ETHIO12.COM

በቆቦ 600 የሚደርሱ ንጹሃን መቀበራቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ገለጹ

ቆቦ፦ አሸባሪው ሕወሓት በቆቦ ከተማ በአንድ ቀን 89 ንጹሃን ገድሎ በጅምላ መቅበሩን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ። የሟች ቤተሰቦችም አስከሬን እንዳያነሱና እርማቸውን እንዳያወጡ በመከልከል ይቅር የማይባል ግፍ መፈጸሙንም ገልጸዋል።

የከተማው ነዋሪ አቶ አበበ ዘውዴ እንደገለጹት፤ በከተማው በሦስት ዙር ከተደረገው ውጊያ የበለጠ የሚከፋው የራያ አርበኞች፣ ሚሊሻና ታጣቂዎች የሽብር ቡድኑን ለመከላከል ጳጉሜን 04 ቀን 2013 ዓ.ም ያደረጉት ነው። አሸባሪው የሕወሓት ቡድንም በዚህ ቂም በመያዝ በየአካባቢው ያገኘውን አርሶ አደር፣ ወዛደር፣ እናቶችን በአማራነታቸው ለይቶ መጨፍጨፉን ተናግረዋል። በአጠቃላይ በወረራ በቆየባቸው ጊዜያት 600 የሚደርሱ ንጹሃን መቀበራቸውንም ተናግረዋል።

በቆቦ ከተማ ብቻ ጳጉሜን 05 ቀን 2013 ዓ.ም አሸባሪው ሕወሓት የጨፈጨፋቸው 89 ንጹሀን ዜጎች በጅምላ መቀበራቸውን አመልክተዋል። በማግስቱ የዘመን መለወጫ ዕለትም 16 ንጹሀን ተቀብረዋል። ይህ አሀዝ በአካባቢው ገጠር ቀበሌዎች የተቀበሩትንና የተሰወሩትን እንደማያካትትም አቶ አበበ ጠቁመዋል።

ሦስት የቤተሰባቸው አባል የተገደሉባቸው ወ/ሮ ወርቄ ጉብሳ፤ በዕለቱ በአካባቢያቸው ከፍተኛ የተኩስ እሩምታ ይሰማ ነበር ብለዋል። ምሽት 11:00 ሰዓት ገደማ ቤት ውስጥ በመግባት ሰባት ሆነው ተሸሽገው ከነበሩት ህጻናትን ትተው አራቱን እንደወሰዷቸው ተናግረዋል።

‹‹እባካችሁ አትውሰዷቸው፣ ገበሬ ናቸው የሚያውቁት ነገር የለም ብላቸውም ተጠይቀው ይመለሳሉ በማለት እየገፈተሩና እየተቆጡ እንደወሰዷቸው፣ አንደኛውን ክንዱን መትተውት ቆስሎ መመለሱን›› አስታውሰዋል። 

“በነጋታው ማለዳ ተነስቼ ፍለጋ ወጣሁ ከእኔ ቤተሰቦች ጭምር አራት ሰዎች አንድ ቦታ ተገድለው አገኘኋቸው ፤ነጠላ አለበስኳቸው፤ ተደፍቼ አለቀስኩ” ብለዋል። “አንቺንም እንዳንገድልሽ ዝም በይ” በማለት እንዳስፈራራቸው ጠቁመዋል። 

“እኔንም ግደለኝ” ቢሉም በማመናጨቅና በመገፈታተር እንዳባረራቸው ይናገራሉ። አስከሬኖቹ ጸሃይ ላይ ውለው አድረው ሽማግሌ ተልኮ ሳያለቅሱ እንዲያነሱ እንደተፈቀደ ተናግረዋል።

ሁለት ወንድሞቻቸውና የእህታቸው ባለቤት የተገደሉባቸው ወ/ሮ ጉዝጉዝ እጅጉ እንደገለጹትም፤ አስከሬን ከወደቀበት ያነሱት ሽማግሌ ልከው መሆኑን፣ በኬሻ ጠቅልለው አስክሬኖቹን ሳያጥቡ መቅበራቸውን ገልጸዋል።

በዕለቱ ጉድጓድ የሚምስ ጠፍቶ ብዙዎችን እየደራረቡ ሲቀበሩ መመልከታቸውን፣ እንዳያለቅሱ መከልከላቸውን በመጠቆምም፤ ምሽት ቤት እያንኳኩ ሲያስቸግሯቸውም ጥለው ወደ ገጠር መሰደዳቸውን ተናግረዋል። ሲመለሱም ቤታቸው ተዘርፎና ወድሞ እንዳገኙት አመልክተዋል።

የተጎጂዎቹ ጎረቤት አቶ ሞላ ንጉሴ አራት ልጆች አንድ ቦታ መገደላቸውን እንደተመለከቱ ተናግዋል። ከወደቁበት በቃሬዛ ሦስቱን አንስተው ሲወስዱ አንደኛውን አስከሬን ስላልለዩት ወደ ጥግ አድርገው ትተውት መሄዳቸውን ገልጸዋል። አሸባሪ ቡድኑ ለቅሶ ስለከለከለ አስከሬኖቹ ሳይታጠቡና አስፈላጊው የሃዘን ስነስርዓት ሳይደረግላቸው በኬሻ ጠቅልለው ለቀብር እንደወሰዷቸው መስክረዋል።

ዘላለም ግዛው አዲስ ዘመን ታህሳስ 15 ቀን 2014 ዓ.ም

Exit mobile version