪካ የስለላ ቢሮ ሲአይኤ ጥቁር መዝገብ የተመዘገበው ትህነግ፣ የአሜሪካንን ህዝብ በሽብር ከጨረሰው አልቃዒዳ የጥፋት ተግባር በምን ስለተለየ ነው የባይደን አስተዳደር ጁንታውን ወዳጄ ያለው? ብሎ የአሜሪካ ህዝብ ይጠይቅ። የአሜሪካ ህዝብ ህጋዊውንና ታሪካዊ ወዳጃችን የሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ የመረጠውን መንግስት ተቃውመህ በጥቁር መዝገብ ያሰፈርከውን አሸባሪው ትህነግን መወዳጀትህ ለምንድን ነው ብሎ ይጠይቅ? አሸባሪነትን እየመረጥክ መዋጋትክን አቁም ይበል።

የአሜሪካ ህዝብ ወዳጅ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ እንጂ አሸባሪው ትህነግ አይደለም። አሜሪካውያን የአሸባሪነትን አውዳሚ ገፅታ ከማንም በላይ ይረዱታል፤ የአሜሪካ መንግስትስ ምን ያህል ይረዳዋል፣ በየቀኑ በወረራ በያዛቸው ቦታዎች ንጹሃንን ሲጨፈጭፍ፣ እንደ አይኤስ በማይካድራ፣ በጋሊኮማ፣ በኮምቦልቻ ንጹሃንን አግቶ ስላረደው አረመኔው ትህነግ ምን ይላል?

የትግራይ ወጣቶችና ሴቶችን በግዳጅ ጦርነት በመማገድ እያስጨረሰ ያለውን አሸባሪው ህወሓት መደገፍ፣ አልቃዒዳን ከመደገፍ በምን ይለያል? የአሜሪካ መንግስት በኢትዮጵያ ጉዳይ ያለው እይታ፣ የአሜሪካን ህዝብ ሞራል፣ ስነ ምግባርና ያለፈ ጊዜ በደል ምን ያህል ይክሳል? ያስከብራል? የአሜሪካ ህዝብ የባይደን አስተዳደርን ይጠይቅ!

ደመናውን መግፈፍ የሚያስችል ብርሃናማ ዘንግ ይዘናል፤ ጨለማውን እያጠራን ወደፊት ማለታችንን እንቀጥላለን። ወደፊታችን በህዝባችን ነው። ለእኛ ከላይ ያለው ህዝባችን፣ ህጋችን፣ አገራችንና እውነትን የያዘ ፈጣሪ እንጂ ከሽብር የወገኑና ያደሙ የውጭ መንግስታት ወይም፣ የተላላኪዎች ጎሬ የሆኑ እንደ ግብፅ መንግስት ያሉ በታሪካዊ ጠላትነት የተሰለፉ ሀይሎች አይደሉም።

ለግል ጥቅሞቻቸው ሲሉ በማንነታችን ላይ በጠላትነት የሚሰለፉ ስላሉ፣ አንቆምም፤ ይልቁንም ተራምደን እንሻገራቸዋለን። ታላቁ ህዳሴ ግድባችን አንዱ ርምጃችን ነው። እሱን ስንራመድ፣ አንድ ተላላኪና አጥፊ ቡድን እናስቆማለን። ጁንታውን ለማጥፋት ስንሰራ፣ ታላቁ ህዳሴ ግድባችንንና የየአካባቢያችንን ልማትና ሰላም እያረጋገጥን ይሁን። ሃያ አራት ሰባትም በትጋትና በፅናት እንኑር። ድሉ ለህልውናችን ፀንተን እየዘመትን ያለነው የእኛ የኢትዮጵያ ህዝቦች ነው።

አካባቢዎን ይጠብቁ!
ወደ ግንባር ይዝመቱ!
መከላከያን ይደግፉ!

ENA

Exit mobile version