ETHIO12.COM

ሆሮ ጉድሩ በሙሉ ወታደራዊ ኦፕሬሽን ውስጥ ገባች፤ 433 የሸኔ አባላት ተደመሰሱ፣115 እጅ ሰጡ፣623 በቁጥጥር ስር ዋሉ

ሆሮ ጉድሩ በዉሉ ወታደራዊ ኦፕሬሽን ውስጥ እንደምትገኝ ተሰማ። የክልሉ የጸጥታ ሃይል በሙሉ ሃይሉ እርምጃ እየወሰደና ዋና ምሽጉ ከሆነበት ሆሮ ጉድሩ ለማጽዳት እየተካሄደ ባለው ዘመቻ 433 የሸኔ ታጣቂዎች ተገድለዋል። የተያዙና እጃቸውን የሰጡ በርካታ መሆናቸው ታውቋል። ሸኔ ሕዝብ የሚጠቀምበትን መሰረተ ልማትና አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ለምን እንደሚያወድም ለአብዛኞች ግራ እንደሆነ እየተጠቆመ ነው።

የዞኑንን አስተዳዳሪ ጠቅሶ ዋልታ እንደዘገበው ከሆነ የተጀመረው ኦፕሬሽን ሕዝብ በምሬት የተሳተፈበትና ሰፊ ሽፋን ያለው ነው። ምስክሮች እንዳሉት ደግሞ ከበባውን ለማደናቀፍና ወታደራዊ ስምሪቱን ለማወክ መንገድ ቢቆርጥም ህዝብ እየጠቆመ በቡድኑ ላይ እስካሁን ከተፈጸመው በላይ ጉዳት ደርሷል።

በሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞን እስካሁን በተካሄደ ኦፕሬሽን 433 የአሸባሪው ሸኔ ቡድን አባላት ሲደመሰሱ 115 አባላቱ ደግሞ መማረካቸውን የዞኑ አስተዳደር አመልክተው ዘመቻው በስፋትና እግር በእግር ተጠናክሮ መቀጠሉን ይፋ አድርገውዋል። ከቢኒሻንጉልና ኦሮሚያ አዋሳኝ ላይ መከላከያ የሚመራው ዘመቻም ቀለበቱን እያጠበበ ወደ ወለጋ እንደገፋቸው ባለፈው ሳምንት መዘገቡ ይታወሳል።

የዞኑን ሰላም ወደ ቦታው ለመመለስ ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በቅንጅት በመስራት አስተማማኝና ውጤታማ ኦፕሬሽን በዞኑ እየተካሄደ ስለመሆኑ የገለፁት የሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ በቀለ ደቻሳ ናቸው።

በዚህም ወደ 433 የአሸባሪው ሸኔ ቡድን አባላት ሲደመሰሱ 115ቱ ተማርከዋል፤ የቡድኑ የመረጃ እና የሎጅስቲክስ ክንፍ የሆኑ ወደ 623 የሚደርሱ አባላትን በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉንም ተናግረዋል።

እንዲሁም ጠላት ሲጠቀምባቸው የነበሩ ዘመናዊና ኋላ ቀር የጦር መሳሪያዎችም ገቢ የተደረጉ ሲሆን የሽብር ቡድኑን እንቅስቃሴ በማጤን አስፈላጊውን ምላሽ እየሰጠን ነው ብለዋል።

ሕዝቡን በማሳተፍና በማደራጀት ሰላምን የማረጋገጥ ስራ በጋራ እየተሰራ ነው ያሉት አስተዳዳሪው በቀለ ደቻሳ አመራሩም አሸባሪውን ቡድን ከዞኑ ለማጥፋት በእቅድ እየተመራ አመርቂ ሚና እየተጫወተ ነው ሲሉም አክለዋል።

አሁን ላይ ቡድኑ በዞኑ የሚያካሂደው መስፋፋት ሙሉ በሙሉ እየደረቀ ሲሆን በአጭር ጊዜም ዞናችንን ከአሸባሪው ሸኔ ነፃ በማድረግ ለሕዝባችን የተሟላ ሰላም እናረጋግጣለን ነው ያሉት። ሙሉ ዘመቻው ህዝብና የጸጥታ ሃይሎችን አጣምሮ የተጀመረው ዘመቻ እንዲደናቀፍ ሸኔ ከታች የተመለከተውን ጥፋት ፈጽሞ እንደነበር አስተዳዳሪው አመልክተዋል።


አሸባሪው ሸኔ የሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞንን ምዕራብ ሸዋ እና ምስራቅ ወለጋ ዞን ጋር የሚያገናኘውን የሻምቡ ባኮን መንገድ ቆራረጠ

አሸባሪው ሸኔ የሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞንን ከምዕራብ ሸዋ እና ምስራቅ ወለጋ ዞን ጋር የሚያገናኘውን የሻምቡ ባኮን ብቸኛ የአስፓልት ኮንክሪት መንገድ በመቆራረጥ የትራንስፖርት ሂደቱ ላይ እንቅፋት መሆኑ ተገለፀ።

የሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ በቀለ ደቻሳ እንደሚሉት ቡድኑ አጠቃላይ የፈፀመውን ጥፋት የመለየት ስራ እየተሰራ ቢሆንም ሸኔ በሕዝቦች ላይ ያደረሰው ጉዳት ቀላል የሚባል አይደለም።

አሸባሪው ሸኔ አንቡላንሶችን ጨምሮ ሌሎች የሕዝብ አገልግሎት ሰጭ ተሽከርካሪዎችን ያለርህራሔ ማውደሙን ገልፀው በዞኑ በሚገኙ 13 ወረዳዎች ላይ ቀላል የማይባል ውድመት ፈፅሟል ብለዋል።

የሻምቡ ባኮን የአስፓልት ኮንክሪት መንገድ ከ 60 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያለው ሲሆን በተለያዩ ስፍራዎች አሸባሪው ሸኔ ቆራርጦ የትራንስፖርት እንቅስቃሴውን ለማስተጓጎል ጥረት ማድረጉም ተገልጿል።

በቅርቡ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የሻምቡ ባኮ የአስፓልት ኮንክሪት መንገድ በዞኑ ብቸኛው የአስፓልት መንገድ ቢሆንም የሽብር ቡድኑ ሸኔ ቆራርጦታል። ሸኔ ከጁንታው የሚሰጠውን ተልዕኮ የሚያስፈፅም ኃይል መሆኑን ሕዝባችን ተገንዝቦ ቡድኑን ለማጥፋት አቋም ይዞ እየታገለው ነው ሲሉ የዞኑ አስተዳዳሪ ተናግረዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የሻምቡ ባኮን የአስፓልት ኮንክሪት መንገድ ከወራት በፊት ማለትም የካቲት 14/ 2013 ዓ.ም በሆሮ ጉዱሩ ዞን ሻምቡ ከተማ ተገኝተው በይፋ መርቀው ስራ ማስጀመራቸው ይታወቃል።


Exit mobile version