ETHIO12.COM

ኢትዮጵያና ጅቡቲ በፀጥታና ደኅንነት፣ በትምህርትና ስልጠና፣ እንዲሁም በሰላም ማስከበር በትብብር ለመሥራት ተስማሙ

9ኛው የኢትዮ- ጅቡቲ የመከላከያ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹሞች ስብሰባ በአዲስ አበባ የመከላከያ ጠቅላይ መምሪያ ተካሂዷል።

የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ የጅቡቲ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀነራል ዘካሪያ ሼክ ኢብራሒም፣ የኹለቱ ሀገራት ፖሊስ ኮሚሽነሮች እና ጀነራል መኮንኖች እንዲሁም በኢትዮጵያ የጅቡቲ አምባሳደር በተገኙበት ነው ስምምነቱ የተፈረመው።

ስምምነቱን የፈረሙት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ ኢትዮጵያ እና ጅቡቲ ታሪካዊና የረጅም ጊዜ ግንኙነት ያላቸው ሀገሮች መኾናቸውን አውስተዋል። በባህልና በቋንቋም የጋራ አንድነት ያላቸው ወንድማማች ሕዝቦች ናቸው ብለዋል።

የኹለቱ ሀገራት ጥምር የመከላከያ ሠራዊት ኮሚቴ በስትራቴጂክና በቴክኒክ መስኮች በጋራ ለመሥራት ስምምነት ላይ መደረሱ ለቀጣናዊው ሰላምና ፀጥታ መረጋገጥ ትልቅ ፋይዳ አለው ነው ያሉት።

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ ኢትዮጵያ እና ጅቡቲ የተለያዩ ዓለም አቀፍና አህጉር አቀፍ ተቋማት መቀመጫ ናቸው ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ፣ ሀገራቱ በሰላም ማስከበር ተልዕኮም ያላቸውን ሚና አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።

ጀነራል ዘካሪያ ሼክ ኢብራሒም በበኩላቸው፣ ቀደም ሲል የኹለቱ ሀገራት ፌዴራል ፖሊሶች በድንበር አካባቢ የተለያዩ ወንጀሎችን በጋራ ለመከላከል መፈራረማቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ በመከላከያ ደረጃ በትብብር ለመሥራት ያደረግናቸው ስምምነቶች ለኹላችንም የሚጠቅም ወሳኝ ስምምነት ነው ብለዋል።

የመከላከያ ውጭ ግንኙነት ዳይሬክተር ብርጋዴር ጀነራል ቡልቲ ታደሰ፣ ኢትዮጵያ እና ጅቡቲ በጋራ ድንበራቸው ላይ ቅኝት ማድረግ፣ በመረጃ ልውውጥ ፣ ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴን በመከላከል፣ በባህል ልውውጥ ፣ በስልጠና እንዲሁም ሽብርተኝነትን ለመከላከልና በሰላም ማስከበር ተግባራት አንድነታቸውን ለማጠናከር መስማማታቸውን ተናግረዋል፡፡

ቀደም ሲል የጅቡቲ ወታደሮች በኢትዮጵያ የተለያዩ ወታደራዊ ስልጠናዎችን የወሰዱ መኾናቸውን አውስተው በቀጣይም የዕውቀት ሽግግሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል መግለጻቸውን ከመከላከያ ሠራዊት የተገኘ መረጃ ያመላክታል።

የካቲት 28/2014 ዓ.ም (አሚኮ)

Exit mobile version