Site icon ETHIO12.COM

[መቅመል፣ ቅማላም] – በሁለት ረድፍ

“መቅመል” ምንድ ነው? ቅማልስ ራሱ … “ቅማላም” ማለትስ? አንተ ራስህስ? አንቺስ? እኔ ራሴ .. አባት ልጁን “ቅማላም” አለው ተናዶ። ልጅ “ራስህን ሰደብክ ፓፓ” አለው። የት? አውሮፓ። ለምን? “የሚሳደብ ራሱን ይሰድባል” ተብለው ስለሚያድጉ።

በነገራችን ላይ በሱስ አበላሽተው መጨረሻቸውን ከሚያወላግዱት በቀር እዚ አውሮፓ፤ ልጆቹ ስድብ አያውቁም። ይቅርታ ቤተሰብ አላልኩም። ልጆቹ አንዳንዶቹ የዘመኑ ሳይሆን “የግዜሩ” የድሮው ያ “ኢየሱስን ይመስላል” የሚሉን ፈረንጅ ያቀፋትን ጠቦት ናቸው። እነማ ? ልጆቹ። አንዳንድ ቤሰብ ታዲያ “ልጄ ሞኝ ሆነ። ምን ላድገው” ሲሉ ይደመጣሉ። የሁለት ዓለም ኑሮ። በአካል ዘመንናው ሰፈር፣ በልቡናና በተግባር አናሎግ። ችክል። እዛው ያሉ። የማይረጥቡ። ” መቅመል ግን ምንድን ነው?”

በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን አንድ ትልቅ ነገር አለ። ቦሰና “ብዙዎች አልቀመሉም” ትላለች። የመቅመሉ በሽታ ጥቂቶችን ማጥቃቱ፣ እንደ ቀመሉት አሳብ አልሆነም። ቦሰና ለጥቂቶቹም ምክር አላት። መቅመል፣ ቅማላም ማድረግ፣ ቅማላም መሆነ፣ የውስጥ ልቡናን ያሳክካል። ልክ ድመት እንዳይወጋት እለት እለት ጥፍሯን እንደምትስል፣ በግ አናቱን ሲበላው ግንባር ለግንባር እንደሚላተም፣ ከብቶች ሲያሳክካቸው ግንድን እንደሚታከኩ …. ለቀመለ ህሊና ማሳከከ መድሃኒቱ እኛ ነን። ሲበላቸው ይተፉብናል። ሲበላቸው ያራግፉብናል። ሲያሳክካቸው የደፉብናል …

ያበደው መቀባጠር ካቆመ ቆይቷል። ዛሬ የሚቀባጥረው ወዶ አይደለም። ተገዶ ነው። በነገራችን ላይ ድሮም ተገዶ እንጂ ወዶ ቀባትሮ አያውቅም። ደግሞ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቀባጣሪ ያላደረገው ማን አለ? ለማንኛውም ሰላም ይብዛላችሁ። ስለም ለምትሹ ይሁንላችሁ። ሰላም መሻት ነው። ሰላምን ካልፈለጓት አያገኟትም። በመጣፉ “ከተቀበሉ ስጧቸው፣ ካልሆነም ትቢያችሁን አራግፉና ውጡ” የተባለው ለሰላም ነው። እናም ለምትሿት ሁሉ ያበደው ሰላም ይላል። “ቅማላም” ለሚሉም “ለቀመሉም” ሰላም ይሁንላቸው። ለራሱ ለያበደውም።

ቦሰና ሊፒስቲክ አትወድም። ከንፈሯ በተፈጥሮ የልጃገረድ ፍየል ሰበር ይመስላል። ያበደው ፈገግ አለ። ልጃገረድ ፍየል?። ” ምን በወጣንኛ ይህን ቀለም የተነከረ የጦጣ በጠጥ” እከንፈሬ ላይ” ትላለች። ሊፒስቲክ ለቦሰና የማን እንደሆነ የማይታወቅ “አር” ነው። “ማናምናቸውን ከተውበት እንጅ ፍግ ነው” ትላለች። ስትኮምክና ጨዋታውን ማሞቅና መሟሟቅ ሲያምራት ደግሞ በሰበር ጀምራ ምንጃርኛውን ታስነካዋለች። ምንጃርናውን ከሰላሌ ጭፈራ ጋር ስታዋህድ ስልጥኖ የትወለደ ሰጋር በቅሎ እንጂ …. ወዴት ወዴት …?

“የቀመልነው ከውስጥ ነው። ተባዩ ቅማል እንዳይመስልህ” አለች በድንገት። ቦሰና ብዙ አድማጭ እንጂ ተናጋሪ አይደለችም። ቀን በቀን ወይም በቀን ሁለትና ሶስቴ አማትቦ ጀምሮ ሲራገም የሚውለውን፣ “ሰውዬ” ነው የምትለው ” የመቅመል ምሳሌ” ስትል ስም ሰጥታዋለች። ሌሎችንም እንዲሁ ትላቸዋለች። ይሕኛውን ግን “አዶ ከርቢያም” ስትል ትጠራዋለች።

ደጎል የአዶ ከርቤ ስም ሲነሳ ጆሮው ይቆማል። ባዕድ ነገር እንደሆነ ይገባዋል። ደጎል ደረጃው ከአምላክ በታች፣ ከሰው በላይ ነው። ቦሰና ሰው “ውሻ” ብሎ ሲሳደብ ” ከሱ በታች ናቹህ” ብላ ስድቡን መሉዕ ታደርጋለች። ደጎል ለሷ ሰው ነው። ቤቱን ያውቀዋል። የቤቱን ደንብ ይረዳል። ለቤቱ ህግ ይገዛል። የሚጠላው ትንተና ነው። የተንታኞችን ድምጽ ሲሰማ ይወራጫል። እንደውም ያዞረዋል። ንግግር ቢለማመድ ” መጥኔ ለናንት” ማለቱ አይቀርም ነበር። አንዳንዴ ንግግር አይሉት ብቻ ያልጎመጉማል። ቻይኖች ጋር ሄደን ምክር እንዳንጠይቅ ቻይናና ውሻ … ያበደው ጎፈነነው። ቻይና ግን ምንድነው የማይበላው?

አንድ ቀን ሳያቋርጡ ሰዓት አክብረው ለሚራገሙ ቦሰና ታዝናለች። እነሱን በቀተሮ ሰዓት ቁጭ ብለው ለሚያዳምጡ ደግሞ ምህረትን ትማልዳለች። እርግማናቸውን በየዋህነት ለሚያሰራጩና ለሚያራቡት ደግሞ “የት አግኝቼ በቀመልኳቸው” ስትጠየፍ የምትለው ነው።

ቅማል ሁለት መልክ አለው። የድሮው ቅማል አናት ላይ ፈልቶ ቅጫም የሚያራ ነው። የድሮ ቅማል ኮሌታና መለመላ ውስጥ ተመሽጎ ደም የሚመገብ ነው። የድሮ ቅማል በውሃና ሳሙና የሚወገድ፣ ምላጭ የሚፈራ ነበር። ፊሊት ከሸተተውማ ያልቅለታል። ቦሰና እንደምትለው የድሮ ቅማል ፋራ ነው። ያሳክካል እንጂ እላፊ አይሄድም። ሲበዛ ለመናፈስ ወደ አናት ጫፍ ሲጓዝ ማጅራት ላይ ከመታየቱ … ታንከኛው!! አማኑኤል ሆስፒታል የሰጡት ስም ነው። አምኑኤል ሆስፒታል የሚጠሉት ቱሃንን ነው። ብዙ ይጠጣል።

በቦሰና ገለጻ ሁለተኛው ቅማል፣ መቅመል፣ ቅማላምነት፣ ቅማሎች … አሁን ላይ የሚስተዋለው ነው። ተላይ ሳይሆን እውስጥ የሚራባ። እውስጥ ሰው ማሰቢያ ውስጥ ዘሩን የሚቀያየር። የሚያረግዝ። የሚፈለፈል። ሲፈቀድለት በሰው ልቡና ውስጥ የሚቀነዝር ይሉታ ቢስ መርዝ። መቅመል!!

ጎበዝ አልቀመልንም? አልቀመልክም? አልቀመሉም? የቅማል መራቢያ አልሆንክም? አልሆንሽም? ድሃ ሲያልቅ “እሰይ” የሚባለው በጤና ነው? አንዱን ከሌላው ማባላት ከአስተሳሰብ መቅመል ውጭ ምን ሊባል ይችላል? በሰላም መሬት እየቧጠጡ የሚኖሩ ምስኪኖችን እየገደለ ቪዲዮ የሚለጥፈው አለቀመለም? ወይም የልቡናው መካከሉ ትል አልተራባበትም? …. ያበደው ከተቀመጠበት ተነሳ።

የተፈናቀሉ እናት፣ አባት፣ ሃጻናት፣ ነብሰጡሮችን ምስል አየ። ላይክ ምልክት ተሰጥቷቸዋል።… ሰበር ዜና የሚሉትን አየ። ወገን ወገኑን እዚህ ግባ ለማይባል ምክንያት ይበላል። የተበላው መልሶ ይበላል። ወገን ወገንን በበላና በተበላላ ቁጥር ሰበር ዜናዎች ይጮሃሉ …. ያበደው እንባ አቆረዛ… ቦሰናን ሳይሰናበት ውልቅ አለ።

“ቅማላሞች ነን። ቀምለናል። ቅማል ተራብቶብናል። የቅማል መናኸሪያ ሆነናል።” እያለ ነጎደ። ወደየት እንደሚሄድ አያውቅም። ግን ያገኘውን ” አልቀመልክም፣ አልቀመልሽም” እያለ ያልፋል። ተራውን ቅማል መስሏቸዋል። አውሮፓ ባለቤቱ ካልጋበዘው በቀር በችግር ሳቢያ የሚከሰት ታዋቂው ቅማል የለም። ግን የቀመሉ አሉ። የውስጥ ቅማል!!

የዕርቅና የሰላም ኮሚሽኑ ሰብሳቢ የአዕምሮ ሊቅ ናቸው። አምላክ ይርዳቸውና የህን የውስጥ ቅማል ይጥረጉልን። ያበደው በጎ ተመኘ። በጎ ሲመኝ በአንዴት ትኩሳቱ ለቀቀው። ሟረተኞችን ተረጋግቶ መከረ። ገና መመስረቱ በወጉ ላልተሰማ “ዕንቁ” ለሆነው ኮሚሽን ” መፍረስን” አታውጁበት። መቋቋሙን ሰምተን ሳናበቃ “እንደሚፈርስ አስጠነቀቁ” የሚል ሰባራ ሚዛን አትስፈሩ። መርዶ ሳይሆን ተስፋን ስበኩ። ሟርትን ሳይሆን መልካምን ተመኙ።

የመቅመል በሽታ ሁሉም ጋር አለ። ሁሉም ዓይነት ሙያ በመቅመል ጣጣ ሊበከል ይቻላል። እዛም እዚህም “መበስበስ” አለ። መለስ ነብሳቸውን አንድዬ እንዳሻው ያድርገውና ” በስብሰባል፣ ገምተናል” ይሉ ነበር። እውነት ነው። እውሸት የነበረው ለሚዲያ ፍጆታና “ለምን” ያለን ውገን ለመብላት የተፈበረከ ምክንያት መሆኑ ነው።

በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን አንድ ትልቅ ነገር አለ። ቦሰና “ብዙዎች አልቀመሉም” ትላለች። የመቅመሉ በሽታ ጥቂቶችን ማጥቃቱ፣ እንደ ቀመሉት አሳብ አልሆነም። ቦሰና ለጥቂቶቹም ምክር አላት። መቅመል፣ ቅማላም ማድረግ፣ ቅማላም መሆነ፣ የውስጥ ልቡናን ያሳክካል። ልክ ድመት እንዳይወጋት እለት እለት ጥፍሯን እንደምትስል፣ በግ አናቱን ሲበላው ግንባር ለግንባር እንደሚላተም፣ ከብቶች ሲያሳክካቸው ግንድን እንደሚታከኩ …. ለቀመለ ህሊና ማሳከከ መድሃኒቱ እኛ ነን። ሲበላቸው ይተፉብናል። ሲበላቸው ያራግፉብናል። ሲያሳክካቸው የደፉብናል …

ያበደው የቦሰናን እይታ እያሰበ መንገድ ቀይሮ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ደጎል ምሱን ፍለጋ ጭራውን በክራት አወዛወዘ። ያበደው አጻፋውን መለሰለት። ቀና ሲል ቦሰና… እንደ ጊደር ፍየል የሚያበራውን ከንፈሯን አየው። እያሰባት ስለመጣ ብዙም ወሬ አላስፈጋቸውም። ሳይስበው ተስፈንጥሮ ያዛት … ያበደው “ሰዓቱ ገና ነው” በሚል ስሜት ተሽኮረመመ።

ቦሰና ጫካ ማለት ነው። ጫካ ይደብቃል። ቦሰና መደበቂያ ነች። ቦሰና እድል ናት። ቦሰና የጎደለውን ሁሉ ትሞላለች። ቦሰና … ምርጥ ነች። የማያውቋት ይፈርጇታል። እሷ ግን ቁብ የላትም። “መቅመል አልፈልግም” የሚል ምላሽ አላት። ቦሰና … ሰላም እንሰንብት … ሻሎም… ያበደው ከበረሃ!!

Exit mobile version