Site icon ETHIO12.COM

አማራ ክልል “ቆሞ ቀር” ያላቸውን የብአዴን ቅሪቶች ያለ ምህረት እንደሚያጸዳ አስታወቀ፤ እንደሚነቀሉ ያወቁ ዘመቻ ከፍተዋል

የሕዝብ ልጅ ከመሆን ይልቅ ሸክም የሆኑ አመራሮች ከሕዝብ ትክሻ ላይ ተራግፈው የአመለካከት ጥራት ያለው፣ የወቅቱን የትግል መድረክ በድል የሚወጣ ብቁ አመራር እንዲፈጠር ያለምህረት እርምጃ እንደሚወስድ የአማራ ክልል ገዢ ፓርቲ አስታወቀ። ውሳኔው በብአዴን ዘመን እንደነበረው ” የተቸከሉ” የተባሉ የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ሃይል ስውር አገልጋዮችን እንደሚነቅል ታውቋል። በማጥራቱ እንደሚወገዱ ያወቁ ዘመቻ መክፈታቸውም ተመልክቷል።

“ልክፍት” ሲል የጠራውን ሁሉንም ዜጋ ያሰለቸ ተንኮ ለሚያቀነባበሩና ያለ እዚህ ተንኮል መኖር ለማይችሉ ” በሴራ ልክፍት እየናወዙ የለውጡ አካል ሆኖ መቀጠል አይቻልም” በሚል ፓርቲው ባሰራጨው ከወትሮ የተለይ መግለጫ፣ ሴራውን ተሸክመው በድሮ ብአዴን የተላላኪነት ማንነት እየነጎዱ ያሉትን ሁለት ቦታ አዳሪዎች እንደሚነቅል አስታውቋል።

ከለውጡ ማግስት ጀምሮ “ያልጠራ፣ ሽንፍላ” ሲባል የነበረው የአማራ ብልጽግና ይህንኑ የሚወቀስበትን ተግባር ለማረምና ቤቱን ለማጽዳት መንቀሳቀስ ከጀመረ መሰነባበቱ አልፎ አልፎ ሲሰማ መሰንበቱ ይታወቃል። በክልሉ ላይ ወረራ ሲፈጸም ተከናውነዋል ከተባሉት የክህደት ተግባራት ጋር ተያይዞ ፓርቲው ክፉኛ ሲወቀስም ነበር።

“…በየደረጃው ያለው የክልላችን አመራር ሙሉ ትኩረቱ በአሸባሪውና ወራሪውን የትግራይ ኃይል የወደሙ አካባቢዎችን መልሶ ለማቋቋም፣ ዳግም ወረራ እንዳይከፈት ለመመከት፣ ነፃ ያልወጡ ቀሪ የተወሰኑ አካባቢዎችን ነፃ ለማውጣት ብሎም ጠላትን ለመቅበር በሚያስችል ሁለንተናዊ ዝግጅት አድርጓል” ያለው የፓርቲው መግለጫ፣ “የተቀናጀ፣ የዕዝ ሰንሰለቱን የጠበቀ፣ ተጠያቂነት ያለበት አመራር በማረጋገጥ ሂደት ላይ እንገኛለን” በማለት ከመመከቱ ጎን ለጎን ያለ አንዳች ርህራሄ እርምጃ ሊወሰድባቸው የሚገባቸው ለይቶ ወደ አፈጻጸም ለመግባት መቃረቡን ያስታወቀው። ለዚህም ተግባራዊነት ከታች ጀምሮ ስራ ተሰርቶ አልቆ የድርጅቱ ጉባኤ በጉጉት የሚጠበቅበት ደረጃ ላይ ተደርሷል።

ይሁን እንጂ ፓርቲው “… እንደ ብአዴኑ ዘመን ጉባዔ በተቃረበ ቁጥር አንድም በውስጣችን ያሉ ቁሞቀሮች ለሥልጣናቸው በመስጋት በሌላ መልኩ ደግሞ በህልውና ዘመቻው የተሸነፉና ተስፋ የቆረጡ ትሕነግና የትሕነግ ወኪሎች” ሲል የጠራቸው ክፍሎች ውሳኔውን አስቀድመው ስለተረዱ ” የአልሞት ባይ ተጋድሎ ላይ ናቸው”

ፓርቲው በቅርቡ በሚያካሂደው ማጥራት እንደሚነቀሉ ስለገባቸው ፓርቲውን ከሕዝብ ለመነጠል የአሉባልታ ዘመቻ መክፈታቸው ያወሳው የአማራ ብልጽና እነዚሁ ክፍሎች ባልጸዳው እጃቸው ተናበውና ተጠባብቀው ” … ሀገርን የማፍረስ ፕሮጀክታቸውን የጉባዔውን ወቅት ተጠቅመው ለማሳካት ሰፊ የሞት ሽረት ትግል እያካሄዱ ነው። ለዘመቻቸው የሚያቀርቡት ምክንያት የተለያየ ይሁን እንጂ ግባቸው በሕዝብ አመኔታ ያገኘውን ብልጽግና ፓርቲን ከውስጥና ከውጭ መናድ፣ ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው” ሲል ስውር ዓላማቸውን አመልክቷል።

የማጥሪያው መንሽ የሚበላቸው አስቀድመው በዘረጉትና ” ቆሞ ቀር” በተባለው ትሥሥር እያሴሩ ላለው ስራ “… በሂደቱ የሚያጋጥመንን የትኛውንም አይነት የሴራ ድር በጣጥሰን የምናልፈው ሕዝብን ማዕከላችን አድርገን ነው፡፡ በዚህ ሂደት በሕዝብ ጫንቃ ላይ የወደቁ፣ በትላንት ያረጀና ያፈጀ የሴራ ፖለቲካ መንገድ እየተጓዙ የሕዝብ ልጅ ከመሆን ይልቅ ሸክም የሆኑ አመራሮች ከሕዝብ ትክሻ ላይ ተራግፈው የአመለካከት ጥራት ያለው፣ የወቅቱን የትግል መድረክ በድል የሚወጣ ብቁ አመራር እንዲፈጠር ያለምህረት እንታገላለን” ሲል ፓርቲው ሃሳባቸው እንደሚመክን አስታውቋል።

የመግለጫውን ሙሉ ቃለ እዚህ ላይ ያንብቡ።

Exit mobile version