Site icon ETHIO12.COM

የኦሮሚያ ክልል “ሕገወጥ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር” በሚል የሰዓት እላፊ ገደብ ጣለ

በኦሮሚያ አዲስ አበባ መዳረሻ ከተሞች በርካታ መሳሪያ፣ የወንጀል እቅዶች ማስፈጸሚያ ገንዘብ፣ የማንነት መሰወሪያ መታወቂያዎችና ከሽብር ጋር የተያያዙ ማስረጃዎች በሕዝብ ጥቆማና ደጋፍ በቁጥጥር ስር እየዋሉ መሆኑ ቢታወቅም በአስቸኳይ አዋጁ መመሪያ መሰረት የሰዓት እላፊ ገደብ ጥሎ የክልሉን ሰላም ማጠናከር አስፈላጊ በመሆኑ በኦሮሚያ የሰዓት እላፊ መታወጁ ተሰማ። “የተለይ ስጋት የለም፣ ለጥንቃቄ ነው” ተብሏል።

የኦሮሚያ ክልል ኮሚኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ግዛቸው ገቢሳ እንደተናገሩት፤ በክልሉ የሰዎችና የተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴን በመለየት ከምሽቱ 2 ሰዓት እስከ ንጋቱ 11፡30 ድረስ እንቅስቃሴ ማድረግ ተከልክሏል መከልከሉን አመልክተዋል። በዚህም መሠረት ሰዎች ከንጋቱ 11፡30 እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ፣ተሸከርካሪዎች ደግሞ እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት ብቻ መንቀሳቀስ የሚችሉ መሆናቸው ሃላፊው ያስረዱት ለቢቢሲ ነው።

ጨምረውም ከሰዓት እላፊው በተጨማሪ “በመንገድ ላይ ፍተሻዎች ይኖራሉ። ድንገተኛ ፍተሻ ይካሄዳል፤ በኬላዎችም ላይ ፍተሻ ይደረጋል። በመንግሥት መስሪያ ቤቶችና ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎችም ፍተሻዎች ይካሄዳሉ” ብለዋል።

አቶ ግዛቸው ገቢሳ አብዛኛዎቹ ፍተሻዎች ምሽት ላይ የሚካሄዱ መሆናቸውን ጠቁመው ፍተሻዎቹ ዘላቂ ላይሆን ይችላሉ ብለዋል። የክልሉ ኮሚኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ ጨምረው እንደተናገሩት፤ በክልሉ የሚገኙ አከራዮች የተከራዮቻቸውን መታወቂያ በመያዝ በቀበሌና በአቅራቢያቸው በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እየሄዱ ማስመዝገብ እንዳለባቸው ተናግረዋል።

“አዲስ ተከራይ፤ ያለመታወቂያ ቤት ማከራየት የለባቸውም። መታወቂያ የሌላቸው ተከራዮች ካሉም መታወቂያ እንዲያወጡ ጊዜያዊ አሰራር ተዘርግቷል” ብለዋል።

ምክትል ኃላፊው በክልሉ ይህን መሰል አዋጅ ማውጣት ያስፈለገው “ሰርጎ ገቦች በክልል ሰላም እንዳያደፈርሱ ለመከላከል ነው” ብለዋል። “በአገር አቀፍ ደረጃ የተረጋጋ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዳይኖር ለማድረግ የተለያዩ እንቅስቀሴዎችን የሚያደርጉ አካላት ሰርገው ገብተው ሕዝብ እና ንብረት ላይ ጉዳት እንዳያደርሱ በሚል ነው” ሲሉ ክልሉ ውስጥ የተጣለውን የሰዓት እላፊ ገደብ ምክንያት አብራርተዋል።

“በክልሉ የተለየ ስጋት የለም” የሚሉት አቶ ግዛቸው፤ “… በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች የህብረተሰቡን የእለት ተዕለት እንቅስቃሴ የሚያናጉ ሕገ-ወጥ የመሳሪያ ዝውውርና ሕገ-ወጥ የንግድ ተግባራት አሉ። እነዚህን ለመከላከል ታስቦ ነው የሰዓት እላፊው የተጣለው” ብለዋል።

ይህን የመንግሥት አዋጅ ተከትሎ የዜጎች መብት እንዳይጣስ በመንግሥት የጸጥታ አስከባሪ አካላት ከፍተኛ ጥንቃቄ ይካሄዳል ያሉት አቶ ግዛቸው፤ የአዋጁ መመሪያ ለጸጥታ አስከባሪ አካላት ተላልፏል ይላሉ።

የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ አዱኛ አሕመድ ሕገወጥ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር የሰዓት እላፊ ገደብ መጣሉንና ከዚሁ ጋር በተያያዘም በክልሉ ውስጥ መሳሪያ ያላቸው ነዋሪዎች በአስር ቀናት ውስጥ እንዲያስመዘግቡ መታዘዙን ለፋና ተናግረዋል።

ከህወሓት ጋር አጋርነት የፈጠረውና በሽብርተኝነት የተፈረጀው መንግሥት ሸኔ የሚለውና እራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር ብሎ የሚጠራው ታጣቂ ቡድን በተለያዩ የኦሮሚያ ዞኖች ውስጥ ጥቃት ሲፈጽም መቆየቱ ይታወሳል። BBC Amharic


Exit mobile version